የመምህራን ምዘና ሚዛኑን ይጠብቅ

(Ephrem Tekle Yacob)

የመምህራን ምዘና በተለምዶ ሁለት ዋና ዓላማዎች አሉት:: በመጀመሪያ ሙያዊ ጥንካሬ እና ድክመቶችን በመለየት የመምህራንን አሰራር ለማሻሻል ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ መምህራን የተማሪውን ትምህርት ለማሻሻል የተቻላቸውን ያህል እዲጥሩ ማስቻል በዚህም ተጠያቂነትን ማስፈን ነው:: ሁለቱ ተግባራት ሚዛናቸውን ጠብቀው ሊሔዱም ይገባል::

በቅረቡ እደተረዳሁት የመምህራን ምዘና በተደረገባቸው አካባቢዎች ቁጥራቸው ከፍተኛ የሆኑ መምህራን ከምዘናው የሚጠበቅባቸውን ውጤት አላመጡም::

ምዘና የትምህርት ስራቱ በተወዳዳሪ መምህራን እዲሞላ እና የትምህርት ጥራቱን ለማስጠበቅ የራሱ የሆነ ሚና አለው:: በመሆኑም ምዘነው የበለጠ ሊበረታታ ይገባል::

ሆኖም የምዘናውን ውጤት በማስጮህ ሊመጣ የሚችለው ለውጥ የጎላ ነው የሚል እምነት የለኝም:: ይህ በተበራከተ ቁጥር መምህራን ከድጋፉ በላይ ተጠያቂነቱ ሊያመዝን እደሚችል በማሰብ ለምዘናው ሒደት ተገቢውን ትብብር ከማደረግ ይቆጠባሉ:: ያለመምህራን ተሳትፎ የተሳካ ምዘና ማደረግ ደግሞ የሚታሰብ አይደለም::

ምዘናው እንደሚነግረን የትምህርት ስራቱ ውስጥ ብቃቱ ያልተረጋገጠ መምህር ተበረክቱል ከተባለ ለዚህ ትልቁን ሚና የተጫወተው የማይጨበጠው እና በግብታዊነት የሚቀያየረው የመምህራን ስልጠና ስራታችን መሆኑን ሊዘነጋ አይገባም::

የ2007 የትምሀርት ሚኒስቴር አመታዊ አብስትራክት እደሚያሳየው  በሐገሪቱ ከቅድመ መደበኛ እስከ መሰናዶ ድረስ 497፣735 መምህራን የነበረ ሲሆን 429፣288 ወይንም 86.24 ፐርሰንቱ እድሜያቸው ከ 40 አመት በታች ነው::

በመሆኑም እነዚህ መምህራን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በስራ ላይ ያለው የትምህርት ፖሊሲ ውጤት ናቸው:: ምዘናው ባጠቃላይ የትምህርት ማዕቀፉ አካል እንጂ ብቻውን ተነጥሎ ሊታይ አይገባም:: የምዘናው ውጤት ወደሁላ ተምልሰን የመምህራን ቅበላን፣ ስልጠናን እዲሁም ተከታታይ ማብቃትን እና ማበረታቻ ስራታችንን  የምንፈትሽበት መነሻ ሐሳብ ሆኖ ማገልገል አለበት::

በምዘናው ውስጥ ያለፉ እና ወደፊትም የሚያልፉ መምህራን ውጤታቸውን ማእከል ያደረገ ሞያዊ ድጋፍ ሊሰጣቸው ይገባል:: በተጨማሪም መምህራን ቢያንስ ከሌላው ሲቪል ሰርቪስ ያላነሰ ማበረታቻ ሊያገኙም ይገባል:: ግለሰባዊ ሚናቸው የጎላ መምህራንን እንደ ሚናቸው ማበረታታት ግድ ይለዋል:: ይህም በሒደት ብቁ የሆኑ ግለሰቦችን ወደ ሙያው ለመሳብ ያስችለናል::

ሌላው ልዩ ትኩረት የሚሻው የምዘናው ተገቢነትና የመዛኙ ብቃትም ምንያህል እደሆነ ግልፀ የማድረጉ ጉዳይ ነው::

የመመዘንና ግብረመልስ በተገቢው የመስጠት ተቋማዊ ብቃት ሊታይ ይገባል:: ከዚህ አንፃር ለመመዘን፣ ለመመዘን እዲሁም የምዘናውን ውጤት ለመማር ማስተማሩ ሒደት ማዳበሪያ አድርጎ ለመጠቀም በቂ ዝግጅት ከማድረግ በተጨማሪም ውጤቱን መሰረት ያደረገ ተቋማዊም ሆነ ግለሰባዊ ተጠያቂነትን ሚዛኑን በጠበቀ መልኩ ማስረጽ የሚቻልበት ቁመና ሊፈተሽ ይገባል::

የመምህራን ምዘና ውጤታማነት በመዛኙም ሆነ በተመዣኙ በኩል ተገቢ የሆነ ብቃትና ክህሎት ላይ የተመሰረተ ሞሆኑ ግንዛቤ ሊወሰድ ይገባል:: በሌላ አነጋገር የምዘናው ውጤት የተመዛኙን ክፍተት ብቻ ሳይሆን የመዛኙንም ችግር ነፀብራቅ ነው::

እንግዲህ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስቴር በተከታታይ ስለመምህራን እና ስለ ትምህርት ስርአቱ ማሻሻያ ያነሱት ሐሳብ በባለሞያው ታግዞና ዳብሮ የበለጠ ተጠናክሮ ወደ መሬት ሊወርድ ይገባል እላለሁ::

********

* The writer, Ephrem Tekle Yacob, is a PhD Candidate at the Institute of Educational Science of Heidelberg University, Germany.

Guest Author

more recommended stories