ነፃነት ለሰው ልጅ የተሰጠ ተፈጥሯዊ ፀጋ ነው። በነፃነት ማሰብ፣ መናገርና መፃፍ የሰው ተፈጥሯዊ ባህሪ፥ የሰውነት (የሰብዓዊነት) መገለጫ ነው። በመሆኑም፣ ነፃነት የሌለው ሰው ሰብዓዊ ክብሩን የተገፈፈ ነው። ሰዎችን በነፃነት ከመኖር፥ ከማሰብ፥ ከመናገር፥ ከመፃፍ፥… የሚያግዱ በሙሉ የሰው ልጅን ተፈጥሯዊ ባህሪ ለመግፈፍ የሚጥሩ ናቸው። የሰው ልጅ የተፈጠረው ከምንም ዓይነት እዳና እገዳ ነፃ ሆኖ ሕይወትን በነፃነት እንዲኖር ነው።
የሁሉም ሰዎች ነፃነት የሚከበረው የእያንዳንዱ ሰው ነፃነት ሲከበር ነው። እያንዳንዱ ሰው ግዴታውን በራሱ ከተወጣ የሁሉም ሰዎች ነፃነት ይከበራል። ነገር ግን፣ አንድ ሰው ግዴታውን በአግባቡ እንዲወጣ “ሌሎች ሰዎች ለእሱ ያለባቸውን ግዴታ በአግባቡ ይወጣሉ” ብሎ ማመን አለበት። ስለዚህ፣ ሕይወትን በነፃነት ለመምራት እያንዳንዱ ሰው ሁሉንም ሰዎች ማመን፣ ሁሉም ሰዎች ደግሞ እያንዳንዱን ሰው ማመን አለባቸው።
ሁሉም ሰው በራሱ ፍላጎትና ምርጫ በሚንቀሳቀስበት፣ በመነሳሳት፣ ለውጥና አደጋ የተሞላ የነፃነት ሕይወት ከፍርሃት ነፃ ሊሆን አይችልም። በዚህ ዓይነት ሕይወት ውስጥ እርስ-በእርስ መተማመን ሊኖር አይችልም። ይህ ያለመተማመን መንፈስ ደግሞ እርስ-በእርስ መፈራራትን ይፈጥራል። ነገር ግን፣ የነፃነት ሕይወት ሁሌም በለውጥና ስጋት የተሞላ ነው።
ምንግዜም ቢሆን ነፃነት ያለው ሰው ነፃነቱን እንዳያጣ ይፈራል። ስለዚህ፣ ሁሉም ሰዉ በራሱ ፍላጎትና ምርጫ በሚንቀሳቀስበት የነፃነት ሕይወት ውስጥ እያንዳንዱ ሰው የሌሎችን እንቅስቃሴ በእርግጠኝነት መገመትና ማወቅ ማወቅ ይፈልጋል። አንድ ሰው ከጎኑ ያለን ሰው እንቅስቃሴ በራሱ ማወቅና መገመት ከተሳነው በውስጡ ያለመተማመን ስሜት ይፈጠራል።
ይህ ያለመተማመን ስሜት “እኔ ለሌሎች ሰዎች ያለብኝን ግዴታ በአግባቡ ብወጣ እንኳን እነሱ ለእኔ ያለባቸውን ግዴታ በአግባቡ ላይወጡ ይችላሉ” ከሚል እሳቤ የመነጨ ነው። ስለዚህ፣ “እኔ የሌሎችን መብት ባከብርም እነሱ ግን የእኔን መብት ላያከብሩ ይችላሉ” የሚል ፍርሃት በውስጡ ይፈጠራል። በዚህ መሰረት፣ በተወሰነ አከባቢ የሚኖሩ ሰዎች ማህበራዊ ግንኙነታቸውን የሚመሩበት የራሳቸው የሆነ ሕግና ሥርዓት ሊኖራቸው የግድ ይላል።
የሕግ ስርዓትን ለመዘርጋት ደግሞ ሦስት አካላት ያስፈልጋሉ። እነሱም፡- ሕግ አውጪ፣ ሕግ ተርጓሚና ሕግ አስፈፃሚ። እነዚህ ሦስት አካላት በጥምረት “መንግስት” ይባላሉ። የእነዚህ አካላት ድርሻና ኃላፊነት በግልፅ ተለይቶ የሚቀመጥበት የውል ሰነድ “ሕገ-መንግስት” ይባላል። በዚህ መልኩ የተወሰነ ጂኦግራፊያዊ ክልል ያለውና በአንድ መንግስት አስተዳደር ስር የሚገኝ ግዛት ደግሞ “ሀገር” ይባላል። በዚህ መልኩ፣ በአንድ የተወሰነ አከባቢ የሚኖሩ ሰዎች ነፃነትን ለማረጋገጥ እና ፍርሃትን ለማስወገድ ከእያንዳንዳቸው የበለጠ ኃይል ያለው መንግስት ፈጠሩ።
“የመንግስት ስልጣን” ማለት የዜጎችን ነፃነት እንዲያስከብር ከእያንዳንዱ ግለሰብ ላይ ተቆርሶ የተሰጠ መብት ነው። ምክንያቱም፣ እያንዳንዱ ዜጋ፤ አንደኛ፡- የሌላውን መብት ሳይነካ የፈለገውን ነገር እየሰራ፣ እየተናገረና እየፃፈ በሰላም በሀገሩ እንዲኖር፣ እና ሁለተኛ፡- በባዕድ ሀገር መንግስት ወይም በሌላ ሰው በኃይል ተገዢ እንዳይሆን ጥበቃና ከለላ እንዲያደርግለት ራሱን በራሱ የማስተዳደርና የመምራት መብቱን ለመንግስት በውክልና ሰጥቶታል። ስለዚህ፣ መንግስት ለዜጎች ነፃነት ጥበቃ የማድረግ ግዴታ እንጂ ነፃነታቸውን ለመገደብ የሚያስችል ስልጣን አልተሰጠውም።
በመሰረቱ ፍርሃትን ለማስወገድ የተፈጠረ አካል ሌላ ፍርሃት መፍጠር የለበትም። የሰው ልጅ ነፃነቱን ለማረጋገጥ ሲል ከነፃነቱ ላይ ቀንሶ የፈጠረው መንግስት ራሱ መልሶ ነፃነቱን ሊነፍገው አይገባም። መንግስት የዜጎችን ነፃነት የሚነፍግ ከሆነ የተፈጠረበት ዓላማ ስቷል። ተፈጥሯዊ ዓላማውን የሳተ ነገር ሁሉ ፋይዳ-ቢስ ነው። እንደዚሁም የዜጎችን ነፃነት የሚነፍግ መንግስት ፍይዳ-ቢስ ነው።
የመንግስት ሕልውና የተመሰረተው የዜጎችን መብትና ነፃነት በማክበርና በማስከበር ላይ ነው። የዜጎች መብትና ነፃነት የሚረጋገጠው ደግሞ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ነው። ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲኖር ከላይ የተጠቀሱት ሁሉም የመንግስት አካላት፡- ሕግ አውጪዎች፣ ሕግ ተርጓሚዎች እና ሕግ አስፈፃሚዎች ሥራና ኃላፊነታቸውን ነፃና ገለልተኛ በሆነ መልኩ መወጣት አለባቸው። እነዚህ የመንግስት አካላት ሥራና ኃፊነታቸውን በነፃነት መወጣት ከተሳናቸው ግን የዜጎችን መብትና ነፃነት ማክበርና ማስከበር አይቻልም።
ፍርሃት በነገሰበት ሀገር በነፃነት ማሰብ ወንጀል ይሆናል፣ በነፃነት መናገር ከአመፅ ይቆጠራል፣ በነፃነት መፃፍ ለእስርና ስደት ይዳርጋል። የሀገሪቱን ዜጎች በነፃነት ከመኖር፥ ከማሰብ፥ ከመናገርና ከመፃፍ የሚያግድ መንግስት ከእድገት ይልቅ ውድቀትን የመረጠ ነው። እንደ ፈረንሳዊው ልሂቅ “Montesquieu” አገላለፅ፣ የዜጎችን መብትና ነፃነት በአግባቡ ማረጋገጥ የተሳነው መንግስታዊ ሥርዓት ተንኮታኩቶ ይወድቃል፡-
“The political liberty of the subject is a tranquility of mind arising from the opinion each person has of his safety. In order to have this liberty, it is requisite the government be so constituted as one man need not be afraid of another. When the legislative and executive powers are united in the same person, or in the same body of magistrates, there can be no liberty; … Again, there is no liberty, if the judiciary power be not separated from the legislative and executive. …As all human things have an end, the state we are speaking of will lose its liberty, will perish. Have not Rome, Sparta, and Carthage perished?” Baron de Montesquieu, The Spirit of Laws, trans. Thomas Nugent, 2 vols. Part 1: page151–162.
*********
ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል
የኦሮሞ ህዝብ ከሀገራችን ህዝቦች መካከል ከዬትኛዉም ብሔር በላይ ከሌሎች ብሄረሰቦች ጋር ተፋቅሮ፣ ተከባብሮ፣ ተጋብቶና ተዋልዶ በመኖርና በታጋሽነት ልዩ ባህሪዉ ይታወቃል፡፡
የኦሮሞ ሕዝብ ጎረቤት ከሆነው የሱማሌ ህዝብ ጋርም እንደ ማንኛውም የኢትዮጵያ ህዝቦች በጉርብትና ከሌሎች ብሄሮች በተሻለ ተቀራርቦና ተግባብቶ በጋብቻም ይሁን በንግድ ተሳስሮ ለዘመናት አብሮ ኖሯል፤ ለወደፊትም ይኖራል፡፡
ይህን ፅሁፍ ለመፃፍ ያነሳሳኝ አቶ ኢስማኢል መሀመድ አብዲ በJigjiga Herald ላይ የኦሮሞ ህዝብ መሪ ድርጅት የሆነዉን የኦህዴድንና የክልላዊ መንግስቱን ስም በማጥፋት እንዲሁም የሱማሌና የኦሮሞን ብሄሮች ግጭት ለማባባስ ሰሞኑን በተከታታይ እየፃፈ በመልቀቅ ላይ ያለው የተዛባ ፅሁፍ በተመለከተ ህዝቡ እውነታውን እንዲረዳ ተጨባጭ መረጃ ለመስጠት ነው፡፡
ፀሐፊው የኦሮሞ ህዝብ ወራሪ ነው ወረራውን ከዚህ ቀደም የጀመረና ወደፊትም የሚቀጥል ነው የሚለው ስለኦሮሞ ማስተዋል የጎደለውና ለብሄሩም ምንም ክብር የሌለው መሆኑን በተጨባጭ ያሳያል፡፡
እረ ለመሆኑ ኦሮሞ ሶማሌን እየወረረ ነው የሚለው መቼ ይሆን? በሪፈረንደም ህዝበ-ውሳኔ ወደ ኦሮሚያ በተካለሉ ወረዳዎች በከባድ መሳሪያና በልዩ የፖሊስ ሀይል ገብቶ አርሶ አደሮችና ኣርብቶ አደሮችን እየገደለ፤እየደበደበ፤ንብረቱን እየዘረፈ ያለው ማን ሆነና? ሀቁ ቀኑን ጠብቆ ይጋለጣል፡፡
ኦሮሞ ከጀርባው በሚያደራጀውና በሚያንቀሳቅሰው ሃይል የትኛውን የሶማሌ ወረዳ ወረረ? እስቲ ንገሩኝ?
ሀቁ በክልላችን ዜጎች ላይ እልቂት እያደረሰ ያለዉ በሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት አብዲ ኢሌ የሚመራውና ከፍተኛ የጦር መሳሪያ የታጠቀዉ የሶማሌ ልዩ ፖሊስ ነው፡፡
የአብዲ ኢሌና የሶማሊያ ልዩ ፖሊስ ሀይል ዋንኛ አላማ የዚያድ ባሬን ፖሊሲና ሌጋሲ ማሳካት እንደሆነ የኢትዮጵያ ህዝብ ሊረዳው ይገባል፡፡
ዚያድ ባሬ በ1969 ሀገራችንን ሲወር ዋንኛ አላማዉ ከአዳማ ጀምሮ ምስራቅና ምዕራብ ሀረርጌን ፤የባሌንና የጉጂን፤ የቦረናን ቆላማ ወረዳዎችንና የሱማሌ ክልልን ከዋናዋ ሶማሊያ ጋር ቀላቅሎ ታላቋን ሶማሊያን መመስረትና ኢት/ያን ማፈራረስ ነበር ፡፡
ይህ ድብቅ አጀንዳ የሰፊው የሱማሌ ክልል ህዝብ ፍላጎት ሳይሆን የአብዲ ኢሌና የልዩ ፖሊሱ መሆኑ መታወቅ አለበት፡፡ ይህንን ተጨበጭ እዉነታ መላው የኦሮሞ ህዝብና የኢትዮጵያ ህዝቦች በደንብ ይረዱታል፡፡
የኦሮሞ ህዝብ ወደ ፊትም ከሶማሌ ህዝብ ጋር እንደ ከዚህ ቀደሙ በወዳጅነትና በወንድማማችነት አብሮ መኖሩን ይቀጥላል፡፡
ልዩ ፖሊስን ወደ ኦሮሚያ እየላከ ሠላማዊ ዜጎችን እያስፈጨፈ ካለው የክልሉ ፕሬዝዳንት አብዲ ኢሌና ከልዩ ፖሊሶች ጋር ግን መቼውንም ቢሆን የማይታረቅና ታሪካዊ ጠላቶቹ መሆናቸዉን በግልፅ ማስረዳት ያሻል፡፡
በአጠቃላይ የዚያድ ባሬ ርዝራዥ የሆኑት አቶ አብዲ ኢሌና ልዩ ፖሊስ ህዝባችንን እርስ በርስ ለማጋጨት የሚጥሩ ኪራይ ሰብሳቢዎች ናቸው፡፡
አላማቸዉና ግባቸዉ በሶማሊያ ከሚንቀሳቀሰው አልሸባብ የተለየ አይደለም፡፡
ኦሮሞ ሶማሌን እየወረረ ነው የሚለው በእውኑ ሶማሌ የተሻለ ምጣኔ ሀብት ኖሮት ነዉ? ቅዠት ካልሆነ በስተቀር ኦሮሞ የክልሉንም ሀብት ለሌሎች አካፍሎ አብሮ እየኖረ ስለመሆኑ ከበቂ በላይ መረጃ ማቅረብ ይቻላል፡፡ እንኳንስ የሌላ ክልል መሬት መውረር ይቅርና ሌላውንም አስጠግቶ የሚኖር ነዉ፡፡ ከ5 ሚሊየን የማያንስ የሌላ ብሄር ተወላጅ የሚኖርበት በኢት/ያ ብቸኛዉ ክልል ኦሮሚያ መሆኑን እወቀዉ ላንተም ይጠቅምሃል፡፡
የኦሮሞ ሕዝብ ከልማታዊ መንግስቱ ጎን በመቆም በሀገሪቱ እየተካሄዱ ላሉ ከ80% በላይ የኢንቨስትመንት ስራዎች ቅድሚያ በመስጠት መሬቱን እየለቀቀና ልማቱን እየደገፋ ያለ ህዝብ ነው፡፡
የኦሮሞ ህዝብ ቻይ፣ በባህሉም ሠላም ፈላጊ፣ አስታራቂ እንጂ ሽብርተኛ አይደለም፡፡ እንደዚያማ ቢሆን ኖሮ ይህቺ ሀገር አንድ ቀን አታድርም፤ ብትንትኗ ይወጣ ነበር፡፡
ምንም ህልም የሌላቸው አንዳንድ የፈረንጅ ጥገኞችና ለማኞች ግን ይህንን ኩሩ ሕዝብ የማይሆን ስም እየሰጡ ሊያሸማቅቁት ይሞክራሉ፡፡
ሌላው opdo is the real enemy of federalism ብሎ በፃፈው ፅሁፍ መሪ ድርጅታችን የሌለውን ስም በመስጠት ስሙን ለማጉደፍ የፃፈው ጽሑፍ የዚሁ መገለጫ ነዉ፡፡
መሪ ድርጅችን ኦህዴድ በዚህ ሀገር ውስጥ የህዳሴ ጉዞ እንዲሳካ፤ በሀገራችን የሰላም፤ የልማትና የዴሞክራሲ ጅምሮች ከዳር ደርሰው ሀገራችን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ እንድትሰለፍ የፌዴራሊዝም ስርዓት እንዲጠናከር፤ ሀገራችንን ወደ ከፍታ የሚያመሩና የህዝባችንን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ተግባራዊ በማድረግ የህዝባችን የኑሮ ሁኔታ እንዲለወጥ ከፍተኛ ትግልና መስዋትነት እየከፈለ ያለ ድርጅት ነው፡፡ ጥገኛ ሀይሎች ጥላሸት ለመቀባት የሚያደርጉት ሙከራ ከንቱ ነዉ፡፡
“የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) የፌደራሊዝም ጠላት ነው” በማለት ፀሐፊው ላሰፈረው ጽሑፍ ሰዉዬዉ መጀመሪያ ፌደራሊዝም ምን ማለት እንደሆነ ትርጉሙን ያልተረዳ፣ የራሱን የልብ ትርታ ብቻ እያደመጠ ለመኖር የሚፈልግና ለፍትህና ለእኩልነት ቦታ የሌለው ጠባብ መሆኑን ያሳያል፡፡
ፌደራሊዝም የፍላጎት መዋጮ እንጂ በግድ የሚጫን ሸክም አለመሆኑን ለፀሐፊው ማን በነገረዉ? መጀመሪያ ት/ቤት ገብቶ ቢማር ይሻለው ነበር፡፡ ያም ሆነ ይህ ፌደራሊዝም የፍትህና የእኩልነት መገለጫ እንጂ የጌታና የሉሌ ሥርዓት መገለጫ አይደለም፡፡ ይህንን ደግሞ ማንም ዛሬ ተነስቶ ለኦሮሞ ህዝብና ለኦህዴድ ማስተማር አይችልም፡፡ እንዲያውም ለፌዴራሊዝም ከፍተኛ መስዋትነት እያከፋፈለ ያለው የኦሮሞ ህዝብ ነው፡፡
ህዝቡም ሆነ ድርጅቱ የመቻቻል፣ የትዕግስትና የሠላም ቁንጮዎች ናቸው፡፡ ይህንን ከታሪክ ተረዳ፡፡ ሲጀመር ፌደራሊዝም ከማንም በላይ የሚጠቅመዉ ኦሮሞን ነዉ፡፡ ዳሩ ግን እኛ ጋር በፌደራሊዝም ሥም ብዙ ተነግዶበታል፡፡ ሐቀኛ ፌደራሊዝም ኦሮሞን ይጠቅመዋል እንጂ አይጎዳውም፡፡ እየገነባን ያለነዉ ትክክለኛዉና የህዝቦችን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ያስከበረና ብዝሃነትን በአግባቡ ማስተናገድ የቻለ ነዉ፡፡ ለዚህ ስርዓት ግንባር-ቀደም ተሟጋቾች የኦሮሞ ህዝብና መሪ ድርጅቱ መሆናቸዉን አመለካከታቸዉ የተንሸዋረረባቸዉ ሁሉ ሊረዱት ይገባል፡፡