የአዲስ አበባ ከተማን ህዝብ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብት የሚጥስ አዋጅ አጥብቀን እንቃወማለን! (ከሰማያዊ ፓርቲ ብሔራዊ ሸንጎ የተሰጠ መግለጫ)

የኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲ በቅርቡ ለፓርላማ የቀረበውን የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ከተማ ላይ ያለውን ልዩ ጥቅም ለመወሰን የወጣ አዋጅ ረቂቅ ሰነድ አስመልክቶ መግለጫ አወጣ።

የኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲ ያወጣው መግለጫ እንዲህ ይነበባል። 

Photo - Semayawi party Yilkal Getnet
Photo – Semayawi party Yilkal Getnet

የአዲስ አበባ ከተማን ህዝብ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብት የሚጥስ አዋጅ አጥብቀን እንቃወማለን!!!

ከሰማያዊ ፓርቲ ብሔራዊ ሸንጎ የተሰጠ መግለጫ

ህወሀት/ኢህአዴግ በ100 ፐርሰንት አሸንፊያለሁ ብሎ ባወጀ ማግስት በመላ ሀገራችን በሁሉም አቅጣጫ እንደየአካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ የነፃነት፣ የእኩልነትና የዴሞክራሲ ጥያቄን በማንገብ የኢትዮጵያ ህዝብ የህይወት መስዋዕትነት እየከፈለ ነው፡፡አገዛዙ ይህንን መሰረታዊ የለውጥ ጥያቄ ለማዳፈን ሲል ለማመን በሚከብድ ሁኔታ አስተዳድረዋለሁ በሚለው ህዝብ ላይ ግድያ፣ የጅምላ እስር እና ማፈናቀል ዋነኛ ተግባሩ አድርጎታል፡፡ በዚህ የአገዛዙ ኢ-ሰብዓዊ እርምጃም ቢሆን የኢትዮጵያን ህዝብ የለውጥ ጥያቄ ማስቆም ባለመቻሉ በድንጋጤና ባልታሰበበት ሁኔታ የኢትዮጵያን ህዝብ ለመከፋፈል እና በጥርጣሬ እንዲተያይ ለማድረግ አዲስ ረቂቅ አዋጅ ይዞ ብቅ ብሏል፡፡

ይህ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ተረቀቀ የተባለው አዋጅ በጥድፊያ የወጣ፣ግልፅነት የጎደለው፣ህገ መንግስቱን የጣሰ፣በመረጃና በጥናት ላይ ያልተመረኮዘ፣አጠቃላይ የዴሞክሰራሲ መርሆና ከህገ መንግስቱ አንቀፅ 49 አላማ ጋር በእጅጉ የተቃረነና ህዝብን ከህዝብ በማጋጨት አገዛዙ የተነሳበትን የፖለቲካ ትኩሳት ለማብረድ በማሰብ የተቀነባበረ ግልብ ሴራ ነው፡፡

አገዛዙ በተቆጣጠራቸው መገናኛ ብዙሃን እንደተገለፀው በዚህ አዋጅ የማርቀቅ ሂደት ላይ የተሳተፉት አካለት የኦሮሚያ ክልል መንግስት፣ኦህዴድ፣የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና ከፍተኛ የመንግስት ሃላፊዎች እንደሆኑ ተገልፅዋል፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ አዲስ አበባን ከሚያስተዳድሩትም ሆነ በፌደራል ፓርላማ 100 ፐርሰንት አሸንፊያለሁ ያለው ኢህአዴግና አጋሮቹ ውስጥ እንደ ድርጅት ኦህዴድ ብቻ መሳተፉና ሌሎች ማለትም ብአዴን፣ደህዴንና ህወሃት እንዳይሳተፉ መደረጋቸው በድርጅቱም ውስጥ ታስቦበትና ሙሉ ስምምነት ተደርሶበት የተዘጋጀ ረቂቅ አለመሆኑን እና ተራ የፖለቲካ ሸቀጥ መሆኑን ግልፅ ማሳያ ነው፡፡

በዚሁ መግለጫ ላይ አንደተገለፀው በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን መስፋፋት ለተፈናቀሉና ወደፊትም ለሚፈናቀሉ ሰዎች ካሳ የሚከፈለው ለኦሮሞ ብሄር ተወላጅ አርሶ አደሮች እንደሆነ ተገልጧል፡፡ ይህም ማለት በዚህ አዋጅ መሰረት በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን መስፋፋት ምክንያት ለሚፈናቀሉ ኦሮሞ ያልሆኑ ኢትዮጵያውያን አርሶ አደሮች ካሳ የማግኘት መብት የላቸውም ማለት ነው፡፡ ይህ አገላለፅ የዜጎችን ተዘዋውሮ የመስራትና ሀብት የማፍራት ህገ መንግስታዊ መብት የሚነጥቅ በመሆኑ ረቂቅ አዋጁ ተቀባይነት የለውም፡፡

የህገ መንግስቱ አንቀፅ 49/5 ዓላማ የአገልግሎት አቅርቦትን፣የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምናን እና የጋራ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን አፈፃፀም የተመለከተ ሲሆን ይህ ተረቀቀ የተባለው አዋጅ ግን ከዚህ አንቀፅ በተቃራኒው ተለጥጦ የአዲስ አበባን ህዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር ህገ መንግስታዊ መብት በመንጠቅ ኦሮሞነትን በላዩ ላይ በመጫንና ተገዶ እንዲቀበል በማድረግ ኦሮሞ ያልሆነው የአዲስ አበባ ህዝብ በገዛ ሀገሩ ባይታወርነት እና እንግድነት እንዲሰማው የሚያደርግ ጨቋኝ አዋጅ ነው፡፡

በዚህ ተረቀቀ በተባለው አዋጅ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የኦሮሚያ ክልል መንግስት ሰራተኞች ተመዝግበው ቤት የማግኘት መብት እንዲከበርላቸው ይደነግጋል፡፡ በመሰረቱ የኦሮሚያ ከልላዊ መንግስት ዋና ከተማ አዳማ መሆኗን በ1994 ዓ.ም የተሸሻለው የክልሉ ህገ መንግስት አንቀፅ 6 ይደነግጋል፡፡ ይህ ሆኖ እያለ ህወሃት/ ኢህአዴግ በ1997 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ አዲስ አበባ ከተማ ላይ በደረሰበት አስደንጋጭ ሽንፈት ምክንያት የወቅቱ የድርጅቱ ሊቀመንበር አቶ መለስ ዜናዊ በምርጫው ማግስት የኦሮሚያ ክልልን ህገ መንግስት በመጣስ በፖለቲካ ውሳኔ የአዳማ ከተማ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማነት መብትን በመንጠቅና ወደ ህዝብ የመቅረብ መሰረታዊ የፌደራሊዝም ፅንሰ ሃሳብ በመጣስ ወደ አዲስ አበባ እንዲዛወር አድርገዋል፡፡ ይህ ውሳኔ የክልሉን ህገ መንግስት ያላከበረ ስለሆነ ሊፀድቅም ሊፈፀምም አይገባም፡፡

በፌደራሉ ህገ መንግስት መሰረት 9 ክልሎችና ሁለት የከተማ አስተዳደሮች እንዳሉ ሲታወቅ አዲስ አበባ በዚህ ህገ መንግስት በአንቀፅ 49/2 መሰረት ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብትና የራሱን የስራ ቋንቋ የመወሰን መብቱ የአዲስ አበባ ህዝብ እና የሚወክላቸው አካላት ብቻ መሆኑ በግልፅ ተደንግጓል፡፡ ይህንን ህገ መንግስታዊ መብት በመጣስ የአዲስ አበባ አስተዳድርን የስራ ቋንቋ የሚወስን አዋጅ በፌደራል መንግስት ማውጣት በራሱ በህገ መንግሰቱ አንቀፅ 9 መሰረት ተቀባይነት የለውም፡፡

ከዚህም በተጨማሪ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኦሮሞኛን የስራ ቋንቋ ማድረግ አዲስ አበባ ተወልደው ያደጉ ኦሮሞ ያልሆኑ ኢትዮጵያውያንን ከስራ እድል በማግለል ኦሮሞ ለሆኑ ኢትዮጵያውያን ቅድሚያ ለመስጠት በማስመሰል በዜጎች መካከል አላስፈላጊ የጥቅም ግጭት እንዲፈጠር የሚያደርግና በህዝብ መካከል ያለውን መስተጋብር የሚንድ መርዘኛ አዋጅ በመሆኑ በፍፁም ተቀባይነት የለውም፡፡

ከላይ በገለፅናቸው ማሳያ ነጥቦች መሰረት ይህ ተረቀቀ የተባለው አዋጅ የህግም ሆነ የሞራል መሰረት የሌለው ስለሆነ በአስቸኳይ አንዲቆምና የኦሮሚያ ክልል መንግስትም የአዳማን የክልል ርዕሰ ከተማነት ህገ መንግስታዊ መብትን በማክበር አሰተዳደሩን ወደ አዳማ እንዲያዛውርና የአዳማ ከተማ በክልሉ ህገ መንግስት የተሰጠውን የክልል ከተማነት መብት ተከብሮ ከዚህ ጋር በተያያዘ የሚገኙ የኢኮኖሚ፣የፖለቲካ እና የማህበራዊ እድገት ተፈፃሚ እንዲሆን በአፅንዖት እንጠይቃለን፡፡

በመጨረሻም ረቂቅ አዋጁ ህወሀት/ኢህአዴግ የኢትዮጵያን መሰረታዊ የህዝብ ጥያዌ ለመመለስ አቅምም ሆነ ፍላጎት እንደሌለው በግልፅ የሚያሳይ ከመሆኑም ባሻገር ለስልጣኔ ይጠቅመኛል ያለውን ሁሉ በህዝብ ላይ ከመፈም ወደኋል እንደማይል ከድርጊቱ ተገንዝበናል፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም የአዲስ አበባ ህዝብ ይህንን ተረቀቀ የተባለውን ከፋፋይና መርዘኛ ረቂቅ አዋጅ ውድቅ እንዲሆን ጥቃቅን ልዩነቶችን በማሶገድ መሰረታዊ ለሆነው ለኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት፣እኩልነትና ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር አውን መሆን ላይ በማተኮር በአንድነት ትግሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

ሰኔ 25 ቀን 2009 ዓ.ም

*********

ማስታወሻ(ከአዘጋጁ):-
ሰማያዊ ፓርቲ ባለፈው መስከረም ባካሄደው ጉባዔ፤ ከምስረታው ጀምሮ ለ4 ዓመታት የመሩትን ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ምትክ የሺዋስ አሰፋን ሊቀመንበር አድርጓል። የሂደቱን አግባብነት እነይልቃል ቢቃወሙትም፤ ምርጫ ቦርድ ግን የየሺዋስን ሊቀመንበርነት አጽድቋል። ይሁን እንጂ እነኢ/ር ይልቃል “የሰማያዊ ፓርቲ ብሔራዊ ሸንጎ” በሚል ስያሜና የሰማያዊ ፓርቲን የፌስቡክ ፔጅ በመጠቀም የተናጥል እንቅስቃሴ ቀጥለዋል።

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories