ፌደራላዊ ስርዓት የሕዝቦች የመግባባት ምንጭ እንጂ የስጋት ምንጭ ኣይደለም ~ ማሕበር ተጋሩ ኣውሮፓ

ማሕበር ተጋሩ ኣውሮፓ

ዕለት፡ 06 ኖቨምበር 2017
ቊፅሪ፡ ማተኣወ 20171106/1

ፌደራላዊ ስርዓት የሕዝቦች የመግባባት ምንጭ እንጂ የስጋት ምንጭ ኣይደለም!

ኢትዮጵያ እንደ ሃገር የረጅም ዘመናት ታሪክ ባለቤት ብትሆንም የሚጠበቀባትን ማሕበረሰባዊ እድገት ማስመዝገብ አልቻለችም። በአንድ ወቅት ከነበረችበት የታሪክ ማማ በድህነት እና ኋላቀርነት የምትጠቀስ ሃገር ወደመሆን መሻገሯ የሕዝቦቿ ቁጭት የሚቀሰቅስ አሳዛኝ ክስተት ሆኖ በታሪክ ይታወሳል።

የኋላቀርነቱ ምክንያት የተከተለችው ስርዓት ውጤትም ነውና ውድ የሕዝብ ልጆች በከፈሉት መስዋእትነት በ1983 ዓም ታሪክ ወደኋላ ላይመለስ ተቀይሯል። ኢትዮጵያ በሕዝቦች መፈቃቀድና መግባባት የተመሠረተ ፌደራላዊ ስርዓት እንደሚያስፈልጋትና ይኽም በተጨባጭ ኢትዮጵያ እንደሃገር ወደልማትና እድገት የምታደርገውን ጉዞ የሚያፋጥን መሆኑ በተግባር የታዬና አሌ የማይባል ሐቅ ነው።

ኢትዮጵያን እንደ ሃገር እንደ አዲስ ወደቀድሞ ክብሯ ለመመለስ በተደረገው መራራ ትግል በወቅቱ የነበረው ማሕበር ተጋሩ ኣውሮፓ (የትግራይ ተወላጆች ማሕበር በኣውሮፓ) ሚና ጉልህ እንደነበረው የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው። አባላቱ በሃብት፣ በእውቀትና በጉልበት ትግሉን ደግፈዋል፣ አንዳንዶችም በአካል የዚያ እኲሪ ታሪክ ለመሆን ትግሉን ተቀላቅለዋል። ትግሉ ፍሬ አፍርቶ በሕዝቦች መፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ ስርዓት ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውም አባላቱ ያደረጉት ትግል በእውነትም ግቡን እንደመታ ማሳያ ነው።

ይሁንና ማሕበራችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሐገራችን እየተስተዋለ ያለው ነገር አሳዛኝም አደገኛም ነው ብሎ ያምናል። ሕዝቦች በሃገራቸው በየትኛውም ክልል በሰላምና በነፃነት የመሥራትና የመኖር መብት እንዳላቸው በሕገመንግሥቱ በግልፅ የተቀመጠ ሆኖ ሳለ ዜጎች በብሄራቸው ምክንያት ብቻ ሲዋከቡ፣ ሲፈናቀሉና ሲገደሉ ማየት እጅግ አሳዛኝና አደገኛም አካሄድ ነው።

ይኽ በእንዲህ እንዳለ ለዘመናት የመቻቻል ተምሳሌት የነበረው ሕዝብ ይኼንን እሴት እንዲያጣው የሚጣጣሩ ሚድያዎች እንዳሉና ነገሩን ከማብረድ ይልቅ የሚያራግቡ ተቋማትም ብቅ ማለታቸው ስናይ ይኽ ክስተት ከእንዲህ ዓይነቱ ብጥብጥ እናተርፋለን ብለው ባቀዱ ኃይሎች የሚነዳ አካል እንዳለ ኣስተውለናል። ስለሆነም ፌደራል መንግሥት የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅ ሐላፊነቱን ይበልጥ ማጠናከር ይኖርበታል ብለን እናምናለን።

ማሕበራችን ኹኔታውን ሲከታተለው ቢቆይም መግለጫ ከማውጣት የተቆጠበው የነበረው የሁኔታ ሲዘገብበት የነበረው መንገድ ብዥታን የሚፈጥር በመሆኑ ነበር። ይኽም ማለት የተወሰኑ የመንግሥት ሚድያዎችም የችግሩ ኣካል እስኪመስሉ ድረስ መወዛገባቸው፣ በውጭ ያለው ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ የሚያገኘው መረጃም ካልተረጋገጡ የማሕበራዊ ሚድያ ግብኣቶች ወደመሆን ስላደላ ነበር።

አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከሁሉም በፊት የዜጎች ደኅንነት እንዲያስጠብቅ ፌደራል መንግስቱን እናሳስባለን፣ የየክልሉ መንግሥታትም በክልላቸው ያሉትን ኢትዮጵያውያን ደኅንነት እንዲያስጠብቁ፣ ፌደራል ስርዓቱ በመፈቃቀድ የቆመ ቃል ኪዳን ነውና ክልሎች በማንኝውም ኢትዮጵያዊ ላይ የባዕድነት ስሜት የሚፈጥሩ አላስፈላጊ አካሄዶች ሲከሰቱ በየደረጃው ማስተካከያ እርምጃ እንዲወስዱ እንዲያ ሲልም ከፌደራል መንግሥት ጋር በመሆን አፋጣኝ መፍትሔ እንዲያበጁ እንጠይቃለን።

የዜጎች ደኅንነት አደጋ ላይ የሚጥል አካሄድ በተስፋ የምናየውን የልማትና ለውጥ ጅማሬ የሚያቀጭጭ ነውና በጥልቅ ሊታሰብበት ይገባል። በዚህ የማስተካከያ ሂደት የመገናኛ ብዙኃን፥ የእምነት ተቋማትና የአገር ሽማግሌዎች የታሪካችን አኩሪ አካል በሆነው የመተሳሰብና የመቻቻል እሴት ላይ አተኩረው እንዲሰሩ ማሕበራችንም በሚያደርጉት ጥረት ሁሉ ከጎናቸው እንደሆነ ይገልፃል።

ዲሞክራስያዊ ፌደራላዊ አንድነት ብዝኃነትን ማስተናገድ የሚችል የእድገትና የጥንካሬ እንዲሁም የመግባባት ምንጭ እንጂ የስጋት ምንጭ ኣይደለም !!!
**********
ማሕበር ተጋሩ ኣውሮፓ (በአውሮፓ የትግራይ ተወላጆች ማሕበር)
ጥቅምት 27፣ 2010 ዓም
[email protected]

Guest Author

more recommended stories