የድርጅታችን የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ከታህሳስ 3 ቀን ጀምሮ ላለፉት 17 ቀናት አገራችን የምትገኝበትን ወቅታዊ ሁኔታ መነሻ በማድረግ ሰፊና ዝርዝር የሁኔታዎች ግምገማ አካሂዷል፡፡ ስራአስፈፃሚ ኮሚቴው በዚህ ስብሰባ ቀደም ሲል የተጀመረው የመታደስ ሂደትና የደረሰበትን ደረጃ እንዲሁምበአገራችን የሚታዩ የቆዩና ወቅታዊ ችግሮችን ከነዝርዘር መገለጫቸው በመለየት በመንስኤና መፍትሄዎቻቸው ላይ መክሮ የሃሳብ አንድነትና መተማመን ፈጥሯል፡፡ ችግሮቹን በመቅረፍ በእስካሁን ትግላችን የተመዘገቡ መልካም ውጤቶችን አስጠብቆ ለማስቀጠል የሚያስችል ቁርጠኝነትና ጠንካራ መግባባትን አረጋግጦ ወጥቷል፡፡
የተከበራችሁ የአገራችን ህዝቦች
ድርጅታችን ኢህአዴግ አገራችንን በለውጥ ጎዳና መምራት ከጀመረበት ከ1983 ዓ.ምጀምሮ በሁሉም የህይወት መስኮች መሰረታዊና ተስፋ ሰጭ ለውጥ ሲመዘገብ የቆየ ቢሆንም፣ ከቅርብ አመታት ወዲህ ደግሞ ለውጡን በተጀመረው ስፋትና ግለት ለማስቀጠል የሚደረገውን ጥረት የሚፈታተኑ ችግሮች እየታዩ መምጣታቸውን ይገነዘባል፡፡ አገራችን በአንድ በኩል በተከተልነው መሰረታዊና ትክክለኛ አቅጣጫ በተገኙ መልካም ውጤቶች እጅግ የሚያስጎመዥ ሁኔታ ላይ ትገኛለች፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በፈፀምናቸው ስህተቶችና ከእድገታችን ጋር ተያይዘው በተከሰቱ አዳዲስ ለውጦችና ፍላጎቶች ምክንያት ለጊዜውም ቢሆን በአሳሳቢ ወቅታዊ ችግሮች ተወጥራ የቆየችበት ሁኔታ መፈጠሩን የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በትኩረት ገምግሟል፡፡
ለሁሉም የአገራችን ህዝቦች ግልፅ እንደሚሆነው ለበርካታ ዘመናት በማሽቆልቆል ሂደት ውስጥ ለማለፍ የተገደደችው አገራችን ለ25 አመታት ቀና ብላ ስትጓዝ ቆይታለች፡፡ ይህምበሁሉም አገር ወዳድ ዜጎች የሚታመንበትና አለምም የመሰከረለት ነው፡፡ የኢኮኖሚ ውድቀትና ማሽቆለቆል ተገትቶ ለሩብ ምእተ አመት የዘለቀው አገራዊ እድገት ኢትዮጵያችን በትንሳኤ ጎዳና መገኘቷን አብስሯል፡፡ ህገመንግስታዊ ዴሞክራሲያችን የግልና የቡድን መብቶችን በማስከበር የሰላምና የእድገት መሰረት እንደሆነ በእነዚሁ አመታት ተረጋግጧል፡፡ ብዝሃነት የኢትዮጵያችን መሰረትና መገለጫ እንደሆነ በመቀበል ይህንንኑ በአግባቡ ለማስተዳዳር ያደረግነው ጥረት አገራችን ዜጎች ለረጅም አመታት በፍቅርና መከባበር የሚኖሩባት የሰላም አገር እንደሆነች አስመስክሯል፡፡
ይሁንና ይህ የሚያስጎመዥ እውነታ ከቅርብ አመታት ወዲህ በመታየት ላይ ባሉ ጊዜያዊ ችግሮች የተነሳ ለአደጋ እየተጋለጠና ለሁሉም ማህበረሰቦቻችን የስጋት ምንጭ መሆን በጀመረ አዲስ ክስተት መልክ የሚገለፅበት አዝማሚያ ሰፋ ብሎ ታይቷል፡፡ ከዚህ የተነሳም መላ የአገራችን ህዝቦችኢትዮጵያችንን ከገጠሟት ጊዜያዊ ችግሮች በማውጣት በትግላችን የተመዘገቡ ስኬኮችን ለመጠበቅና ለማስፋት፤ ድክመቶችንና አደጋዎችን ደግሞ በቁርጠኝነት ለማስተካከል የሚሹበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ መንግስትና የለውጡን ሂደት የሚመራው ድርጅታችንም ለዚህ የህዝብ ጥያቄ አስተማማኝ ምላሽ የሚሰጡበት ሁኔታ እንዲፈጠር አጥብቀው ሲጠይቁ ቆይተዋል፡፡
የኢህአዴግ ስራአስፈፃሚኮሚቴ ከሁለት ሳምንት በላይ ጊዜ ያካሄደው ግምገማ በዚህ የህዝባችን ልባዊ ፍላጎትና ቅን አገራዊ አስተሳሰብ ላይ የተመሰረተና ለዚሁም መላው ድርጅታዊ አቅሙን ተገዥ ለማድረግ በሚያስችል ቁርጠኝነት የተካሄደ ነው፡፡ በመሆኑም ስብሰባው በትናንተናው እለት በመላው የአገራችን ህዝቦች ከባድ ተጋድሎ የተመዘገቡ ስኬቶችን ለመጠበቅና ለማስፋት እንዲሁም ከምንም ነገር በላይ በአመራር ድክመት የተፈጠሩትን አደጋዎችና ስጋቶች ለመቅረፍ በሚያስችል ስምምነትና መግባባት ተጠናቋል፡፡
የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባለፉት አስራ ሰባት ቀናት ባደረገው ግምገማ በየደረጃው ባሉ የአመራር እርከኖች በተለይ ደግሞ በከፍተኛው አመራር ደረጃ የውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲ እጦት ስር እየሰደደ እንደመጣ አረጋግጧል፡፡ ይህም ሐሳብ በነፃነት የሚንሸራሸርባቸውን የመታገያ መድረኮች የሚገድብና የሚያጠብ ስለዚም ደግሞ በአመራሩ ውስጥ የአመለካከትና የተግባር አንድነትና ጥራት እንዳይፈጠር መሰናክል ሆኖ እንደቆየ ተመክልቷል፡፡ ይህ ችግር በዋነኛነት በድርጅታችን ከፍተኛ አመራር ደረጃ ከታየው የተዛባ የስልጣን አተያይና አጠቃቀም ጋር ተያይዞ የተከተሰተ ሲሆን ችግሩ የድርጅታችን አይነተኛ መለያ የሆነውን ዴሞክራስያዊነት በማዳካም ሳይወሰን ስልጣን የህዝብ መገልገያ እንዲሆን የጀመርነውን መልካም ጉዞ ለአደጋ ያጋለጠ ሆኖ ቆይቷል፡፡
ዴሞክራሲ እየጠበበ አድርባይነት በመስፋፋቱ ምክንያት በግልጽነትና በመርህ ላይ ተመስርቶ ከመተጋገል ይልቅ መርህ አልባ ግንኙትና አካሄድ ማስፈን የተለመደ ስልት ወደመሆን ተሸጋግሯል፡፡ ይህን የመሰለው በጠባብ ቡድናዊ ጥቅሞች ላይ የተመሰረተ መርህ አልባ ግንኙነት ኢህአዴግና አባል ድርጀቶቹን የማዳከም ውጤት አስከትሏል፡፡ ልማታዊ መንግስትታት በጠንካራ ዲስፒሊንና የሃሳብና የተግባር አንድነት የሚታወቁ ሆኖ እያለ ተገቢ ባልሆኑ ጥቅሞች ላይ የተመሰረቱት የቡድን ትስስሮች ልማታዊ መንግስታችንና ድርጅታችን ተልእኮአዋቸውን በብቃት እንዳይፈፅሙ ከፍተኛ መሰናክል ሆኖ እንደቆየ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው አረጋግጦአል፡፡
በሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴያችን ግምገማ መሰረት ማንኛውም መርህ አልባ ቡድናዊ ትስሰር ከምንም ነገር በፊትና በላይ እያንዳንዱን ብሄራዊ ድርጅትና በእሱም የሚራውን ህዝብ የሚጎዳ አደገኛ ጉደይ ነው፡፡ በመቀጠልም በግባራችን የሚመራውን የጋራ ትግልና አገራዊ የለውጥ ሂደቱን ለአደጋ የሚያገልጥ ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት ስራአስፈፃሚ ኮሚቴው በየትኛውም ክልል ሆነ ብሄራዋ ድርጅት የሚከሰቱ መርህ አልባ ጉድኝቶች በጥልቅ እየተፈተሹ ሊወገዱ እንደሚገባ ወስኗል፡፡
እንደሚታወቀው በአገራችን የሚገነባው ፌዴራላዊ ስርዓት መላ የአገራችን ብሄር ብሄረሰቦች ለዘመናት ያካሄዱት ትግል ውጤት ነው፡፡ አዲሲቱ ኢትዮጵያ ከየትኛውም ህብረብሄራዊ አገር የምትለየው በዝሃነትን በማወቅና በማክበር ነው፡፡ ለ25 አመታት የተገነባው ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የቋንቋ፣ የባህል፣ የታሪክ እኩልንተን አረጋግጦአለ፡፡ የአገራችን ብሄር ብሄረሰቦች ራሳቸውን በራሳቸው ካልሆነ በቀር በሌላ የማይተዳደሩበት ሁኔታ ፈጥሯል፡፡ በፊዴራላዊ አስተዳደራዊ ስርአታትን በእኩልነትና በመተሳሰብ የሚሳተፉበትን ሁኔታም አመቻችቷል፡፡ በዚህ የተነሳ ስርዓቱ ለበላይነትና የበታችነት የማይመች ሆኖ ተዋቅሯል፡፡ በተግባርም እኩልነት እንጂ የባላይነትም ሆነ የበታችነት የማይፈጠርበት ስርዓት ተገንብቷል፡፡ ይህንን መሰረታዊ መርሆ የሚነካ ማንኛውም ዝንባሌ የበላይነትን በዘላቂነት ሊፈጥር የማይችልና ከመኖቆር ውጭ ሌላ ውጤት የማያስገኝ እንደሚሆንም ይታመናል፡፡ ከዚህ በመነሳት ለሩብ ምእተ አመት በእኩልነትና በሰላም የዘለቀው ስርዓታችን የዚህ ውጤት እንደሆነ ስራ አስፈፃሚያችን በድጋሚ አረጋግጧል፡፡ በመሆኑም በማንኛውም ሽፋን ይህንን የእኩልነት ስርዓት ለማዳከም የሚደረግ ሙከራ ተቀባይነት እንደሌለውና ሊመከት እንደሚገባው ወስኗል፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በአንድ ወይም በሌላ ብሔር ህዝብና ድርጅት ስም እየማሉና እየተገዘቱ ጥገኛ ፍላጎታቸውን ለማርካት የሚንቀሳቀሱ ወገኖችን እንቅስቀሴ ማክሰም እንደሚገባ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ ሁሉም ብሔራዊ ድርጅቶች በሚያስተዳድሩት ክልል ውስጥ ያሉ ጥገኞችን ያለልዩነትና ማመንታት መታገል እንዳለባቸው ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
ሥራ አስፈፃሚው በድርጅታችን የዴሞክራሲ መጥበብ እዛው በዛው የውሳኔዎችን በታማንኝነትና በቁርጠኝነት የመፈፀም ዲሲፒሊንን እያላላ እንደመጣ አረጋግጦአል፡፡ በዚህ የተነሳ በድርጅትና በመንግስት ቋሚ መመሪያዎች በመገዛት መፈፀም የነበረባቸው ተግባራትና መሰጠት የነበረባቸው የእለት ተለት ውሳኔዎች እየቀሩ በብዙ የመንግስት መ/ቤቶች ህዝብ የሚጠብቃቸው አገልግሎቶች የማይሟሉበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡
በአጠቃላይ በድርጅታችን በተለይም ደግሞ በሥራ አስፈፃሚው ውስጥ የታየው የውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲ ችግር አደጋው በድርጅቱ ውስጥ ብቻ ታጥሮ የቀረ አልነበረም፡፡ የህዝብ መብትን በማክበርና ተገቢውን ህጋዊ አገልግሎት የመስጠት ግዴታን ባለመወጣት ጭምር የሚገለፅ ነበር፡፡ ከዚያም አልፎ ዴሞክራሲያችንን ማስፋትና ማጠናከር ሲገባ በተለያዩ መንገዶች የማጥበብ አዝማሚያም ተስተውሏል፡፡ ህገ መንግስታዊ ስርአታችን ልዩ ልዩ ጥቅሞችና ፍላጎቶች እንዲሁም በእነዚህ ላይ የተመሰረቱ ልዩነቶች በዴሞክራሲያዊ፣ ህጋዊና ሰላማዊ መንገድ እንዲስተናገዱ በቂና አስተማማኝ እድል ከፍቶ እያለ አመራራችን ዴሞክራሲውን የማስፋት ግዴታውን ባለመወጣቱ ችግሮችና ልዩነቶች በግጭት መንገድ የሚፈቱበት ሁነታ እንዲፈጠር አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ይህም ለሰላማችን መታወክ የበኩሉን አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡
ለመላው የአገራችን ህዝቦች ግልፅ እንደሚሆነው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በርከት ባሉ የአገራችን አካባቢዎች ሰላመና መረጋግት እየደፈረሰ ሁከት የለት ተለት ከሰተት እየሆነ መጥቷል፡፡ በክልሎችም ሆነ በክልሎች መካከል በልዩ ልዩ ሰበቦች የሚከተሰተው የሰላም መደፍረስ ለዜጎቻችን አሳዛኝ ሞት መበራከትና መቁሰል እንዲሁም ከባድ መፈናቀል ምክንያት ሆኗል፡፡ በተጨማሪም ከፍተኛ የንብረት ውድመትና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መገታት አስከትሏል፡፡ ይህ ለረጅም አመታት በሰላም በኖረችው አገር ውስጥ የስጋት መንፈስና ጭንቀት ፈጥሯል፡፡ ከበየቦታው እየተነሱ ያሉ ግጭቶች ከሰው ሞትና ከንብረት ውድመት በዘለለ የሃገራዊ ሕልውናችን ለአደጋና ሕዝባችንን ለጥፋት ቋፍ ያደረሱበት ሁኔታ ከመኖሩ በላይ ለውጭ ጥቃት ተጋላጭነታችንን የመጨመር ውጤት አስከትለዋል፡፡ ይህም በአጭር ቃል የመበልፀግ ተስፋና የሐገራዊ ሰላም መናጋት የተፋጠጡበት ሁኔታ ላይ እንደድንገኝ አድርጎናል፡፡ ከዚህ በመነሳት ስራአስፈፃሚ ኮሚቴያችን ህገመንግስታዊ ዴሞክራሲያችንን በታማኝነት ተግባራዊ ማድረግ ብቻ ሳይሆን መድረኩ የሚጠይቀውን ሁኔታ መነሻ በማድረግም ማስፋትና የግጭት መንስኤዎችን መቅረፍና የአገራችንን ሰላም ወደተለመደው አስተማማኝ ሁኔታ በአጭር ጊዜ መመለስ እንደሚገባ ወስኗል፡፡
በአገራችን የሚገነባው ህገመንግስትታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት በፍላትና ጥቅሞች ብዝሃነት ላይ የተመሰረት ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ በድርጅታችንና በመንግስት መሪነት ለ25 አመታት የቀጠለ ቢሆንም ከቅርብ አመታት ወዲህ የአስተሳሰብ ብዝሃነት በአግባቡ እንዲገለፅ የሚያደርግ ተጨባጭ ሁኔታ እየተዳከመ መጥቷል፡፡ ይህንን ችግር በጊዜና በአግባቡ ተገንዝቦ ማስተካከል የሚገባው ድርጅታችን ተገቢውን ህጋዊ እርምጃ በመውሰድ ረገድ ያሳየው ዳተኝነት የመድብለ ፓርቱ ስርግቱን ችግር እንዲገጥመዉ አድርጓል፡፡ የዴሞክራሲ ምህዳሩን የማስፋት ጉዳይ ምንም እንኳ በአዋጅና በድርጅታችን በጎ ፈቃድ ላይ ብቻ የሚመሰረት ባይሆንም በዚህ ረገድ ልንወስደው ይገባን የነበረውን ርምጃ ከመውሰድ አንፃር ሰፊ ክፍተት እንደነበር ሥራ አስፈፃሚው ይገነዘባል፡፡
ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሁነኛ ድርሻ ካላቸው ተቋማት መካከል የሃገራችን ሚዲያና ፕሬስ በሚገባው ደረጃ ነፃነታቸው ተጠብቆ የህዝብ ዓይንና ጆሮ ሆነው ያገለግሉ ዘንድ የተደረገው እንቅስቃሴ የሚፈለገውን ውጤት እንዳላመጣ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በግምገማው ተመልክቷል፡፡ በዚህ ረገድ የታየው ዘገምተኛ ዕድገት እንደተጠበቀ ሆኖ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በክልልም ይሁን በፌዴራል ያሉ የህዝብ የሚዲያ አውታሮች ሕግና ሥርዓትን ጠብቀው የማይሠሩበት ሁኔታ እያመዘነ የህዝቡን ሰላምና አብሮ የመኖር ገንቢ ባህል የሚሸረሽሩ ሰበካዎች የሚሰጥባቸው፣ ብሎም ህዝብን ከህዝብ ጋር የሚያጋጩ አጥፊ ቅስቀሳዎች የሚካሄድባቸው እየሆኑ ለመምጣታቸው የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚም ሆነ የሚመራው መንግሥት ድክመት አስተዋፅኦ እንዳደረገ ይቀበላል፡፡
አመራሩ ዴሞክራሲያዊ ህብረተሰብ በመገንባትና በህገመንግስታዊ ስርዓታችን ዙሪያ ብሔራዊ መግባባት መፍጠር እየተገባው የህዝብ የተደራጀ ሲቪል እንቅስቃሴ እንዳልተጠናከረ አረጋግጧል፡፡ በአገራችን ህገመንግስታዊ ዴሞክራሲ ዋስትና የሚኖረው ከአዋጅ አልፎ ህዝብ በተደራጀና ንቁ አኳኋን ሲሳተፍና ሲጠቀምበት ቢሆንም በዚህ ረገድ የተደረገው እንቅስቃሴ የሲቪል ማህበረሰቡን ተሳትፎ መሆን በሚገባው ደረጀ ከፍ ለማድረግ ያስቻለ እንዳልሆነ ተመልክቷል፡፡ በዚህ መሰረት በአገራችን የሚገነባው ዴሞከራሲያዊ ስርአት የሚታይበትን የሲቪል ማህበረብ ተሳትፎና ሁለገብ እንቅስቃሴ ገደብ ከጣሉበት ችግሮች በማላቀቅ ማጠናከር እንደሚባ ታምኖበታል፡፡ አመራሩ የዴሞክራቲክ ተቋማት ግንባታና የህዝብ የተደራጀ ተሳትፎ የሞት የሽረት ጉዳይ እንደሆነ ተገንዘቦ ባለመንቀሳቀሱ የተፈጠረውን መሰረታዊ ጉድለት ለመፍታት ልዩ ትኩረት መስጠት እንደሚገባም መግባባት ላይ ተደርሷል፡፡
ልክ እንደዴሞክራሱው ሁሉ በአገራችን የህልውና ጥያቄ የሆነውን መልካም አስተዳደርን የማስፈን እንቅስቃሴያችን በአመራር ድክመት ምከነያት ለበረካታ ችግሮች እንደተጋለጠ ስራ አስፈፃሚኮማቴው አረጋግጧል፡፡ በዚህ ረገድ የህዝቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማስፋት፣ የህግ የበላይነትን ለማደረጋገጥ፣ የግልፅነትና የተጠያቂነት አሰራርን ለማንገስና ውጤታማና ቀልጣፋ አስተዳዳር ለመገንባት የተደረጉ ጠረቶች ያስገኙትንን መልካም ፍሬ መጠበቅና ማስፋት አዳጋች ሆኖ ቆይቷል፡፡ በየደረጃው የመኑ የመንግስት አስፈፃሚ አካላት በቅን ልቦናና መንግስታዊ መመሪያዎችን በተከተለ አኳኋን ህዝቡን የሚያገለግሉና ተሳትፎና ተጠከሚነቱን የሚያረጋግጡበት እድል ቀንሷል፡፡ በዚህ የተነሳ ከፍተኛ የህዝብ ምሬት ተፈጥሯል፡፡ ስራ አስፈፃሚው ይህ ችግር ከምንም ነገር በላይ በከፍተኛው አመራር ደረጃ በሚታይ ጉድለት ምክንያት የተፈጠረና የተባበሰ እንደሆነ አረጋግጧል፡፡ የህግ የበላይነት የማስፈን ድክመት በመታየቱ በሙስናም ሆነ በሌሎች ጥፋቶች ውስጥ የተዘፈቁ ግለሰቦችን በወቅቱና ህጋዊና አስተማሪ በሆነ መንገድ መጠየቅ ሳየቻል ቆየቷል፡፡ ዜገች በህገመንግስቱ ዋስትና ያገኙ መብቶቻቸው የሚጥሱ ሰዎችን በህግ ተጠያቂ ማድረግ መሆን በሚገባው ደረጃ ሳይፈፀም ቆይቷል፡፡
በተጨማሪም መንግስት የህዝብና የአገር ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በነደፋቸው ፕሮጄክቶት ዙሪያ የሚታዩ የአፈፅፀምና የስነምግባር ችግሮችን አስተማማኝና ውጤታማ በሆነ መንገድ የማረምና የማስተካከል ጉድለት ታይቷል፡፡ በዚህ የተነሳ አገራችንን በሁሉም መስክ ተወዳዳሪ ሊያደርጉ የህዝባችንን ተጠቃሚነት ሊያሰፉ የሚችሉ ፕሮጄክቶች፣ የጊዜ የዋጋ ንረትና የሃብት ብክነት የሚታይባቸው ሆነዋል፡፡ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው እነዚህ የመልካም አስተዳዳር ችግሮች ህዝብና አገርን ያልተገባ ዋጋ የሚያስከፍሉ እንደሆኑ በመገንዘብ በአፋጣኝ እንደስተካከሉ ማድረግ እንደሚገባ አምኖበታል፡፡ በዚህ ረገድ ይህንን የመልካም አስተዳደር ችግር በተግባር ማቃለል ሲገባ ባጉል ተስፋና በባዶ ቃልኪዳን የመሸንገል ህዝበኛ አዝማሚያዎች በጥብቅ መመከት እንዳለባቸው ወስኗል፡፡
ድርጅታችን የሁሉም ህዝቦች እኩልነት በተከበረባት አገራችን አንድ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማህበረሰብ የመገንባትን መርህ ተክትሎ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡ በተጨባጭም አገራችንን ከመበታተንቋፍ አውጥቶ አዲስ አይነት ዴሞክራሲያዊ አንድነትና የእኩልነት ትስስር በመገንባት ረጅም ርቀት ተጉዟል፡፡ ይህ በአገር አቋራጭ የመሰረተ ልማት አውታሮች የማይበጠስ ትስስር እንዲፈጠር አድርጓል፡፡ ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በሃገራችን በየደረጃው እየተካሄዱ ያሉና ሊካሄዱም የሚገባቸው የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቶች የድርጅታችን ሃገራዊ ራዕይና የፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችንን በሚያጠናክር መልክ በማስኬድ ረገድ ቁጥራቸው የማይናቅ ጉድለቶች በአመራሩ ተፈጽመዋል፡፡
በአጭሩ በህብረተሰባችን ዘንድ ህገመንግሥታዊ ሥርዓቱን፣ ልማታዊ አስተሳሰብና፣ በብዝሃነት ላይ የተመሠረተ ኢትዮጵያዊ አንድነት በማጠናከር ረገድ የተሰራው ስራ መሆን የሚችለውን ያህል ውጤት ሳያመጣ እንደቀረ ሥራ አስፈፃሚው ባደረገው ግምገማ ማረጋገጥ ችሏል፡፡ በዚህ የተነሳ ብሄረሰባዊና አገራዊ ማንነትን አስተሳስሮ በመገንባት በኩል የታየውን ጉድለት በአፋጣኝና በአስተማማኝ መንገድ መፍታት እንደሚኖርብን ታምኖበታል፡፡
ከላይ የተገለፁት ችግሮችና በተራዘመ ትግል የተገነባችውን አገር ለአደጋ ማጋለጥ የጀመሩት ጉድለቶች በዋነኛነት የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራር በተለይም የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ድክመቶች ናቸው፡፡ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላቱና የድርጅትና የመንግስት ከፍተኛ ሃላፊዎች በተናጠልና በጋራ፣ ስትራተጅያዊና ታክቲካዊ አመራር የመስጠት ሃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው የተፈጠረ ችግር ነው፡፡ በዚህ ግምገማ የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴና የመንግስት የበላይ አመራሮች ወቅቱ የሚጠይቀውን ስትራቴጂያዊ አመራር የመስጠት ጉድለታቸው ሰፊ እንደሆነ ታይቷል፡፡ ከፍተኛ አመራሩ ችግር አስቀድሞ የመለየት፣ ተንትኖ የማወቅ፣ የመፍቻ መንገዶች የመተለምና በዚሁ መሠረት የመፍታት ብቃቱ ወቅቱና መድረኩ ከሚጠይቀው ደረጃ ጋር አብሮ ባለማደጉ የተወሳሰበውን አገራዊ መድረክ በብቃት የመምራት ጉድለት እንደነበረበት የጋራ አቋም ተይዟል፡፡
በመሆኑም ለተፈፀመው ስህተትና ለደረሰው ጉዳት ከፍተኛ አመራሩ ሃላፊነቱን እንደሚወስድ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
ከዚህ በመነሳት ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው መላ የአገራችን ህዝቦች በከባድ ተጋድሎአቸው ያስመዘገቡዋቸውን ድሎች ጠብቆና አስፍቶ ለማስቀጠል ባለመቻሉ፤ እንዲሁም በድርጅታችን ውስጥም ሆነ በአገራችን ውስጥ የሚታዩ ልዩ ልዩ ችግሮችን በጊዜና በከፍተኛ የሃላፊነት መንፈስ ለመፍታት ባለመቻሉ ለደረሰው ጉዳት ሙሉ ሃላፊነቱን ከመውሰድ በተጨማሪ ለመላ የአገራችን ህዝቦችና የድርጅታችን አባላትና ደጋፊዎችን ልባዊ ይቅርታ ይጠይቃል፡፡ ድርጅታችን ኢህአዴግ የትግልና የለውጥ ድርጅት ብቻ ሳይሆን ለዘመናት በማሽቆልቆል ውስጥ የቆየችውን አገር ለሩብ ምእተ አመት በእድገትና የለውጥ ጎዳና እንድትገሰግስ ያደረገውን ጥረትና የተመዘገቡትን ህዝባዊ ድሎች ለአደጋ የሚያጋልጥ ሁኔታ እንዲፈጠር በማድረጉም የተሰማውን ከልብ የመነጨ ፀፀት ይገልፃል፡፡ ይህ ሁኔታ እንዳይደገምም እንዳለፉት አመታት ሁሉ በቁርጠኝትና በፅናት እንደሚንቀሳቀስ ቃል ኪዳኑን ያድሳል፡፡ ለማናቸውም ፈተና ሳይንበረከክ ከድል ላይ ድል በማስመዝገብ የመጓዝ እንቁ ታሪክ ያለው ድርጅታችን ኢህአዴግ አሁን በአገራችን የሚታየውን ሁኔታ እንደሚያስተካከልና የድል ጉዞውን እንደሚያስቀጥልም ቃል ይገባል፡፡
የተከበራችሁ የአገራችን ህዝቦች
የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ከላይ በተገለፀው ግምገማና መግባባት ላይ በመመስረት ከዚህ የሚከተሉትን አቅጣጫዎች ላይ ትኩረት ሰጥቶ በመንቀሳቀስ አጣዳፊ ችግሮችን እየፈታ ለዘላቂ ለውጥ መስራት እንዳለበት ወስኗል፡፡
1. ባለፉት 17 ቀናት ባካሄደው ግምገማ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው የሕዝባችንን የዴሞክራሲና የልማት እንቅስቃሴ በማጎልበት ተሳትፎና ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥና ለማስፋት፤ አስተማማኝ ሰላም ባጠረ ጊዜ ማረጋገጥና ሕዝባችን ወደተረጋጋ ኑሮው እንዲመለስ ማድረግ እንደሚገባ በአጽንኦት ወስኗል፡፡ በዚህም መሠረት የሕዝባችንን ሰላማዊ ኑሮ የሚያውኩ ማንኛውም እንቅስቃሴዎች ከህዝብ ጋር በመሆን በቁጥጥር ስር ለማዋል መንግሥት ሙሉ ሃላፊነት ወስዶ እንዲያስፈፅም ተወስኗል፡፡ የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥ ጉዳይ ላፍታም ቢሆን ጥያቄ ውስጥ ሊገባ እንደማይገባውና በዚህ ረገድ የሚታዩ የህግ ጥሰቶችን በመቆጣጠር ህግና ሰላምን በአስተማማኝ ደረጃ ማስፈን እንዳለበት ተወስኗል፡፡ በየአካባቢው በሕገወጥ መንገድ የሚደረጉ መንገድ የመዝጋት፣ የዜጎችን በነፃ የመንቀሳቀስ መብት የማወክ እንዲሁም የሕዝቡን የእለትተለት እንቅስቃሴ የሚያስተጓጉሉ የቡድንም የተናጠልም እንቅስቃሴዎች እንዲቆሙ ይደረጋል፡፡ በወሰንም ሆነ በሌሎች ምክንያቶች የሚያጋጥመውን ሞትና መፈናቀል ሙሉ በሙሉ ለማስቆም ወስኗል፡፡ በቅርቡ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል መካከል ባሉአዋሳኝ አካባቢዎች ባጋጠሙ ግጭቶች ሳቢያ የተፈጠረው የዜጎች ሞትና እንግልት እንዲሁም የመቶ ሺዎች መፈናቀል በአስቸኳይ ተገቶ ተፈናቃዮች መደበኛ ህይወታቸውን በተረጋጋ መንገድ የሚመሩበት ሁኔታ ባስቸኳይ ለማመቻቸት ወስኗል፡፡ በተጨማሪም በእነዚህ አካባቢዎች ለግጭት መንስኤ የሆኑ የሕገ ወጥ ንግድ እንቅስቃሴዎች እንዲቆሙ፤ አርሶአደሮችና አርብቶ አደሮች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴያቸው ለአደጋ እንዳይጋለጥ አስፈላጊው ጥበቃና ድጋፍ እንዲደረግ ወስኗል፡፡ በዚህ አጋጣሚ የአገራችን የመከላከያ ሰራዊትና የፀጥታ አካላት በአስቸጋሪ ሁኔታ ሰላማችንን ለማስከበር ለከፈሉት መስዋእትነት የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ያለውን አክብሮት ይገልፃል።
2. ከውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲ አኳያ አሁን የተጀመረውን ግምገማ መሠረት በማድረግና የትራንስፎርሜሽን አጀንዳችንን በውጤት ለማስፈፀም እያንዳንዱ ብሔራዊ ድርጅት በከፍተኛ አመራር ደረጃ የሚታይበትን ድክመት በጥልቀት ገምግሞ በግልጽነትና በተጠያቂነት ላይ የተመሰረተ የማስተካከያና የእርምት ርምጃ እንዲወስድ ወስኗል፡፡
3. ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓታችን እኩልነትንና ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ መሠረታዊ ጥያቄዎችን የመለሰ ቢሆንም ከአፈፃፀም ድክመት ጋር በተያያዘ ከቦታ ቦታ የሚታዩ የልማት አቅርቦት ልዩነቶች እንዳሉ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ገምግሟል፡፡ በድህነት ላይ ያስመዘገብናቸው ድሎች እንደተጠበቁ ሆነው አሁንም ቢሆን ወደ ሩብ የሚጠጋው ሕዝባችን ከድህነት ወለል በታች መገኘቱ መሆኑ እጅግ አሳሳቢ እመሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት በዚህ ረገድ ትግላችን ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው በአጽንኦት ተገልጿል፡፡ የፌዴራል የልማት ፕሮጀክቶች ሚና እንደተጠበቀ ሆኖ በስርዓታችን ውስጥ ያለው ትልቁ የልማት አቅም በክልሎች የሚገኘ እንደሆነና ክልሎችን የሚያስተዳድሩ ብሄራዊ ድርጅቶች የየክልላቸውን የልማት አቅም አሟጠው የሚጠቀሙበትን ሁኔታ መፍጠር እንዳለባቸው ሥራ አስፈፃሚው በአጽንኦት አስምሮበታል፡፡ በተጨማሪም ሃገራዊ አንድነትን ለማጠናከር የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ እንቅስቃሴዎችን ከህዝብና ከመንግሥት ጋር በመሆን ማከናወን እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
4. የመንግሥት መዋቅሩ ለህዝብ ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ መስጠት እንዲችል ለማድረግ የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎችን ውጤታማ ለማድረግና መስተካከል ያለባቸው አቅጣጫዎች እንደገና ከህዝባችንና ከፈፃሚ አካላት ጋር በመሆን ተከልሰው ሙሉ ትግበራ ውስጥ እንዲገባ ተወስኗል፡፡ በዚህ አጋጣሚ በፌደራልም በክልልም ያለው ሲቪል ሰርቪስ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የአገልጋይነት መንፈስ የሕዝቡን ጥያቄዎች ለመመለስ እንዲረባረብ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
5. በአገራችን የተመዘገቡት ስኬቶች ዋነኛ ሚስጢር የሕዝብን ተሣትፎማረጋገጥ መቻሉ ነው፡፡ በዚህም መሰረት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው የህዝብን አመኔታ መልሶ ለማግኘትና ለህዝብ ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ ተከታታይ እርምጃዎችን መውሰድ እንደሚገባ ወስኗል፡፡ ሕዝብ የሚደመጥበትና ወሳኝነቱ በሚገባ የሚረጋገጥበት እድል እንዲሰፋ አፅንኦት ሰጥቶታል፡፡ በተለይ ደግሞ ወጣቶቻችን የሚያነሱዋቸውን ጥያቄዎች በሚገባ ለመመለስና በዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታና በልማት ሊኖራቸው የሚገባውን ተሣትፎ በተሟላ መልኩ ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተከታታይ ሥራዎች እንዲሰሩ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፡፡
6. በመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ላይ የሚታዩ ጉድለቶችን ከሁሉም ተቃዋሚ ድርጅቶችና ከህዝቡ ጋር በመሆን ለመቅረፍ መንቀሳቀስ እንደሚገባ ወስኗል፡፡ ምሁራንና የሲቪክ ማህበረሰቦች ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታና የዴሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋት ተገቢ ሚናቸውን የሚጫወቱበት ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠር ወስኗል፡፡
7. ህገመንግስታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓታችን ያስከበራቸውን ሰብአዊና ዴሞከራሲያዊ መብቶች የመጣስ አዝማሚያዎችና ተግባራት በጥብቅ እንዲመከቱ ወስኗል፡፡ በዚህ ረገድ የህዝብን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች በአስተማማኝ ደረጃ ለማስከበር ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸው ተጨማሪ ርምጃዎች እንዲወሰዱም አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
8. በልማትና በሃገራዊ አንድነት ዙሪያ መትጋት ሲኖርባቸው ሕዝብን ከህዝብ ጋር በሚያራርቅ አፍራሽ ተግባር ውስጥ የተሰማሩ የግልና የመንግሥት የሚዲያ ተቋማት አካሄዳቸውን የሚያስተካክሉበት ሁኔታ ለመፍጠር እንደሚንቀሳቀስ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው የወሰነ ሲሆን በተለይም በክልልም ሆነ በፌዴራል ደረጃ ከፖለቲካዊ፣ ከሕጋዊ አሠራርና ከሕገመንግሥታዊ ሥርዓት በራቀ መልኩ የሁከትና የግርግር መልእክት በህዝብ ሚዲያ የሚሰበክበትን እድል ለመዝጋት የሚያስችሉ የተቀናጁ እርምጃዎችን እንደሚወስድ በዚህ አጋጣሚ ይገልፃል፡፡
የተከበራችሁ የአገራችን ህዝቦች፣ ምሁራን፤ የድርጅታችን አባላትና ደጋፊዎች፣ አጋር ድርጅቶች እንዲሁም የፀጥታና የህግ አስከባሪ አካላት
ድርጅታችን ኢህአዴግ ለአለፉት 26 አመታት በእናንተ በመተማመንና ከእናንተ ጋር እጅ በእጅ በመተሳሰር ለመብታችሁና ጥቅማችሁ መከበር የምትበቁባት አገር መገንባት ጀምረናል፡፡ በዚህ ሂደት የከፈልነው መስዋእትነት ከባድ እንደነበረው ሁሉ ከሩብ ምአተ አመታት በላይ የዘለቀ ለውጥ ለማስመዝገብ ችለናል፡፡ ምንም እንኳ በዚህ አጭር ጊዜ ሁሉም ችግሮቻወትን ተሟልተው ይቀረፋሉ ተብሎ መጠበቅ ባይቻልም በተመሳሳይ የእድገት ደረጃ ከሚኙ አገሮች በላቀ ፍጥነት ተጉዘን አገራዊ ትንሳኤያችንን ማረጋገጥ ጀምረናል፡፡ የአገራችን የወደፊት እድል የሚወሰነው የጀመርነውን የህዳሴ ጉዞ ጠብቀን ድሎቻችንን በማስፋትና ድክመቶቻችንን አርመን ዳር ለማድረስ ስንችል ብቻ ነው፡፡ በመሆኑም የአጋጠሙንን ጊዜያዊ መሰናክሎች ሁሉ በፅናት ተፋልመን ዴሞክራሲያዊና ልማታዊ ድሎቻችንን ለማስፋት የተለመደ ድጋፋችሁና ወሳኝ እንቅስቃሴያችሁ እንዳይለየን፤ በአጠፋንበት እያረማችሁ፣ በአጎደልንበት እየሞላችሁ አገራችንን ተባብረን እንድንገነባ የኢህዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ
*******
ኢህአዴግ ምን እያለ ነው?!
መስከረም አበራ Democracy ጥር 8, 2018 0 Minutes
Ethiopian Think Thank Group
የኢትዮጵያ ህዝብ በከፍተኛ የለውጥ ፍላጎት ውስጥ መሆኑ ያፈጠጠ ሃቅ ነው፡፡ የለውጥ አምሮቱ የሚንጠው የሃገራችን ፖለቲካ ከዲሞክራሲ ባነሰ ነገር እንደ ማይረጋጋ ሸርተት የማይል ሃቅ ሆኖ ሳለ ይለወጥ ዘንድ የተፈለገውን ስርዓት የሚጋልበው ህወሃት መራሹ ኢህአዴግ ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርግ፣ከቅን ልቦና የመነጨ ለውጥ ለማምጣት ተፈጥሮውም፣አቅሙም፣ ፍላጎቱም፣ጆሮውም አለው ወይ የሚለው ወሳኝ ነጥብ ነው፡፡ህወሃት የቤቱን ራስ አቶ መለስን ካጣ በኋላ እንደተዳከመ እሙን ቢሆንም ከማንም በላይ የሃገራችንን የወደፊት እጣፋንታ በመወሰኑ በኩል አሁንም የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ እሙን ነው፡፡ በሃገራችን ኢኮኖሚ፣ ፖለቲካ፣ ውትርናም መስክ ክቡድ ህልውና ያለው ህወሃት ከስልጣኑ አሻግሮ የሃገርን እጣፋንታ በጎ የማድረጊያውን የተሻለ መንገድ የማየት አርቆ አሳቢነት እንዳለው የሚያሳይ ሪኮርድ የለውም፡፡ይልቅስ በማንኛውም መስዕዋትነት ስልጣኑን ማዳን፣በየትኛውም ኪሳራ የበላይነቱን ማረጋገጥ፣ እንደምንም ብሎ የጎሳውን ዘመን ተሻጋሪ ገዥ/ነጅነት ለማረጋገጥ በመፋተር ነው የምናውቀው፡፡
ንፁሃንን ከእስር መፍታት ግዴታ ነው ደግነት?!
ኢህአዴግ ከሰሞኑ ለሃገራዊ መግባባት ስል የተቃውሞ ፖለቲካ ፓርቲ አመራር የሆኑ እስረኞችን ሁሉ እፈታለሁ እያለ ነው፡፡ይህ ውሳኔው በጣም የሚያስደስት ቢሆንም ቅንነት አጥብቆ ከራቀው ህወሃት መራሹ ግንባር የወጣ ነውና ልናየው ሚገባው በጥንቃቄ መሆን አለበት፡፡ እስረኞቹ እስርቤት የሚማቅቁት ቀለላል የሆነውን ለራስ የኖር ዘይቤ ንቀው ብፁዕ እና ከባድ የሆነውን ለሌሎች የመኖርን መልካም ዕጣ ስለመረጡ ነው፡፡ኢህአዴግ አንዴ አሸባሪ ሌላ ጊዜ ፀረ-ሰላም እያለ እንደ ተራ ወንበዴ የሚያበሻቅጣቸው ሰዎች የኢትዮጵያ ህዝብ ከተዘፈቀበት መከራ መውጫ የተስፋ ጭላንጭል አድርጎ የሚያስባቸው ባለብሩህ አዕምሮዎች ናቸውና እስራቸው እስሩ ነው፡፡በበኩሌ እነዚህን የፖለቲካ እስረኞች ባሰብኩ ቁጥር ከባድ የባለ ዕዳነት ስሜት ይሰማኛል፡፡
ኢህአዴግ እነዚህን ሰዎች ሲያስር ሚሊዮኖችን አብሮ እንዳሰረ፣በሚሊኖች ልብ ውስጥ ክፉ ጥላቻን እየተጠላ እንደሆነ የሚያስብ አይመስለኝም፡፡ እንደውም በተቃራኒው ጉብዝናውን የሚለካው አስሮ በገረፈው ሰው ብዛት ይመስላል፡፡ ደደቢት በረሃ ኖሮ፣ጉና ተራራ ሰንብቶ የመጣ፣ጉብዝናውን በጣለው የወንድሙ ሬሳ ብዛት የሚመዝን፣ጀግንነቱን ባጠነው የባሩድ ሽታ የሚወስን እግረኛ ቀን ቀንቶት ስልጣን ላይ ሲወጣ ያንኑ የጦር ሜዳ የቆረጣ ስነልቦናውን ሊተው አይችልምና በየእስርቤቶቹ የሚያደርገው አውሬያዊ ባህሪ ከለመደው ግዳይ መጣል ጋር ያመሳስለዋል፡፡እናም የቀን ጎዶሎ በክፉ እጁ ላይ የጣላቸውን የህሊና እስረኞች በማይሞላው እስርቤቱ አጉሮ አሳር መከራ ያሳያል፡፡ ማሰባቸው ብቻ ወንጀል ሆኖባቸው የሲኦል ኑሮ መኖራቸው ሳያንስ በደጋፊዎቻቸው እንኳን እንዳይጠየቁ፣ታመው እንዳይታከሙ አድርጎ ‘ጎበዝነቱን’ በክፉነቱ ሲለካ ኖሯል፡፡ እድሜ እየተለመነላቸው ለሃገራቸው ሊሰሩ የሚገባቸውን ሰዎች እስርቤት አጉሮ ምጡቅ አዕምሯቸውን ቦአዝኖ፣ኩሩ ማንነታቸውን አሸማቆ፣ቅስማቸውን ሰብሮ፣ከሰውነት ጎዳና አውጥቶ በምትኩ ሃገርን ለጥራዝ ነጠቅ ካድሬ አስረክቦ ማላገጫ ማድረጉ ለይቅርታ የሚያዳግት የህወሃት/ኢህአዴግ ከተራራ የገዘፈ ጥፋት ነው፡፡
ይህ የሃገርን እርምጃ የማዘግየት ትልቅ ውድመት ድሮም መታሰር የሌለባቸውን ሰዎች በመፍታት ብቻ የሚስተሰረይ ሃጥያት ነው ብሎ ማሰብ የሞኝ ብልጠት ነው፡፡ ንፁሃንን ማሰሩ ራሱ ወንጀል መሆኑ የማያጠያይቅ ስለሆነ እስረኞቹን ከማይገባቸው የሲኦል ኑሮ መፍታቱ በትክክለኛው የፍትህ መንገድ ከታሰበ የመንግስት ግዴታ እንጅ እጅግም አጀብ የሚያስብል የደግነት መገለጫ አይደለም፡፡ማንም የማይጠይቀው አፄ በጉልበቱ ሆኖ ከመኖሩ የተነሳ ሳያጠፉ የታሰሩ የሃገር ሃብቶችን በእስርቤት ሲያሰቃይ ከርሞ ሲፈታልንም ስንደሰት ኖረናልና የዛሬው የእስረኛ እፈታለሁ የኢህአዴግ አዋጅ ከደስታ በላይ እንደሚያስደስተን የታወቀ ነው፡፡
ሆኖም ከደስታችን ስሜታዊነት ስንመለስ እነዚህ ሰዎች በእስር ያጡትን ነገር ከእስር መፈታት ብቻ እንደማይመልስላቸው እርግጥ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡በእስርቤት የባከነን የጉብዝና ወራት የሚመልሰው ማን ነው? ከገራፊ እጅ ከሚወርደው የዱላ መዓት እኩል ካልተገራ አፍ የሚዘንበውን ቅስም ሰባሪ ስድብ ከዕለታት አንድ ቀን ከእስር መፈታት ይክሰዋል?የልጅን ናፍቆት የቤተሰብን ርሃብ መካሻው ምንድን ነው? ይህ ሁሉ መከራ ሲወርድበት የኖረ ሰው ሃገሩን ሲወድ ከነበረው ውድ እጥፍ ጥላቻ ጠልቶ ከእስር ቢወጣ የሚጠቀመው ማን ነው? ለዚህ ሁሉ መንስዔ የሆነው አስሮ የማይጠግበው መንግስት ታዲያ እስረኛ ስለፈታሁ ይህ ለመለወጤ ምልክት ይሁናችሁና ተነስታችሁ አመስግኑኝ እያለ ነው፡፡ ለዚሁም ማን ተፈትቶ ማን ይቅር የሚለው ገና ጌቶችን እያወዛገበ እንደሆነ ነው የሚወራው፡፡
የመብት ተሟጋቾችን አስሮ ማሰቃየቱ የኢትዮጵያ ህዝብ በኢህአዴግ ላይ ካቄመባቸው ብዙ ጥፋቶቹ አንዱ እና ዋነኛው ነው እንጅ ብቸኛው አይደለም፡፡ ስለዚህ እስረኞችን እፈታለሁ ማለቱ አንድ በጎ ነገር ሆኖ ይወሰድ ይሆናል እንጅ የሥራ ሁሉ ፍፃሜ ነው ማለት አይደለም፡፡ኢህአዴግ ሲያጠፋ የኖረው ብዙ ስለሆነ ያለጥፋታቸው የታሰሩ እስረኞችን ከመልቀቁ ባሻገር ሊያርመው የሚገባው የትየለሌ ስህተት አለው፡፡
በሽፍታ ጭካኔ እንጅ በመንግስት ርህራሄ እና ምህረት የማናውቀው ኢህአዴግ ብድግ ብሎ እስረኛ እፈታለሁ ያለበት አካሄድ አላማ ግብ ራሱ በጥልቅ መጤን አለበት፡፡ በሃገራችን የፖለቲካ እስረኛ የለም ሲል የኖረው ገዥው ግንባር ዛሬ ብድግ ብሎ እፈታቸዋለሁ ያላቸውን የፖለቲካ እስረኞች የሚጠራበት ስም አጥቶ “የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች” ይል ይዟል፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የሚል ስም የተሰጣቸው ሰዎች ከፖለቲካ በቀር የምን እስረኞች ሊባሉ ነው?ደግሞስ መንግስት ሃሳባቸው ከሃሳቡ ጋር ስላልገጠመ ብቻ ያሰራቸው የተቃውሞ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን ብቻ ነው?ከሆነ እስክንድር ነጋ የየትኛው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ተብሎ ነው የታሰረው? ይሄ ሁሉ መንተፋተፍ ቀድሞ የፖለቲካ እስረኞች በግዛቴ የሉም ሲባል የተኖረውን ለማስተባበል ታስቦ ነው፡፡ነገሩ ግን ከንቱ ድካም ነው፡፡የሚያመላክተውም የኢህአዴግን ከአፈርኩ አይመልሰኝ ገታራነት ዳርቻ፣ስህተቱን ከሚያምን ፍርጥ ብሎ መሞትን የሚመርጥ፣በመለወጡ ተስፋ የማያደርጉበት ድርጅት መሆኑን ነው፡፡ ይህ እና ሌሎች በኢህአዴግ አባል ፓርቲ ሊቀመንበሮች በተሰጠው መግለጫ ላይ የተሰገሰጉ የማድበስበስ፣ማስቀየስ፣መካድ እና ሃቅን የመሸሽ ሁኔታዎችን ስናስተውል ፓርቲው እስረኞችን እፈታለሁ የማለቱ እርምጃ ራሱ ኢህአዴግ እንደሚያወራው ለሃገራዊ መግባባት ሲል ያደረገው ከራሱ የመነጨ፣የፍፁም መለወጡ ምልክት ነው ብሎ ለመቀበል ያስቸግራል፡፡
መግለጫው ሲገለጥ
ኢህአዴግ የቀድሞው ተሃድሶየ ጥልቀት ስለጎደለው ተመሼ ወደ አዘቅት ወርጃለሁና ሌላ ግምገማ ያስፈልገኛል ብሎ ለሃያ የተጠጋ ቀን እንደ ኑዛዜ የሚቃጣው ግምገማ አድርጓ ተመልሷል፡፡ ግንባሩን ለአስቸኳይ ሂስ ቀመስ ስብሰባ ያበቃው በአሁኑ ወቅት ሃገራችን ያለችበት አስፈሪ ፖለቲካዊ ቀውስ እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ይህ ቀውስ የታየው ደግሞ አራቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በሚያስተዳድሯቸው ክልሎች ብቻ አይደለም፡፡እንደውም ከፍተኛ ቀውስ ላስከተለው የኦሮሞ ህዝቦች ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል መፈናቀል ስረ-ምክንያቱ አጋር ፓርቲ በሆነው ኢሶህዴፓ አስተደደር ነው፡፡ነገር ግን ኢሶህዴፓ በሰሞኑ የኢህአዴግ የስራ አስፈፃሚ ስብሰባ አልተካፈለም፤ለማብራሪያም አልተገኘም፡፡ በተመሳሳይ አማሮች በገጀራ እየተመተሩ የተጣሉበትን ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልን የሚያስተዳድረው ቤጉዴፓም የስብሰባውም ሆነ የመግለጫው አካል አይደሉም፡፡ይህ ከኢህአዴግ የአባል እና አጋር ድርጅቶች ሚስጥራዊ ተፈጥሮ እና ግንኙነት የሚመነጭ እንቆቅልሻዊነት አጋር ድርጅቶች ምን አይነት አካላት እንደሆኑ ይበልጥ እንድንጠይቅ የሚያስገድድ ነው፡፡ ከግማሽ ሚሊዮን ህዝብ በላይ እንዲፈናቀል፣ክቡር የሰውልጅ በአሰቃቂ ሁኔታ በገጀራ እንዲመተር ያደረገን አመራር የግምገማው አካል ያላደረገ የተለውጠናል አዋጅ ለማን ትርጉም ይሰጣል ተብሎ እንደሚወራ ግራ ነው፡፡
እንዲህ አንዱን ጥሎ ሌላውን አንጠልጥሎ የተሰየመው ስብሰባ እንደ ተቋጨ ለየት ያለ ከፍተኛ ፖለቲካዊ ውሳኔ የተላለፈበት እንደሆነ ኢህአዴግ በፀሃፊው በአቶ ሽፈራው ሽጉጤ በኩል አስነገረ፡፡ይህም መግለጫው በጉጉት እንዲጠበቅ አደረገ፡፡ ከዚሁ ግምገማ መልስ ረዘም ያለ መግለጫ ማውጣቱ የማይበቃ ሆኖ የግንባሩ እህት ድርጅቶች ከረዥሙ መግለጫ የረዘመ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ሆኖም የግምገማው መግለጫም ሆነ የእህት ድርጅቶ ማብራሪያ የተጠበቀውን ያህል የኢህአዴግን መለወጥ የሚያመልክት ሆኖ አልተገኘም፡፡ይልቅስ የተለመደው ማድበስበስ፣ አድማጭን ቂል አድርጎ የማየት የሞኝ ብልጠት እና ጭልጥ ያለ ክህደት የታየበት ነው፡፡
ማስቀየስ
በመግለጫውም ሆነ የኢህአዴግ እህት ፓርቲዎች ነን ብለው በቀረቡት የፓርቲ ሊቀመንበሮች የተሰጠው ማብራሪያ የችግርን አናት ከመምታት ይልቅ ማድበስበስ እና ማስቀየስ የበዛበት ነበር፡፡ ኳስ ሜዳ ሳይቀር በዘር የሚጋደሉበት መድረክ የሆነው በጎሳ ፌደራሊዝሙ ሳይሆን በአፈፃፀሙ የተነሳ ነው ይላሉ የተሻለ የተናገሩ የመሰላቸው ኢህአዴጎች፡፡ዘራቸውን መቁጠራቸው ብቻ ባለስልጣን ያደረጋቸው ካድሬዎች የስልጣን ህልውናቸው የሆነውን የጎሳ ፌደራሊዝም በክፉ ባያነሱ አይገርምም፡፡የሚገርመው የሚወቅሱት የጎሳ ፌደራሊዝሙ አፈፃፀምም ቢሆን ከራሳቸው ውጭ ባለቤት እንደሌለው አለማወቃቸው ነው! አፈፃፀሙ አላማረም የሚሉት የጎሳ ፌደራሊዝም በማን እጅ ሆኖ ነው ያላማረው? የአፈፃፀም እንከኑ በስልጣን ላይ ቂጥጥ ካሉት ከእነሱ አላዋቂነት ሌላ በማን ሊመካኝ ነው? ሃያ ምናምን አመት ሙሉ አፈፃፀም አልቻልኩም የሚል አስፈፃሚ ምን ሊያደርግ ስልጣን ላይ ይቀመጣል?
እውን ችግሩ ከጎሳ ፌደራሊዝሙ ሳይሆን ከአፈፃፀሙ ቢሆን ኖሮ በካቢኔ ለውጥ፣በሹም ሽር የሚፈታ ቀላል ነገር ነበር፡፡ ኢህአዴግም በየጊዜው ሹም ሽር ሲያደርግ ኖሮ ጭራሽ የዶክተሮች ካቢኔ አመጣሁ ባለ ማግስት አፈፃፀምን እንደ ብርቱ ችግር እያወራ ነው፡፡ይህ የሚያሳየው የሃገሪቱ የፖለቲካ ችግር ሁሉ የሚቀዳው ከራሱ ከግንባሩ ማንነት እንደሆነ ነው፡፡ ስለዚህ የሃገር ችግር እንዲፈታ ራሱ ግንባሩ ከነእህትም ሆነ አክስት ድርጅቶቹ ከህዝብ ጫንቃ ላይ ሲወርድ ነው፡፡ የህዝብ ጥያቄም ያረጀ ያፈጀው ግንባር ከስልጣን ገለል እንዲል እንጅ ለማያርመው ጥፋቱ የተለያየ ስም እያወጣ ሁሌ ማሩኝ እንዲል አይደለም፡፡
መግለጫውም ሆነ የባለስልጣናቱ ማብራሪያ ያስቀመጠው ሌላው ጉዳይ የሃገሪቱ ብሄር ብሄረሰቦች እየተዳደሩ ያሉት በራሳቸው ልጆች ነው የሚለው ባለ መንታ ገፅ ማስቀየሻ ነው፡፡ የዚህ አባባል አንዱ መልዕክት ለሃገሪቱ ችግር ሁሉ ህወሃትን ተቀዳሚ ተወቃሽ አታድርጉ፣ችግር ካለም ችግሩን የፈጠሩት በየክልላችሁ የሚያስተዳሯችሁ የጎሳችሁ ሰዎች ናቸው የሚል ነው:: ይህ በዋነኝነት የሚያነጣጥረው በትግራይ እና በሌሎች ክልሎች መሃከል ፍትሃዊ ያልሆነ እድገት አለ በሚል ጎላ ብሎ በሚነሳው እና ህዝዊ እንቅስቃሴውን በዋናነት ባጎነው ጉዳይ ላይ ነው፡፡
በአይን የሚታየውን የኢፈርትን መንሰራፋት ተጠቅሶ ለሚቀርበው ክርክር ህወሃት መልስ ማድረግ የፈለገው ኢፈርትን ያመጣው የህወሃት አመራሮች ጠንካራነት እንጅ ሌላ እንዳልሆነ፣በሌሎች ክልሎች ተመሳሳይ የፋብሪካዎች መዋለድ እንዲታይ ያላደረገው የእህት ፓርቲዎች መሪዎች ድክመት ስለሆነ እዛው የራሳችሁን መሪዎች ውቀሱ እና ተቻቻሉ እንጅ ነገሩን የህወሃት የበላይነት ያመጣው አድርጋችሁ አትውሰዱ ለማለት ነው፡፡ ይህ ማድበስበስ የማይመልሰው አብይ ጥያቄ ግን ክልሎች ራሳቸውን እያስተዳደሩ ከሆነ በቅርቡ በኦሮሚያ፣በአማራ እና በደቡብ ክልሎች በሚደረጉ የህባዊ አመፆች ላይ ድምፃቸውን የሚያሰሙ ሰልፈኞች የሚያስተዳድሯቸውን ፓርቲ ማለትም ኦህዴድ ወይም ብአዴን ወይም ደኢህዴን ይውረድ ከማለት ይልቅ “ዳውን ዳውን ወያኔ” ሲሉ አሻግረው የህወሃትን ፍፃሜ የሚናፍቁት ለምንድን ነው? የሚለው ነው፡፡
የዚህ ማስቀየሻ ሌላው መልዕክት የጎሳ ፌደራሊዝሙን የማሞካሼቱ ቅጥያ ነው፡፡የትግራይ ህዝብ በየቤቱ ልጅ አዋጥቶ ለድል ያበቃው ህወሃት የፈጠረው የጎሳ ፌደራሊዝም ብሄር ብሄረሰቦች ራሳቸውን በራሳቸው እንዲያስተዳድሩ ያደረገ፣የሃገሪቱ ብሄረሰቦች ፈቅደው የመሰረቱት ብቸኛ እፁብ መንገድ ነው ባይ ነው ህወሃት/ኢህአዴግ፡፡ በአሁኑ ጊዜ የተፈጠረው የጎሳ ግጭትም የአፈፀፀም እንጅ የሌላ ችግር ስላልሆነ ህወሃት አምጦ የወለደውን፣ዘላለም የበላይ ሆኖ በስልጣን የመኖሩ መሰረት የሆነውን የጎሳ ፌደራሊዝም በዜግነት ፖለቲካ በተቃኜ ሌላ አይነት ፌደራሊዝም ለመቀየር የምታስቡ አደብ ግዙ የሚል ነው፡፡ ይህን አጥብቆ መናገር ስላስፈለገ ከመሄዳቸው መምጣታቸው የቀደመው አቶ በረከት ስምኦንም በየደረሱበት ሲያወሩት ሰንብተዋል፡፡ ይህን ማስረገጥ ያስፈለገው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ህወሃት አጥብቆ በሚፈልገው የጎሳ ፌደራሊዝሙ ላይ ተስፋ የመቁረጥ አዝማሚያዎች በህዝቡ ዘንድ ስለታዩ ነው፡፡
ማድበስበስ
የእህት ፓርቲ አመራር ነን ብለው የቀረቡት አራት አመራሮች አብዝተው ያድበሰበሱት የህወሃት የበላይነት ጉዳይ ከህወሃት በቀር ሶስቱ ፓርቲዎች ያሉበትን የአሽከርነት ደረጃ ያሳያል፡፡ አቶ ለማ እና አቶ ደመቀ የማይጋረደውን የህወሃት ጌትነት ለመጋረድ የሚያደርጉት መቁነጥነጥ፣የሚናገሩት ሞልቶ ተርፎ በጌታ ምሳር ላለመከተፍ ሲሉ ብቻ ሃቅን ከአፋቸው ለመመለስ የሚታገሉት ትግል፣ቁና ቁና የሚያስተነፍሳቸው የፍርሃት ሰራዊት እነሱን ሳታደርግ ግደለኝ ያስብላል፡፡
የገዥዎች እንጅ የአንድ ብሄር የበላይነት ዛሬም ድሮም እንደሌለ ለማስገንዘብ ታሪክን አጣቅሰው ያስረዱት አቶ ለማ መገርሳ ይህ ማለት እበልጣለሁ ባይ የለም ማለት አይደለም፣በፌደራል መስሪያ ቤቶች የአንድ ወገን ህልውና ጎልቶ አይታይም ማለት አይደለም ሲሉ የጌታን ስም ሳይጠሩ ዳርዳር ብለዋል፡፡የህወሃት አድራጊ ፈጣሪነት የፈጠረባቸው ብሶት ከፊታቸው የሚነበበው አቶ ለማ መገርሳ ህወሃት ከራሱ ፓርቲ አልፎ በእሳቸው ፓርቲ ውስጥ ቡድንተኞችን እያሰለፈ እንደሚያምሳቸው፣የሚሰራ በማይሰራ ተጠልፎ እንዲወድቅ እያደረገ ፈተና እንደሆነባቸው በግልፅ አስቀምጠዋል፡፡ በአንፃሩ ሌሎች እህት ፓርቲዎች ድንበር አልፈው በሌላ ፓርቲ ውስጥ ገብቶ በመፈትፈት አልተወቀሱም፡፡ ይህ ራሱ የህወሃትን የበላይነት የማይመሰክረው እንዴት እንደሆነ እህትማማች ነን ባዮቹ ራሳቸው ያውቃሉ!
አቶ ኃ/ማርያም በበኩላቸው የትግራይ የበላይነት ቢኖር ኖሮ ትግረኛ ተናገሩ ተብለን መቸገር ነበረብን፣የትግሬ ባህል እላያችን ላይ ይጫን ነበር ይህ ባልሆነበት ሁኔታ የአንድ ብሄር የበላይነት አለማለት አንችልም ሲሉ የፖለቲካ ግንዛቤያቸውን ያህል ሲናገሩ በአቶ መለስ አእምሮ ለምክትል ጠ/ሚኒስትርነት ያሳጫቸውን ምስጢር ገለፁ፡፡ አቶ መለስ ያደረጉት እንዳይቀርባቸው “አንድ አሰፋ የሚባል ሰው ከእናቱ ጋር ሲኖር ሲኖር…” ብለው ለሶስተኛ ክፍል ተማሪዎች እንኳን በሚያዛጋ ተረት አዘል ማብራሪያ የጀመሩት አቶ ኃ/ማርያም ይህን ሲሉ ማንኛውም ካድሬ አፉን የሚፈታበትን የአማራን ጨቋኝነት እና የህወሃትን ከዚህ ጭቆና አውጭ ቤዛነት ማስረገጣቸው ነው፡፡ እግረ መገዳቸውንም እሳቸውን የመሰለ ሰው ጠ/ሚኒስትር ያደረገውን “ድንቅ” ሥርዓት ለመመስረት የትግራይ ህዝብ ከአንድ ቤት ስድስት ሰባት ሰው በመገበር የከፈለውን መስዕዋትነት ገልፀው ከዛው ብሄር የወጡ ግን ደግሞ ለትግሉ ልጅ ያላዋጡ ኪራይ ሰብሳብዎች እንዴት በትግራይ ህዝብ ስም እየነገዱ እንደሆነ ገልፀው አሳርገዋል፡፡በእሳቸው ቤት ኪራይ ሰብሳቢ የተባሉት ትግሬዎች ኪራይ የሚሰበስቡት ከላይ አይዞህ ባይ ጌታ ሳያስቀምጡ እንዲሁ በአየር ላይ ነው፡፡ሰውየው አቶ ኃ/ማርያም ናቸውና ከዚህ በላይ አይጠበቅባቸውም፤የአንድ ወገን የበላይነት የሚገለፅበትን ፈርጄ ብዙ ማመሳከሪያ አገናዝበው እንዲናገሩ መጠበቅ ከእሳቸው መባስ ነው፡፡
መናገሩም መተውም የከበዳቸው የሚመስሉት አቶ ደመቀ ፈራ ተባ እያሉ የህወሃት የበላይነት አለ የሚባለው እንዲሁ ሳይሆን መንጠላጠያዎች ስላሉ ነው ቢሉም መንጠላጠያዎቹ ምን እንደሆኑ ሳያስረዱ አድበስብሰው ትተውት ለህወሃት ሽንጣቸውን ገትረው የሚከራከሩ ቤተኛ ነኝ ባይ ትግሬዎች የትግራይ የበላይነት ያለ የሚያስመስሉ ስለሆኑ ከተግባራቸው እንዲቆጠቡ ጠቁመው አለፉት፡፡የአቶ ደመቀ ንግግር ሲጠቃለል የህወሃት የበላይነት ያለ ይመስላል እንጅ የለም፡፡ ያለ የመሰለው ደግሞ አንዳንድ መንጠላጠያዎች ስላሉ ስለሆነ እነዚህን መንጠላጠያዎች ለማስወገድ ኢህአዴግ በመወሰኑ ችግሩ ይቀረፋል ሲሉ ሌላው ቢቀር አራቱ ሰዎች በተቀመጡት መድረክ ላይ የሶስቱ ፓርቲዎች መሪዎች ስለ ህወሃት የበላይነት ለመናገርም ለመተውም በሚያዩት አሳር መከራ ሳይቀር የሚገለፀውን የህወሃት የበላይነት አድበስብሰውት አልፈዋል፡፡ አቶ ኃ/ማርያም የህወሃት የበላይነት እንደሌለ የደሰኮሩትን ነገር የማይዋጥለት ብዙ እንደሆነ ጠቆም ማድረጋቸው የሚናገሩት ነገር እውነት ሃሰትነት ለራሳቸውም እንደማይጠፋቸው ያሳብቃል፡፡የህወሃቱ ዶ/ር ደብረፅዮን የህወሃት የበላይነት የሚለወን ነገር ያስጀመረባቸው ደርግ እንደሆነ፣ ያኔ በድርድሩ ወቅትም ከህወሃት እንጅ ከኢህዴን ጋር አልደራደርም ሲል እንደነበረ ይህ ነገር አሁንም የቀጠለው የተመሰረተው ስርዓት የሁሉም እንዳልሆነ ለማስመሰል በሚደረግ ተንኮል እንጅ ሌላ የሚጨበጥ ምክንያት እንደሌለው ሰሚ ካገኙ ለማስረዳት ሞክረዋል፡፡
ሌላው አናዳጅ ማድበስበስ የኢህአዴግ መንግስት የሰብዓዊ መብት አያዝን በተመለከተ የተነገረው ይሉኝታ ቢስነትን የጨመረ ሹፈት ነወ፡፡በዚህ ረገድ አራቱም መሪዎች አላግጠዋል፣የምናውቀውን እንደማናውቅ ሊያሞኙን ሞክረዋል፡፡የመንግስታቸው አውሬያዊ አረመኔነት የሚገለፅበትን የህሊና እስረኞች አያያዝ በተመለከተ ያለውን ያፈጠጠ ሃቅ ሊክዱ ከንቱ ደክመዋል፡፡ በፍርድ ቤት ችሎት የተገኘ ሁሉ የሚያነባበትን በተለይ በፖለቲካ እስረኞች ላይ ስለሚፈፀመው አረመኔያዊ ድርጊት ትንፍሽ ሳይሉ ‘እንደተጠበቀው አይደለንም እንጅ ምንም አንልም’ ሲሉ አላገጡ! ማዕከላዊ የሚባለው የሲኦል ቅርንጫፍም የሚዘጋው በደርግ ዘመን የነበረው የስቅይት ቆሌ እየመጣ እያስደነገጠ ስለሆነ እንጅ ዛሬ ግፍ ስለሚሰራበት አይደለም ባይ ናቸው በደህና ቀን ይሉኝታቸውን የጣሉት ጠ/ሚኒስትር ተብየው ሰውየ! አቶ ለማ መገርሳም እስረኞች በምርመራ ጊዜ የሚደረገውን የሰብአዊ መብት ጥሰት በለሆሳስ አልፈው በፍርድ ስርዓቱ ሂደት እና መዛባት ላይ ማተኮርን መርጠዋል፡፡
ጠ/ሚ ኃ/ማርያም ደሳለኝ ደርግ ሰዎችን ሲያሰቃይበት የነበረውን ማዕከላዊ የተባለውን ማጎሪያ ሙዚየም ልናደርገው ነው ሲሉ ማዕከላዊን የሲኦል ቅርንጫፍ በማድረጉ በኩል እሳቸው አቤት ወዴት የሚሉለት ስርዓት የባሰው እንደሆነ እኛ ቂልነታችን የተረጋገጠ ህዝቦች አናውቅም፡፡ ለመሆኑ በዚች ሃገር ሰው የሚሰቃየው ማዕከላዊ ብቻ ነው?የነገሩ ስር ያለውስ በማዕከላዊ ሙዚየም መሆን አለመሆን ነው በስርዓቱ ኢሰብዓዊ ጨካኝ ተፈጥሮ?በደብረዘይት፣ በሸዋሮቢት፣ በቂሊንጦ፣ በዝዋይ ቀርቶ በጦር ኃይሎች ሆስፒታል ሳይቀር ሰው እየታሰረ ቁም ስቅል እንደሚያይ የአይን ምስክሮች አልገለፁም? ጠላቱን በማሰቃየት የሚደሰት ሥርዓት ማዕከላዊ ስለተዘጋ የማሰቃያ መቼት አጥቶ ያነደደውን የበቀል እሳት ሊያጠፋ መሆኑ ነው? ማዕከላዊን ለግፍ ይጠቀምበት የነበረው ደርግ ብቻ ከሆነ ለምን እስካሬ አልዘጉትም? ከሃያ ስድስት አመት በኋላ ምን መጣ? ዛሬ ተቀይረው ነው ብለን በቅንነት እንዳንቀበል እልፍ ማድበስበሳቸው፣ሽህ ማስመሰላቸው ያለመቀየራቸው ምስክር ነው! እንዲህ ባለው ማድበስበስ እና ጨፍኑ ላሙኛችሁ ውስጥ ሃገራዊ መግባባት ቀርቶ ግለሰባዊ መደማመጥ ሊመጣ አይችልም፡፡መለወጥ ከመፀፀት ይጀምራል፡፡ መፀፀት ደግሞ ስህተትን ጠብሰቅ ረገጥ አድርጎ ማመንን ይጠይቃል ፡፡
አቶ ኃ/ማርያም ምናልባት ደርግ ከወደቀ በኋላ ማዕከላዊ ውስጥ የሚመረመር ሰው ለስላሳ ሙዚቃ ተከፍቶለት ነው ተብለው ይህንንም አምነው ይሆናል፡፡ እኛ ግን ስለማዕከላዊ በእዛው የግፍ ጊቢ ውስጥ ፍዳ መከራቸውን ከቆጠሩ፣ዘራቸውን መተካት ቀርቶ ሱሪ መታጠቅ እንዳይችሉ ተደርገው ግልድም አገልድመው ፍርድቤት የቀረቡ፣የበደላቸው ብዛት ሃፍረታቸውን አስረስቷቸው ልብሳቸውን አውልቀው በወንድነታቸው ላይ የደረሰውን በደል ለህዝብ ሲሳዩ አይተን ሰምተናልና በኃ/ማርያም ቀልድ የምንስቅበት ጥርስ የለንም! ማዕከላዊን ለሰይጣናዊ ጭካኔው የሚጠቀምበት ደርግ ብቻ ከሆነ ዛሬ የእነ ንግስት ይርጋን አስር የእግር ጥፍር ነቅሎ በፌስታል እነሆ የሚለው ማነው ነው? ማዕከላዊ ሰው በእግሩ ገብቶ በቃሬዛ የሚወጣበት፣መነኩሴ ቆቡ ወልቆ ቱታ እንዲለብስ የሚገደድበት፣የሰው ልጅ እንደ ክርስቶስ የሚሰቀልበት የዝነኛ አረመኔዎች አምባ መሆኑን አላውቅም የሚል ካለ ሆዱ እና ጭንቅላቱ የተቀያየረበት የስልጣን አምላኪ ብቻ ነው! ይህን ለማድበስበስ መሞከር በራስ ላይ እሳት ማንደድ ነው! ስህተትን ማድበስበስ እና ማስቀየስ ሳይታረሙ የመሞት ምልክቶች ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ የማንን መጨረሻ እንደሚያከፋ ይታያል፡፡
ሌላው ግልፅ ማድበስበስ ግማሽ ሚሊዮን ህዝብ ለዓመታት ከኖረበት ቀየው በማንነቱ ብቻ ተፈናቅሎ ሜዳላይ የተሰጣበትን ወንጀል ሃላፊነት የሚወስድ ማን እንደሆነ የተቀመጠበት መንገድ ነው፡፡ የዚህን ትልቅ ወንጀል ሃላፊነት የሚወስዱት መናፍስት ይሁኑ ሰው ማይታወቁ ኪራይ ሰብሳቢዎች እና ኮንትሮባንዲስቶች ሆነው ተቀምጠዋል፡፡ይህን የሚሉት ለህዝብ አሳቢ ተደርገው ድቤ እየተመታላቸው ያሉት አቶ ለማ መገርሳ መሆናቸው ተስፋ ያስቆርጣል፡፡ የወልቃይት ጉዳይ በዝምታ መታለፉ ደግሞ የብአዴንን የቁም ሞት ብቻ ሳይሆን የህወሃትን የልቡን ሳይሰራ የማይተኛ፣የሁልጊዜ አሸናፊነት ያስገነዝባል፡፡ በዚህ ጉዳይ የሚመጣውን መዘዝ መመለሱ አድበስብሶ እንደማለፉ የሚቀል ከሆነ የምናየው ይሆናል፡፡
ኢህአዴግ በማብራሪያው የተቃውሞ ፖለቲካውን ስላሽመደመደበት እኩይ ስራው ያስቀመጠው ማብራሪያ ከማድበስበስም በላይ ነው፡፡ የተቃውሞ ጎራውን እግር በእግር እየተከታለ ቋንጃውን ሲቆርጥ የኖረው ባለጠመንጃው ኢህአዴግ ‘ለተቃውሞ ፖለቲካው ድጋፍ ባለማድረጌ ፀፅቶኛል፤ ይህንንም ያለ ሃፍረት መክሬበታለሁ’ ሲል የሰራው ስራ አሳፋሪ መሆኑን ልቦናው እንዳወቀ ያሳብቃል፡፡ ኢህአዴግ ተቃዋሚዎች እግር ሲያወጡ ጠብቄ እግር እቆርጣለሁ ከማለት በገንዘባቸው የሆቴል አዳራሽ ተከራይተው እንኳን እንዳይመክሩ እስከማድረግ የደረሰ፣ በመጨረሻም ለመደራደር ስምንት ወር የሚደራደሩ ምንደኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን አዝሎ የቀረ እኩያ አልቦ አምባገነን ፓርቲ እንደሆነ ቤት ቀርቶ ጎረቤት ያወቀው ሃቅ ነው፡፡
የተቃውሞውን ጎራ በጠመንጃ እና በእስርቤት ታግዞ ፀጥ ካደረገ በኋላ አውራ ፓርቲ ነኝ ሲል የኖረው ኢህአዴግ ዛሬ ብድግ ብሎ የተቃውሞ ፖለቲካውን ባለማገዜ አዝናለሁ ማለቱ ቀልድ ይሁን ቁምነገር ውሎ አድሮ ይለያል፡፡ ያለምንም ይሉኝታ ምርጫ ቦርድን ሳይቀር ተጠቅሞ፣ፍርድቤቶችን አስከትሎ፣ወታደሩን አሰማርቶ፣ይሁዳዎች አስርጎ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን እንዳልነበረ ማድረግ የተቃውሞ ፖለቲካውን ማውደም ሳይሆን አለማገዝ ብቻ ሆኖ የቀረበበት መንገድ ለነገሩ ቀልድነት ፍንጭ ሰጭ ነው፡፡
መካድ
ከግምገማው መልስ ሃገራችን የምትገኝበት ችግር ሁሉ መንስኤ በፓርቲችን አባል ፓርቲዎች መሃከል የሚደረገው መርህ አልቦ ግንኑነት ነው እንጅ አስተዳደራችን ለእኩልነት የተመቼ የማንም የበላይነት የሌለው ነው ይላሉ ክህደት መድህን የሚመስላቸው የኢህአዴግ መሪዎች፡፡ የባሰውን ያመጡት አቶ ለማ መገርሳ ደግሞ “የኢትዮጵያ ህዝብ እያለ ያለው ተስተካከሉና እናንተው አስተዳድሩን ነው” ሲሉ ወፍራም ክህደት ይክዳሉ፡፡“ዳውን ዳውን ወያኔ!” የሚለው በየሰላማዊ ሰልፉ የማይጠፋው ጥያቄ እንዴት ሆኖ ተስተካክላችሁ ግዙን ተብሎ እንደተተረጎመ ካድሬ ያልሆነ ሰው ሊገባው አይችልም፡፡
የኢትዮጵያን ህዝብ ወገብ ያጎበጠው የዲሞክራሲ እጦት፣የእኩልነት ጥማት፣ የመተንፈሻ መድረክ ማጣት ቀንበር፣የድህነት መንሰራፋት፣የሰብዓዊ መብት ረገጣ፣ የሙሰኛ ባለስልጣናት በስልጣን መባለግ፣ የፍርሃት ቆፈን ሁሉ ወደጎን ተጣለና ዋኛው የሃገሪቱ ችግር የኢህአዴግ አባል ፓርቲ የላይኛው አመራር ከቀድሞ አሽከርነቱ መጉደሉ ተደርጎ ቀረበ፡፡ ይህ የሚያሳየው ህወሃት ኢህአዴግን ችግር መስሎ የሚታየው የራሱን ስልጣን ሊያሳጣ የሚችል ችግር ብቻ መሆኑን ነው፡፡ እንደ ጉድ የተወራው የግንባሩ አባል ፓርቲዎች የጎንዮሽ ልፊያ ፈፅሞ የኢትዮጵያ ህዝብ ችግር አይደለም፡፡ችግር ከሆነ ችግር የሚሆነው በአሽከር ካድሬዎች አድሮ ኢትዮጵያን ሲዘውር ለኖረው እና ታማኝ አሽከሮቹ ቀን አይተው ላንጓጠጡት ህወሃት ብቻ ነው፡፡በዚህ ከቀጠልን በሃሳብ ብቻ ሳይሆን በሌላም መታኮሳችን አይቀርም የሚለው የዶ/ር ደብረፂዮን ንግግር የዚህ ምስክር ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ጥያቄ የስርዓት ለውጥ፤የእኩልነት ጥማት፣የሃገር ባለቤትነት፣የሰብዓዊ ክብር አምሮት ነው እንጅ የህወሃት በኦህዴድ ላይ መግነን ወይም የዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት የቀድሞ ግርማ መሸራረፍ አይደለም፡፡በነዚህ እውነተኛ የህዝብ ጥያቄዎች ዙሪያ ያላጠነጠነ የክህደት መንገድ ለራስ እንጅ ለህዝብ ጥያቄ መልስ አይሆንም!
የመግለጫ/ማብራሪያው አያዎ
ኢህአዴግ ታላላቅ ፖለቲካዊ ውሳኔዎች አስተላለፍኩበት ሲል ብዙ ያለለት መግለጫም ሆነ ማብራሪያ ልብ ላለው በተቃርኖዎች የተሞላ ነው፡፡ የተቃርኖውን አሃዱ ሲል ኢህአዴግ የመሰረተው ስርዓት ማንንም የበላይ ማንንም የበታች የማያደርግ የእኩልነት ዓለም እንደሆነ በመግለጫው የወተወተው ተረስቶ በኢህአዴግ እህት ድርጅቶች ውስጥ ከፍተኛ አፈና በመኖሩ የተለየ ሃሳብ ማንፀባረቅ ስላልተቻለ በፓርቲው ውስጥ ዲሞክራሲ ሊቀጭጭ ቻለ ሚል ነገር በአራቱም አመራሮች አብዝቶ ተነገረ፡፡ያለ ፍርሃት መናገር ባለመቻሉ ደግሞ በእህት ፓርቲዎች ውስጥ አለመተማመን እና ጥርጣሬ ነገሰ፤የሰፈነው አለመተማመን እና ጥርጣሬ ደግሞ እስከመታኮስ ሊያደርስ እንደሚችል ነው የተብራራው፡፡እንደተባለው ፓርቲው የበላይ እና የበታች የሌለው የእኩልነት ቤት ከሆነ የተለየ ሃሳብ እንዳይነገር የሚያፍነው ማን ነው? አፈና እና አፋኝ ካለ አፋኙ የበላይ ታፋኙ የበታች መሆኑ ያነጋግራል? አፈና ባለበት እኩልነት ከወዴት ይመጣል?የበላይ የበታች ካልኖረ ማን ማንን ነው የሚፈራው? ምን እንዳይመጣ ነው ጥርጣሬው?
ሌላው አያዎ በአቶ ለማ መገርሳ ተነገረው የኢትዮጵያዊነት ጭነት ጉዳይ ነው፡፡ አባይን ተሻግረው “ኢትዮጵያዊነት ሱሴ ነው” ሲሉ የባጁት ኦቦ ለማ ከዶ/ር ደብረፅዮን ጋር በተሰየሙበት መድረክ ደግሞ ኢትዮጵያዊነት በብሄር ብሄረሰቦች ላይ የተጫነ ጭነት በመሆኑ በጎሳ ፌደራሊዝሙ በኩል ብሄር ብሄረሰቦች ራሳቸውን ያስተዳድሩ ዘንድ ግድ እንደሆነ ፈርጠም ብለው ይገልፃሉ፡፡ ወዲያው ደግሞ ማንኛውም የግንባራቸው እርምጃ ሃገራዊ አንድነትን ጥያቄ ውስጥ የማያስገባ፣የሃገርን ህልውና ያስቀደመ መሆን እንደሚገባው ጠንከር አድርገው ይናገራሉ፡፡ በግድ የተጫነ ላሉት ኢትዮጵያዊነት ህልውና ይህን ያህል ማሳሰቢያ ማብዛታቸው ግራ ነው፡፡
ሌላው የአቶ ለማ ግራ አጋቢ ንግግር በስራ አስፈፃሚው ስብሰባ ውጤት መርካታቸውን የገለፁበት ነገር ነው፡፡በአራቱ ድርጅቶች መግለጫ ላይ በተሻለ ድፍረት እውነትን ለመግለፅ ሲጣጣሩ የዋሉት አቶ ለማ ብዙ ጭጋግ በወረሰው የግንባራቸውን የስራ አስፈፃሚ ስብሰባ ውጤት ለመርካት መቸኮላቸው የውድ ይሁን የግድ ራሳቸው ያውቃሉ፡፡አቶ ደመቀ መኮንን ስለ ህወሃት የበላይነት አለመኖር እየተናገሩ ይህን የሚያስጠረጥሩ አንዳንድ መንጠላጠያዎች ግን መኖራቸውን የደሰኮሩት የአሽከርነት ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ነገር ቢሆንም ምንም በሌለበት መንጠላጠያ ከየት መጣ ማስባሉ አይቀርም፡፡ አቶ ደመቀ አንዳንድ መንጠላጠያዎች ሲሉ ሊያሳንሱት የሞከሩት በውትድርናው፣በደህንነቱ፣በውጭግንኙነቱ፣በውጭ ንግዱ፣በኢፈርት ግዝፈት፣በየፌደራል መስሪያቤቱ የአድራጊ ፈጣሪ ስብጥር፣በአዲስ አበባ ሁለመና የሚገለፀውን ለአደግዳጊ ብቻ የማይከሰተውን የገዘፈሃቅ ነው፡፡በዚህ ረገድ አይናቸውን በጨው አጥበው ከተናገሩት አቶ ደመቀ ይልቅ “ህወሃት የበላይ አይደለም የምንለውን ሁሉም ሰሚ እንደማያምነን እናውቃለን” ያሉት አቶ ኃ/ማርያም ይሻላሉ፡፡
የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ስብሰባ በእህት ድርጅቶቹ በኩል ያለውን ችግር በመፍታቱ ለሁሉ መፍትሄ ያመጣ፣በውስጠፓርቲው ቀርቶ ለተቃዋሚዎ ፓርቲዎች የመጫወቻ ሜዳውን በመክፈት ዲሞክራሲን የማስፋት ስራ እንዲሰራና ሃገራዊ መግባባት እንዲመጣ በማድረግ ሃገራችን ላለችበት ችግር ፖለቲካዊ መፍትሄን የሚያመጣ ተደርጎ ቀርቧል፡፡ይህ በሚነገርበት ወቅት ግን ከፖለቲካዊ መፍትሄ ጋር ግንኙነት በሌለው ሁኔታ መለዮለባሾችን ያጨቀ በአቶ ሲራጅ ፈጌሳ እና በአቶ ኃ/ማርያም ደሳለኝ የሚመራ፣በክልል ፕሬዚደንቶች የታጀበ የብሄራዊ ፀጥታ ምክርቤት ስብሰባ ይከወናል፡፡ ይህ የፀጥታ ምክርቤት ፋኖ በየክልሉ አሰማርቶ የሃገሪቱን ፀጥታ በክላሽ በታጀበ ሁኔታ የሚያስጠብቅ ግብረሃይል ነው፡፡ ይህ ግብረሃይል ከተዋቀረ አንድ ወር አስቆጥሯል፤ከሰሞኑም የየክልል ፕሬዚደንቶችን ጨምሮ ለስብሰባ ተሰይሟል፡፡በዚህ ውስጥ ጉልበት እንጅ ፖለቲካዊ መፍትሄ አይታይም፡፡ እውን ኢህአዴግ ለሃገራችን ወቅታዊ ችግር ፖለቲካዊ መፍትሄ ቢሰጥ ኖሮ የክልሎችን ፀጥታ ለማስጠበቅ የክልል ፖሊስ በቂ ነበር፡፡
ብሄራዊ የፀጥታ ምክርቤቱ ፀጥ የማድረግ ስራውን ለመከወን ወደ ክልሎች ሲወርድ የክልሎች የሲቪል አስተዳደር ተሸመድምዶ ለዚሁ ወታደራዊ ጫማ እጅ አለመስጠቱን፣ያልታወጀ የአስቸኳይ ጊዜ አስተዳደር በሃገሪቱ ስለአለመስፈኑ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ሃገርን የማረጋጋቱ ስራ በወታደራዊ ጡንቻ ታገዘ ማለት የደህንነት እና ወታደራዊ ክንፉን የሚዘውረው ህወሃት የተለመደ ግዝፍናውን አገኘ ማለት ነው፡፡ይህ ማለት ደግሞ በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ምክርቤት ስብሰባ ብዙ የተወራለት የግንባሩ እህት ድርጅቶች ነፃነት፣ራስን በራስ የማስተዳደር ነገር ውሃ በላው ማለት ነው፡፡
“ወደህ በገባህ አትከራከር!”
አስራሰባት አመት መታገሉን የጌትነቱ ሰገነት ያደረገው ህወሃት በኢህአዴግ ማዕቀፍ ውስጥ አጋርም ሆነ አባል ብሎ የሰየማቸው ፓርቲዎች ውልደት እድገታቸው ህወሃት በደሙ በላቡ በፃፈው “ደማቅ ታሪክ” እንደሆነ አምነው የተጠመቁ፣ይህንኑ የቤቱን ህግ አክብረው ሊኖሩ ወደው የገቡ የድሮ የጠመንጃ ገድል ምርኮኞች ናቸው፡፡ ይህን በተግባርም በቃልም ከማስገንዘብ የማይቦዝነው ህወሃት ከአንድ ትግሬ አባወራ ቤት ስንት ሰው ሞቶ በአጠቃላይ ስልሳ ሽህ ትግሬ ተሰውቶ አዲስ አበባ እንደ ተደረሰ ለወዶ ገቦቹም ሆነ ለኢትዮጵያ ህዝብ ለመተረክ ደክሞት አይውቅም፡፡ ህወሃት ስልጣን ላይ ለመቀመጥ ስልሳ ሽህ ምክንያት እንዳለው በቅርቡ በትግራይ ኦንላይን ላይ ተፅፎ አንብበናል፡፡
በኢህአዴግ ቤት ተቀምጦ የህወሃት እበልጣለሁባይት አስቸገረኝ፣ቡድንተኞች አሰማራብኝ፣ዘመዶቹ ይበልጥ ቤተኛ ነን አሉኝ፣ እኔ ሳላውቅ በክልሌ ወታደር ልከው አስተኮሱብኝ የሚለውን ክስ የሚያቀርብ ባለሟል ይሳቅበት ይሆናል እንጅ አይታዘንለትም፡፡የተለመደውን፣ወደው የገቡበትን፣የቤቱን ዋነኛ ደንብ ዛሬ ከሰማይ ዱብ ያለ በደል አድርጎ ማውራት ትርጉም የለውም፡፡
ጥያቄያቸው እና ጥያቄያችን ….
ኢህአዴግ ብዙ ችግሬን አየሁበት መፍትሄም አስቀመጥኩበት ባለበት የሰሞኑ የስራ አሰፈፃሚ ስብሰባው አንገብጋቢ አድርጎ ያነሳው ጉዳይ ሲጠቃለል ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት በግንባሩ ውስጥ የቀድሞ ሞገሱን ማጣቱ፣የአባል ፓርቲዎች ቋንቋ መደበላለቅ፣ከቀድሞ አቤት ወዴት ባይነታቸው መጉደል፣የውሰጠ ፓርቲ ደሞክራሲአለመኖር ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ደግሞ የራሱን የቤት ጣጣ ነው እንጅ የኢትዮጵያ ህዝብ ጉዳይ አይደለም፡፡ ችግር ተደርጎ የቀረበው የግንባሩ ፓርቲዎች የቋንቋ መደበላለቅ፣ የዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ክንድ መዛል ለኢትዮጵያ ህዝብ ደስታ እንጅ ሃዘን አይደለም፡፡
የኢትየጵያ ህዝብ የሚፈልገው ዲሞክራሲ እነ አቶ ለማ/ደመቀ የሚናፍቁት ከኢህአዴግ ውስጠ ፓርቲ ተነስቶ፣በሊጎች እና ክንፎች ዞሮ ህዝብ ጋ የሚደርስ፣ በዲሚክራሲያዊ ማዕከላዊነት የተቀፈደደ አይነት ዲሞክራሲ አይደለም፡፡ስለሆነም ኢትየጵያህዝም ጥያቄ ከኦህዴድም ሆነ ከብአዴን ጥያቄ ጋር አይገጥምም፡፡ኢህአዴግ የሚወተውተው የተለውጫለሁ ጋጋታም ከሚፈለገው ለውጥ ርቆ የቆመ ማስመሰሉ የበዛ፣ ይጨብጡት ዘንድ ህልውና የሌለው፣እስረኛ እፈታለሁ ከሚለው በስተቀር ሌላ የሚጨበጥ ቁምነገር የሌለው ነገር ነው፡፡ እስረኛ እፈታለሁ የሚለውም የባቡር ሃዲድ ስለሰራሁ፣አባይን ስለገደብኩ ስልጣ ላይ ልቀመጥ የሚለው የተለመደ ስልጣን ላይ ለመሰንበት የሚጠየቅ የዋስትና ማረጋገጫ ከመሆን አይዘልም፡፡
ለአስተያየት [email protected]
ሊለመድ የሚገባው የክርክር አካሄድ ግለሰቡን ከመስደብ ይልቅ ሃሳቡን በተሸለ ሃሳብ የማምከን ሂደት የሚሻል ይመስለኛል፡፡ የስድብ ናዳ ስድብን እንጂ የተሻለ ተሟጋች አያፈራም፡፡ ምናልባትም ይሄ ይመስለኛል ሃሳብን የሚፈራ ትውልድ እንድናፈራ ያደረገን፡፡ ስለዚህ የለማ መገርሳ ና የጓዶቹ አካሄድ ያልጣመው ግለሰብ ወይም ቡድን ያለጣመውን ሃሳብ በላቀ ሃሳብ ሊያሸንፍ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡ ሃሳብህን የመግለጽ መብትህን አከብራለሁ፡፡ ስለሰውይው ያለን እይታ ግን ይለያል፡፡ ይህን እይታዬን ካከበርክ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጰያዊነት ብዙ የምናበረክተው ነገር ይኖረናል፡፡ከስሜት በጸዳ፤ከጎሰኝነት በራቀ፤ጥቅመንነትን ባለወገነ… ከመሳሰሉት ጉዳዮች ከራቅን ፈጣሪ ይረዳናል፡፡ምን ትላለህ ወንድሜ፤