የአፍሪካ ህብረት ለቀዳማዊ ኃይለስላሴ እና መለስ ዜናዊ ሀውልት እንዲቆምላቸው ወሰነ

29ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ስብሰባ ዛሬ በስኬት ተጠናቋል፡፡ መሪዎቹ በስብሰባው ማጠናቀቂያ ለቀድሞው የኢትዮጵያ ንጉስ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ እና ለቀድሞው የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በአፍሪካ ህብረት መታሰቢያ ሃውልት እንዲቆምላቸው መሪዎቹ ወስነዋል፡፡

ይህ ለኢትዮጵያውያን ታላቅ ድል ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን በየትኛውም ስርዓትና ጊዜ ለአፍሪካውያን ታማኞች መሆናቸውን ያረጋገጠ ውሳኔ ነው፡፡

አፍሪካውያን በመሪዎቻቸው አማካኝነት፣ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲሁም ለአፍሪካ ህብረት መመስረትና መጠናከር የኢትዮጵያ ህዝቦችና መንግስታት በየትውልዱ ላደረጉት አስተዋጽኦ የተሰጠ ክብር ነው፡፡

የኢፌዲሪ መንግስትም ይህ እንዲሆን ተደጋጋሚ ጥረት ሲያደርግ የቆየ ሲሆን በመሳካቱም ደስታውን ይገልጻል፡፡

Photo - Emperor Haileselasie and PM Meles Zenawi
Photo – Emperor Haileselasie and PM Meles Zenawi

ኢትዮጵያና ህዝቦቿ ለትናንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እና ለዛሬው የአፍሪካ ህብረት አላማዎች መሳካት የምንጊዜውም ታማኞች ናቸው፡፡ በዚህ አክብሮትና እውቅና ውስጥ የኢትዮጵያ ህዝቦች አሉ፡፡

በዚህ አክብሮት ውስጥ 50 አመታት ሙሉ የየአገሩን መሪዎች ቆመው መንገድ ላይ በክብር ሲያሳልፉ ከልጅነት እስከ እውቀት ሃላፊነታቸውን የተወጡ አያሌ ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡

ዛሬ በተጠናቀቀው 29ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ስብሰባ ላይ ለቀድሞ የአገራችን መሪዎች ክብርና አስተዋጽኦ ሃውልት እንዲቆምላቸው የተላለፈው ውሳኔ ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያውያን የተሰጠ ሽልማት ነው፡፡

አፍሪካውያን ለኢትዮጵያ ህዝቦች የሰጡት ይህ ክብር ነገንም ይጨምራል፡፡ የዛሬውና የነገው ትውልድ፣ የቀድሞ መሪዎቹ ያገኙት አውቅና ነገ ለምንሰራው አመላካች ሲሆን የምንቀበለውም በከባድ የአደራና የሃላፊነት ስሜት ነው፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ ይህን ከባድ ሃላፊነት ለመወጣት ያላሰለሰ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል ወደፊትም ያደርጋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር

ሰኔ 27 ቀን 2009 ዓ.ም

**********

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories