(በስንታየሁ ግርማ)

 የአሜሪካው ሁቨር ግድብ እ.ኤ.አ በ1929 እና በ1930ዎቹ በአሜሪካ ተከስቶ የነበረው የኢኮኖሚ ድቀት ወቅት የተገነባ ግድብ ነው፡፡ ግድቡን ለመገንባት በ10000ዎች የሚቆጠሩ አሜሪካኖች የተሳተፉ ሲሆን በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተሰውተዋል፡፡ ግድቡ ለኔቨዳ ለአርዞንያ እና ለካርፎርኒያ ወዘተ ምእራብ ግዛቶች ዋነኛ የሀይል እና የብልፅግና ምንጭ ሲሆን በየዓመቱ በሚሊዬን የሚቆጠሩ ቱሪስቶች መናኽሪያ በመሆን በአሜሪካ ብልፅግናም ከፍተኛ አስተዋፆኦ አድርጓል፡፡ በተለይም ለምእራብ አሜሪካ ብልፅግና ቁልፍ ሚና አለው፡፡ ስያሜውን ያገኘውም ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ሐርፐርት ሁቨር ነው፡፡

ኢንጅነር ስመኘው በቀለ ለዋሽንግተን ፖስት በአንድ ወቅት እንደተናገሩት እንደሁቨር ግድብ ሁሉ የታላቁ የህዳሴ ግድብ ኢትየጵያን ወደ ሥልጣኔ ማማ በመመለስ ታሪክ ይጻፍለታል ብለዋል፡፡ ኢንጅነር ስመኝ እንደሚሉት ሁቨር ግድብ ለአሜሪካ ስኬት አሰተዋጽኦ አለው ይላሉ፡፡

ምንም እንኳን ኢትዪጵያ ግድቡ ሁሉንም በፍትሀዊነት ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ብትገልፅም ግብፅ በተደጋጋሚ እና በተከታታይ እርስ በእርሱ የሚጋጩ መግለጫዎችን ስትሰጥ እና ድርጊቶችን ስታከናውን እየታየች ነው ፡፡ ሰሞኑን ደግሞ ግብፅ አሸባሪውን ኦነግ ጋር በመለጠፍ ስለህዳሴው ግድብ መቆም ቅዠት እያሰማች ነው፡፡

Photo - Grand Ethiopian Renaissance Dam, 2016. [Photo: Reuters/Tiksa Negeri]
Photo – Grand Ethiopian Renaissance Dam, 2016. [Photo: Reuters/Tiksa Negeri]

ግብፅ የህዳሴው ግድብ እንደሚጠቅማት እና ጉልህ ጉዳት / No significant harm/ እንደማያደርስ ብታውቅም የኢትዮያን እድገት እና ልማት በአዎንታዊ መልኩ ልታየው እና ልትቀበለው አትችልም፡፡ የመጀመሪያው ምክንያት ለጥቁር ህዝብ (ለአፍሪካ) ካላት ዝቅተኛ አመለካከት ይነሳል፡፡ ሁለተኛ የኢትዪጵያ መልማት በአፍሪካ እና በአለም ተቀባይነትን ማሳደግ በቀጣይ አባይን የመጠቀም አቅም ያሳድጋል: ለሌሎች የተፋሰሱ ሀገሮች አይን ይገልጣል ይህም ግብፅን ይጎዳል የሚል ስጋት አለባት፡፡ በሶስተኛ ደረጃ የግብፅ አብዮት መሰረታዊ እና መዋቅራዊ ችግሮች አሁንም አልተፈቱም፡፡ ችግሮቹ ተፈተዉ ፍትሀዊ የሀብት ክፍፍል እሲኪሰፍን ገዢዎቹ አባይን የትኩረት ማስቀየሸ ያደርጉታል፡፡

የቅኝ ገዢ ውሎችን በመጥቀስ ናይልን የመጠቀም አለም አቀፍ መብት የእነሱ ብቻ እንደሆነ የሚገልፁ አንዳንድ ግብጻውያን አሉ፡፡የአባይ ወንዝን በተመለከተ የመጀመሪያው ስምምነት የተካሄደው እ.ኤ.አ. በ1891 ነበረ፡፡ በዚህ ስምምነት መሠረት ጣሊያን በአታባራ ወንዝ ላይ ግድብ ላለመስራት ከእንግሊዝ ጋር እንደተስማማች የሚያነሱ አሉ፡፡ ፕሮፌሰር አሊ አብደላ አል ግን በስምምነቱ በግል ቋንቋ ያልተቀመጠ ነው ይላሉ፡፡ ፐሮፌሰር አሊ በሱዳን የኡምድሮማን ዩኒቨርስቲ መምህር ናቸው፡፡

ሁለተኛው ስምምነት እ.ኤ.አ. ከ1902 በእንግሊዝ፣ ከጣሊያን እና በአፄ ሚኒሊክ የአባይን ወንዝ ላለማስቀረት እንደተስማሙ የሚያስቀምጡ አሉ፡፡ በሌላ በኩል ስምምነቱ በወቅቱ የእንግሊዝ እና የኢትዮጵያ መንግሥት የዘውድ ም/ቤት ስላላፀደቁት ተቀባይነት የለውም የሚሉ አሉ፡፡ የእንግሊዝኛው እና የአማርኛው ፍቺዎች የተለያዩ በመሆናቸው ኢትዮጵያ እንዳላፀደቀችው ፕሮፌሰር አሊ ይናገራሉ፡፡

የ1929 እና የ1959 ስምምነት ለ”ታሪካዊ መብት” ዋነኛዋቹ መነሻዎች ናቸው፡፡ በእነዚህ ስምምነቶች መሠረት፡-

– ግብፅ እና ሱዳን ጠብታ ውሃ ሳያስቀሩ ሙሉ በሙሉ በራሳቸው ተከፋፍለውታል፣

– ሌላ ይገባኛል የሚል ሀገር ከመጣ ከሁለት ሀገራት እኩል እንዲቀነስ ተስማምተዋል፣

– ግብፅ በናይል ወንዝ ላይ የሚሰራ ግድብን ድምፅ በድምፅ የመሻር መብት አጎናፅፏታል፣

– በሌሎች ሀገሮች በወንዙ ላይ የሚሠሩ ሥራዎች ለመከታተል የሚያስችል የቴክኒክ ቡድን ለማቋቋም ተስማምተዋል፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን ሃሳቦች ከዓለም አቀፍ ሕግ እና ተቀባይነት ካለው መርህ አንፃር ማየቱ ተገቢ ነው፡፡

– በመጀመሪያ ደረጃ ግብፅ እና ሱዳን በ1929/በ1959 እኩል ተጠቃሚ ናቸው ብሎ መውሰድ ተገቢ አይደለም፡፡ በ1929 ስምምነት ግብፅ ሱዳንን አላማከረችም፣፣ ምክንያቱም በወቅቱ ሱዳን በእንግሊዝ ግዛት የግብፅ አንድ አካል ተደርጋ ስለምትወሰድ ነበር፡፡ በ1959 ስምምነት ደግሞ የሱዳን ውሃ ባለሙያዎች አስተያየት ግምት ውስጥ ሳይገባ የሱዳን ባለሥልጣናት ግብፅን በመፍራት እንደፈረሙት ፕሮፌሰር አሊ ታሪክን በመጥቀስ ይከራከራሉ፡፡ ከሁሉም በላይ በስምምነቱ የታችኛው የተፋሰስ ሃገራት በተለይም 86% የውሃ ምንጭ የሆነችው ኢትዮጵያ ሀሳቧ አልተካተተም፡፡ የስምምነቱም አካል አይደለችም፡፡ አንድ ስምምነት ተቀባይነት ያለው አለም አቀፍ ሕግ ሊሆን የሚችለው ስምምነቱን በፈረሙት እና ባፀደቁት አካላት መካከል ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያም ሆነች ሌሎች የተፋሰስ ሀገራት በሁለት ስምምነቶች የመገዛት ግዴታ የለባቸውም፡፡

– ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን በተመለከተ ደግሞ በአሁኑ ሰዓት ተቀባይነት ያለው መርህ የእኩል ተጠቃሚነት እና ከፍተኛ ጉዳት ያለመድረስ መርሆዎች ናቸው፡፡ በእነዚህ መመዘኛዎች መሠረት የ1929 እና የ1959 ስምምነት ዘጠኝን የተፋሰሱ ሀገራት ያገላል፡፡ በመሆኑም ውሎቹ ከላይ የተጠቀሱትን መርሆዎች የሚጥሱ በመሆናቸው በዓለም አቀፍ ማህበረሰብ እና ጉዳይም ወደ ገላጋይ ቢሄድ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ስምምነቶቹ በይዞታቸው የእኩል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሳይሆን የሚያገሉ (Discriminatory) በመሆናቸው በዓለም አቀፍ ሕግ ተቀባይነት የላቸውም፡፡ ለነገሩ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ለመላክም ኢትዮጵያ መስማማት ይኖርባታል፡፡

– እ.ኤ.አ. ሜይ 21/1997 የተመድ ለመጓጓዣነት የማይውሉ ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን አጠቃቀም ባወጣው ኮንቬሽን መሠረት ሁሉም የተፋሰስ ሀገራት ወንዙን በሚጠቀሙበት ጊዜ የእኩል /ፍትሃዊ/ አጠቃቀም መርህን በዋነኝነት መከተል እንዳለባቸው ያስቀምጣል፡፡ እኩል የመጠቀም መብት መርህ በተመለከተ አንዳንዶቹ በሁሉም ሀገራት እኩል ማከፋፈል ነው በማለት ይተረጉሙታል፡፡ ይህ ግን በአብዛኛው ተቀባይነት የለውም፡፡ በኮንቬሽኑ መሠረት የእኩል /ፍትሃዊ ሚዛናዊ መርህ የሚከተሉትን መስፈርቶች የሚይዝ ነው/ በአንቀጽ 6 መሠረት/

1) የጂኦግራፊ፣ የሃይድሮ ግራፊክ፣ የሃይድሮሎጂክ፣ የኦኮሎጂካል እና ሌሎች የተፈጥሮ ሁኔታ መመዘኛዎች፣

2) በተፋሰስ የሚገኝ ሀገራት ያለው የኢኮኖሚ እና ማህበራዊ ፍላጎቶች፣

3) አንድ ሀገር ውሃውን ሲጠቀም በሌላኛው ተፋሰስ ሀገር ላይ ያለው ተፅዕኖ፣

4) በጥቅም ላይ ያለ እና እምቅ የውሃ አቅም፣

5) ውሃውን ለመጠበቅ፣ ለመከላከል፣ ለመበልፀግ ያለው ጠቀሜታ እና ለዚህ የሚውለው ወጪ፣

6) አማራጭ የውሃ ምንጮች

በእነዚህ መመዘኛዎች መሠረት ሀገራት መከፋፈል እንዳለባቸው ኮንቬሽኑ ያስቀምጣል፡፡ በእነዚህ መመዘኛዎች መሠረት ያልተከፋፈለ ድንበር ተሻጋሪ ወንዝ አጠቃቀም በድርጅቱ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ለእነዚህ መመዘኛዎች ቀረቤታ ያለው የቅኝ ግዛት ውሎች ሳይሆኑ የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት /የኢንተቤ ስምምነት/ ነው፡፡ ስለዚህ ለግብፅ እና ሱዳን በዘላቂነት የሚያዋጣቸው የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት መሠረት መፈረም ነው፡፡ ለነገሩ ስምምነቱን ከአባል ሀገራት 2/3ኛው ካፀደቁት ዓለም አቀፉ ተቀባይነት እና አስገዳጅነት ያለው ሕግ ይሆናል፡፡ እስካሁን ስምምነቱን ኢትዮጵያ አፅድቃዋለች፡፡ በቀጣይም ዩጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ኬንያ፣ ታንዛንያ እና ሱዳን ያፀድቁታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜም ናይልን በተመለከተ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው ሕግ ይሆናል፡፡

በ1997ቱ የተመድ ኮንቬሽን መሠረት ከእኩል ተጠቃሚነት በተጨማሪ ጉዳት ያለማድረስ መርህ ሌላኛው መመዘኛ ነው፡፡ የህዳሴውን ግድብ በተመለከተ በግብፅ ላይ ትርጉም ያለው ጉዳት እንደማይደርስ በተደጋጋሚ ኢትዮጵያ አስቀምጣለች፡፡ እንዳውም የግድቡ ሥራ ሲጀመር ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ ፍትሃዊነቱ ቢሆን ኖሮ የግድቡን ወጪ ሥራን 20 በመቶ ሱዳን 30 በመቶ ግብፅ ሊሸፈኑ ይገባ ነበር ይላሉ፡፡

ባለሙያዎች እንደሚገልፁት በኢትዮጵያ የሚሠራ ግድብ ትነትን በመቀነስ ተጨማሪ ውሃ ያስገኛል፡፡ በኢትዮጵያ የሚሠራ የተፈጥሮ ሀብት እንክብካቤ የታችኛው የተፋሰስ ሀገራት ግድብ ከጎርፍ እና በደለል ከመሞላት ይከላከላል፡፡ የተመጠነ የውሃ ፍሰት ዓመቱን ሙሉ እንዲኖር ያስችላል፡፡ በተመጣጣኝ ዋጋ የሃይል አቅርቦት እንዲኖር ያስችላል ይላሉ፡፡ አንዳንድ የዘርፉ ባለሙያዎች ምክራቸውን ሲለግሱ ዘላቂው ስትራቴጂ የአባይን ወንዝ በዘላቂነት ለመጠቀም ውሃው የሚከማችበትን አስዋን ግድብ ከፍተኛ ትነት ካለበት ግብፅ እና ሱዳን ይልቅ ወደ ቀዝቃዛው የኢትዮጵያ ክፍል ማሸጋገር ነው ይላሉ፡፡

አንዳንድ ግብፃዊያን የሚያቀርቡት  የመከራከሪያ ነጥብ 55.5 ቢሊዮን ኪቢዩክ ሊትር ውሃ የመጠቀም ታሪካዊ መብት አለኝ ይህም ተለምዷዊ አለም አቀፍ ሕግ ሆኗል የሚል ነው፡፡ እንደ ልምድ ተቀባይነት ያለው ተለምዷዊ አለም አቀፍ ሕግ ተቀባይነት የሚኖረው ተቃዋሚ ወገን ሳይኖር ሲቀር ነዉ፡፡ ይሁንና ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የመጠቀም መብት እንዳላት ለግብጽ እና ለሌሎችም በየጊዜው ከማሳወቋም በላይ ቅኝ ገዢዎች እና ግብጽ ኢትዮጵያን በማግለል የተዋዋሉትን ስምምነቶች በተደጋጋሚ ለሀገሪቱ እና ለዓለም አቀፍ ተቋማት ለሊግ ኦፍ ኔሽን እና ለተ.መ.ድ. በፅሁፍ መግለጻቸው ይታወቃል፡፡

በተለይ የአጼ ሚኒሊክ እና የአጼ ኃይለሥላሴ ተቃውሟ በፅሁፍ ሰፍረው ይገኛሉ፡፡ ስለዚህ ታሪካዊ መብት የሚባለውን ኢትዮጵያ ተቃውሞዋን የገለፀችበት ስለሆነ በዓለም አቀፍ ሕግ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ በተጨማሪም በ1978 የቬየና ኮንቬሽን መሠረት ሀገራት ከቅኝ ግዛት ሲላቀቁ መውረስ ያለባቸው ድንበር እንጂ ሌሎች መብቶችን እና ግዴታዎችን እንዳልሆነ ያስቀምጣል፡፡ የቅኝ ገዢዎች ውል /ስምምነት/ በየጊዜው ካለው የሰው ልጅ ፍላጎቶች ጋር የሚያያዙ እና የሚሻሻሉ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ መቅደም ያለበት ውል ሳይሆን የሰው ልጅ ፍላጎት ነው፡፡ በ1920ዎቹ እና በ1950ዎቹ ያሉ የሰው ልጅ ፍላጎት ከ21ኛው ክፍለ ዘመን ጋር አንድ እና ያው ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ስለዚህ የሰው ልጅ ፍላጎት ጋር ውሳኔዎች በየጊዜው እየተሻሻሉ መምጣት ይገባቸዋል፡፡ ሀገራት በቅኝ ገዢዎች አማካኝነት የተገቡትን ስምምነቶች የማክበር ግዴታ የለባቸውም፡፡ ሀገራት ከቅኝ ገዢዎች ውል ግዴታ የነፁ መሆን እንዳለባቸው ኮንቬንሽኑ ይደነግጋል፡፡ ሲጠቃለል የአባይን ወንዝ በተመለከተ ለኤሌክትሪክም ሆነ ለሌላ አገልግሎት የሚውል አለም አቀፍ ሕግ ኢትዮጵያን የሚደግፍ እንጂ የሚከላከል አይደለም፡፡

********

Guest Author

more recommended stories