በካናዳ ኣልበርታ ክፍለሃገር ከሚኖሩ ተጋሩ ኢትዮጵያዊያን የተሰጠ መግለጫ

በአሁኑ ወቅት በአገራችን ኢትዮጵያ በታሪካችን አይተነው በማናቀው ሁኔታና በጣም አሳስቢ በሆነ ደረጃ  በተለያዩ ክልሎች በርካታ ኢትዮጵያዊያን በብሄራዊ ማንነታቸው ብቻ ለእንግልት ስቃይና ሞት እየተዳረጉ ይገኛሉ።
መንግስት ባለበት አገርና የዜጎቻችን በየትኛወም የኣገሪትዋ ክፍል በሰላም የመኖር፣ ንብረትና ሃብት የማፍራትና ኣምራች ዜጋ የመሆን ህገመንግስታዊ መብት በሚፃረር መልኩ ከቀያቸው እንዲፈናቀሉ፣ ጥረው ግረው ያፈሩት ንብረት በግፍ እንዲቃጠልና እንዲዘረፍ ሲደረግ፤ በርካታ ንፁሃን ዜጎች ኣሰቃቂና ኢስባዊ በሆነ መንገድ ጭፍን ጥላቻ ባሰከራቸው እብሪተኞች በኣደባባይ በድንጋይና ዱላ ተወግረው ተግድለዋል። 

ዜጎቻችንን በላቀ ዕውቀት ክህሎት እና ስነምግባር የማነፅ ተልእኮ የተሰጣቸው አንዳንድ የክፍተኛ ትምህርት ተቋማት ብሄር ላይ ያተኮረ ጥላቻ እሚሰበክባቸው አንዱ አሳዳጅ ሌላው ተሳዳጅ እሚሆንባቸው ተቋማት እየሆኑ ነው :: ለአብነት ያህል በመቱ ዩኒቨርሲቲ የተመደቡ የትግራይ ብሄር ተማሪዎች እነዝህ ጥላቻ ያሰከራቸው ቡድኖች እያደረሱባቸው ባለው ጥቃት በተረጋጋ መንፈስ መማር አልቻሉም ብቻ ሳይሆን ለህይወታቸው በጣም አስጊ ሁኔታ ላይ ናቸው;; ብዙዎቹም ትምህርታችውን አቋርጠው ወደ አጎራባች ክልሎች ለመሸሽ ተገደዋል::

ይህ እየተከሰተ ባለበት ሁኔታ ግን የክልሉና የዩኒቨርሲቲው መስተዳድሮች አይተው እንዳላዩ ድርጊቱን ጆሮ ዳባ ልበስ ብለውታል ;; ወንጀሉ ግን አሁንም እንደቀጠለ ነው:: ይህ እኩይ ተግባር ለማናችንም እማይበጅ፣ የህዝቦቻችንን አንድነትና መፈቃቀር እሚሸረሽርና የአገሪቱን ህልውና አደጋ ላይ ከትቶ የጠላት ሲሳይ እሚያደርገን አካሄድ መሆኑ መገንዘብ ይኖርብናል::

የፖለቲካ ችግር አለብኝ የሚል አካል ከሚመለከታቸው ፖለቲከኞች ጋር በሚፈልገው ቋንቋ መነጋገር ይኖርበታል እንጂ ንፁህ ኢትዮጵያውያን ዚጎችን በማንነታቸው ምክንያት ማዋከብ ፣ ማንገላታትና መግደል በማነኛውም መመዘኛ ተቀባይነት የሌለውና ኣጥብቀን የምናውግዘውና የምንታገለው ጉዳይ ነው::

ስለዚህ እኛ በከናዳ ፤ ኣልበርታ ክፍለሃገርና ኣከባቢዋ የምንኖር የትግራይ ተወላጆች ከላይ በተጠቀሱት  ወቅታዊ ጉዳዮች  ላይ የሚከተሉትን የአቛም መግለጫ  ውሳኔዎች ኣስተላልፈናል።

1. በአሁኑ ግዜ በኦሮሚያ ክልል እየተከሰተ ያለውን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎችና ወቅቶች በግለሰብ ደረጃም ይሁን በተደራጀ መልኩ ብሄር ላይ ያተኮረ ወንጀል ላይ ተሳትፊ የሁኑ ሁሉ መንግስት በአስቸኩዋይ ወደፍርድ እንዲያቀርባቸውና ቅጣታቸውን እንድያገኙ፤ ለወደፊቱም እንደዚህ አይነት ኢሰብኣዊ ወንጀሎች ከመከሰታቸው በፊት ኣስቅድሞ እንዲከላከል እንጠይቃለን።

በአንዳንድ ኦሮሚያ ውስጥ በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ዉስጥ እሚማሩ የትግራይ ተወላጆችን ጨምሮ  ብሄር ለይቶ እየተፈፀመ ያለውን ማንኛውም ጥቃት አጥብቀን እናወግዛለን :: ስለዚህም የችግሩ አሳሳቢነት ተገንዝቦ የሚመለከተው የመንግስት አካል የተማሪዎችን ህይወት ከአደጋ እንዲከላከልና  በተመደቡበት የከፍተኛ ትምህርት ተቛማት ተረጋግተው እንዲማሩ በኣፅንኦት እንጠይቃለን::

2. የትግራይ ህዝብ ከደርግ ጭቆና ለመውጣት ባካሄደው መራራ የትጥቅ ትግል ከቁጥሩ ጋር ፈፅሞ እማይመጣን ከፍተኛ መስዋእትነት የከፈለና ያ እስከፊ ጦርነት ካሳደረበት ጠባሳ ለማገገምና ከድህነት ለመውጣት ደፋ ቀና እያለ እሚገኝ ህዝብ ነው :: ሆኖም ላለፉት 26 ዓመታት ትርፍ ተጠቃሚ እንደሆነ ተድርጎ በበርካታ ተቃዋሚ ግለሰቦችና ድርጂቶች በጣም ከባድና ያላሰለሰ የሃሰት ፕሮፓጋንዳ ዘመቻ እንደተካሄደበት ግልፅ ነው።

ይህ ሲሆን ግን በፌደራል መንግስም ይሁን በክልሎች መንገስታት (በተለይ በትግራይ ክልል ባለስልጣናት) ይህንን የጥላቻ ዘመቻ ለማክሸፍና ህዝባችን ትክክለኛ እውነታውን እንዲረዳ ጥረት ሲደረግ አላየንም። ስለዚህ ይህ የሃሰት ፕሮፓጋንዳ  እንዲታረምና ህዝቡ ጥናት ላይ የተመሰረተ ትክክለኛ መረጃ በወቅቱ እንዲያገኝ መንግስት ከፍተኛ ጥረት እንዲያደርግ እንጠይቃለን::

3. በውጭ ሃገራት በተለይ በምእራቡ ኣለም እየኖሩ የዘር ማጥፋት ኣላማና ኢላማ የሚሰብኩና  በኢትዮጵያ ዉስጥ በፈፀሙት ወንጀል በህግ እሚፈለጉ እንደነ ሻለቃ ዳዊት ወ/ግዮርጊስ  የመሳሰሉት የቀድሞው ወታደራዊ መንግስት ባለስልጣናት እና ሌሎች ግለሰቦች መንግስት በህግ እንዲከታተላቸው በአጽንኦት እንጠይቃለን። እኛም በበኩላችን እነዚህ ገልሰቦችንና ሌሎች ጥላቻንና የዘር ማጥፋት ዘመቻን እየሚሰብኩና ለተግበራዊነቱም እየተጉ እሚገኙትን ግለሰቦችንና ሚድያዎችን በህጋዊ መንገድ እንደምንታገላቸው እናረጋግጣለን::

4. መንግስት በማህበራዊ ሚድያዎች በገፍ እየተለቀቁ ያሉትን አፍራሽና ከፋፋይ የጥላቻ ቅስቅሳዎችን ከሚዲያዎቹ ባለቤቶች ፧ለምሳሌ ፌስቡክ ትዊተር ወዘተ ጋር በመመካከር ቁጥጥር እንዲያደርግላቸው እና የአገር በቀል መገናኛ ብዙሃን ትክክለኛና ወቅታዊ መረጃዎች ለህዝብ እንዲያቀርቡ እንዲያበረታታ እንጠይቃለን።

5. በክልል መንግስታት ባለስልጣናት ሀገራዊ ጉዳዮች በተመለከተ የሚደረጉ  መግለጫዎችና ውሳኔዎች፣ የፌዴራላዊ መንግስት ህግጋትን የጣሱ ስለሚመስሉና ለዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንቅፋት ስለሚሆኑ እነዚህ መግለጫዎች ወደህዝብ ይፋ ከመሆናቸው በፊት ፌደራል መንግስቱ በሰከነ ልቦና ተወያይቶ እልባት ካደረገባቸው በኋላ መሆን ኣለበት ብለን እናምናለን።

የኢትዮጵያዊ ሁሉ ህገመንግስትዊ መብቱ ይከበር!!

ኖቮምበር 2017   አልበርታ ካናዳ

********

Guest Author

more recommended stories