ሚኒስተር መላኩ ፈንታ በሙስና ተጠርጥረው ታሠሩ [የመግለጫው ሙሉ ቃል]

ከኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ መንግስት የፌዴራል የስነ ምግባር ጸረ ሙስና ኮሚሽን የተሰጠ የዜና መግለጫ

በዛሬው እለት የፌዴራል የስነ ምግባር ጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ ሁለት የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት የሚገኙባቸውን 12 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር አውሏል፡፡

እንደሚታወቀው ሁሉ ኮሚሽኑ በህዝብና በመንግስት ንብረት ላይ የሚፈፀምን የሙስና ወንጀል ተከታትሎ አስፈላጊውን መረጃ በማሰባሰብ ተጠርጣሪዎችን በህግ ፊት አቅርቦ በማስጠየቅ ሙስናን የመከላከልና የመቆጣጠር ሃላፊነት በአዋጅ የተሰጠዉ አካል ነው፡፡

አገራችን ኢትዮጵያ የተያያዘችዉን የልማትና የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ በማጠናከር የህዝቦቿን ተጠቃሚነት ታጎለብት ዘንድ ሙስና መከላከል አማራጭ የሌለው አገራዊ ተግባር ነዉ፡፡ ከዚህ መሰረታዊ ግንዛቤና ቁርጠኝነት በመነሳት ኮሚሽኑ ከልዩ ልዩ መንግስታዊ አካላትና ከመላ የሃገራችን ህዝቦች ጋር በመደጋገፍ በተለያዩ ተጠርጣሪዎች ላይ ህጋዊ ስርዓቱን ተከትሎ ምርመራ በማካሄድና በቂ ማስረጃ የተገኘባቸውን ለፍድ አቅርቦ በማስቀጣት ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡

ኮሚሽኑ ተልዕኮውን ለመፈጸም በሚያደርገው እንቅስቃሴ የህዝብ ትብብር ያልተለየዉ ከመሆኑም በላይ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ደግሞ ከልዩ ልዩ ባለጉዳዮችና ከንግዱ ማህበረሰብ እንዲሁም ከተለያዩ መንግስታዊና ህዝባዊ አካላት በአንዳንድ የገቢዎችና ጉሙሩክ መስሪያ ቤት ሃላፊዎችና ሰራተኞች እንዲሁም በግል ንግድ በተሰማሩና ህገወጥ አካሄድን በሚያዘወትሩ ግለሰቦች ላይ የተለያዩ ጥቆማዎች ሲቀበል ቆይቷል፡፡Melaku Fanta - Director of Customs & Revenue Authority(Minister)

ኮሚሽኑ ከህዝብ የተቀበላቸውን ጥቆማዎች መሰረት በማድረግ ከብሄራዊ የመረጃ አገልግሎት ጋር በመተባበር በጥናት ተሰማርቶ ከቆየ በኃላ በተጠርጣሪዎች ላይ በቂ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን ለማሰባሰብ በመቻሉ ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት እስኪቀርብ ድረስ ተጠርጣሪዎቹ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዲቆዩ ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡

በዚህ መሰረት በዛሬው እለት ከፍርድ ቤት ህጋዊ የብርበራና የእስር ትእዛዝ በማውጣት አንደኛ አቶ መላኩ ፈንቴ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉሙሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር እንዲሁም አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉሙሩክ ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር የሚገኙባቸው 12 ያህል ተጠርጣሪዎች በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ስር ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል፡፡

የፌዴራል የስነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን በአዋጅ የተሰጠውን ስልጣን መነሻ በማድረግ ተጨማሪ ምርመራውን እንዳጠናቀቀ ህጋዊ ስርአቱን ተከትሎ ተጠርጣሪዎቹን ከነሙሉ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎቹ ለመደበኛው ፍርድ ቤት ያቀርባል፡፡

በዚህ አጋጣሚ ኮሚሽኑ ወደፊት በጉዳዩ ላይ እንዳስፈላጊነቱ ተጨማሪ ማብራሪያ እንደሚሰጥ እየገለፀ መላ የሃገራችን ህዝቦች መንግስት ሙስናን ለመታገልና በቁጥጥር ስር ለማዋል ለሚያደርገው የተቀደሰ ጥረት የተለመደ ትብብራቸውን በመስጠት እንዲቀጥሉ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

ግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም

አዲስ አበባ

*************

[Acknowledgments to Danielberhane’s Blog source who provides us this text]

Daniel Berhane

more recommended stories