ብሔራዊ መግባባት ወይስ ግራ-መጋባት?

የሕወሃት/ኢህአዴግ መስራችና ከፍተኛ አመራር አቦይ ስብሃት ነጋ ከአዲስ ዘመን ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ ከተለመደው ወጣ ያለና በገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ ላይ ጠንከር ያለ ትችት የሰነዘሩበት ነው። አቦይ ስብሃት ከሁሉም ባለስልጣናት በተለየ ሃሳባቸውን በነፃነት ሲገልፁ በተደጋጋሚ ይስተዋላል። አሁንም የገዛ ፓርቲያቸውን ልክ-ልኩን ነገሩት እኮ! መቼም እንደሳቸው የተሰማውን በነፃነት መናገር የማይሻ ሰው ይኖራል ብዬ አላስብም። ይሁን እንጂ፣ አሁን ባለው ሁኔታ ልክ እንደ እሳቸው በነፃነት ወይም በድፍረት ለመናገር የሚደፍር ሰው መኖሩን እጠራጠራለሁ። በእርግጥ “ከሁላችንም በተሻለ ኢህአዴግን ያለ ስጋት የመተቸት ዕድል ያለው እሳቸው ብቻ ናቸው” ብል ማጋነን አይሆንም።

ይህ ፅኁፍ አቦይ ስብሃት “ለእኔ ብሔራዊ መግባባት ያለ አይመስለኝም። አሁን ላይ ያለው ትምክህት፣ ጠባብነት እና አክራሪነት ነው” በማለት በሰጡት አስተያየት ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው። በእርግጥ እሳቸው እንዳሉት በሀገራችን ብሔራዊ መግባባት የለም። ነገር ግን፣ ብሔራዊ መግባባት እንዳይኖር ያደረገው ዋና ምክንያት ምንድነው? አቦይ ስብሃት የጠቀሱዋቸው የትምክህት፣ ጠባብነት እና የአክራሪነት አመለካከቶችን ከብሔራዊ መግባባት አለመኖር ጋር ተያያዥነት አላቸው? እነዚህንና ሌሎች ተያያዥ ጥያቄዎችን እንደሚከተለው ለመዳሰስ እሞክራለሁ።

በመሰረቱ በአንድ ሀገር ብሔራዊ መግባባት ሊኖር የሚችለው በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ የሆነ አቋምና አመለካከት ሲኖር ነው። ለዚህ ደግሞ በተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ዘንድ በሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ግልፅና ነፃ የሆነ ውይይት በማድረግ የጋራ ግንዛቤ ሊፈጠር ይገባል። በመሆኑም፣ ብሔራዊ መግባባት እንዲኖር ዜጎች በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት የሚያደርጉበት፤ ሃሳብ የሚለዋወጡበት፣ እምነትና አመለካከታቸውን የሚያንፀባርቁበት፣ ያሏቸውን ጠቃሚ ልምዶች፥ ዕሴቶችና ባህሎች የሚጋሩበት…ወዘተ፣ ከፖለቲካዊ ወገንተኝነት የፀዳ የጋራ የሆነ መድረክ ሊኖራቸው ይገባል።

ይህ ካልሆነ በሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የጋራ የሆነ ግንዛቤ በዜጎች ዘንድ መፍጠር አይቻልም። በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በቂ የሆነ ግንዛቤ የሌላቸው ዜጎች ብሔራዊ መግባባትን በሚያሳይ መልኩ የጋራ አቋምና አመለካከት እንዲያንፀባርቁ መጠበቅ “ላም ባልዋለበት…” የሚሉት ዓይነት ነው። ስለዚህ፣ በሀገራችን ብሔራዊ መግባባት ላለመኖሩ በዋና ምክንያትነት ሊጠቀስ የሚገባው ነገር ነፃና ገለልተኛ የሆነ የውይይት መድረክ አለመኖር ነው።

በተመሣሣይ፣ እንደ ትምክህት፥ ጠባብነትና አክራሪነት ያሉ ፅንፈኛ አመለካከቶች በሀገሪቱ ውስጥ እንዲስፋፉ ያደረገው ነፃ የውይይት መድረክ አለመኖሩ ነው። በተለይ ባለፉት 25 ዓመታት፤ ስለ ብሔራዊ አንድነትና የቀድሞ ታሪክ የሚናገሩትን ወገኖች “ትምክህተኞች”፣ የብሔርተኝነትና እኩልነት ጥያቄ የሚያነሱትን ወገኖች ደግሞ “ጠባቦች”፣ እንዲሁም ስለ ሃይማኖትና እምነት ነፃነት የሚጠይቁትን “አክራሪዎች” ብሎ በጅምላ በመፈረጅ ያላቸውን የተለየ ሃሳብና አመለካከት በነፃነት እንዳያንፀባርቁ ተደርገዋል።

ነገር ግን፣ ሃሳብና አመለካከታቸውን በነፃነት የሚያንፀባርቁበት የጋራ መድረክ አለመኖሩ ወይም መነፈጋቸው ይበልጥ ፅንፈኛ እየሆኑ እንዲሄዱና ይህንንም ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በማህብረሰቡ ውስጥ ለማስረፅ ጥረት እንዲያደርጉ አድርጓቸዋል። ከዚህ በተጨማሪ፣ በውይይት ያልዳበረና በምክንያታዊ ዕውቀት ላይ ያልተመረኮዘ ግንዛቤ የሌለው ማህብረሰብ ለፅንፈኛ አመለካከቶች ተጋላጭ ቢሆን ሊገርመን አይገባም። ስለዚህ፣ ከብሔራዊ መግባባት በተጨማሪ፣ ለትምክህት፥ ጠባብነትና አክራሪነት አመለካከቶች በሀገሪቱ እንዲስፋፉ በዋና ምክንያትነት ሊጠቀስ የሚገባው ነገር በድጋሜ ነፃና ገለልተኛ የሆነ የውይይት መድረክ አለመኖሩ ነው።

ከላይ በዝርዝር ለመጥቀስ እንደተሞከረው፣ ለብሔራዊ መግባባት መጥፋት እና ለትምክህት፥ ጠባብነትና አክራሪነት መፈጠር ዋና ምክንያቱ ነፃና ገለልተኛ የሆነ መድረክ አለመኖር ነው። ነፃና ገለልተኛ የሆነ የውይይት መድረክ እንዲኖር ደግሞ በቅድሚያ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ያለ ምንም መሸራረፍ ሊከበር ይገባል። ምክንያቱም፣ ስለ ራሱ ችግር በግልፅ ለመናገር የሚፈራ ሰው ስለ ሌሎች ሰዎች ችግር ለመስማት ፍላጎት አይኖረውም። ስለ ራሱ መብትና ነፃነት መከበር በግልፅ ለመናገር ዕድል የሌለው ዜጋ ስለ ሀገር አንድነትና ልማት እንዲናገር መጠበቅ “የራሷ እያረረባት የሰው ታማስላለች” የሚሉት ዓይነት ይሆናል።

በፅሁፉ መግቢያ ላይ የሕወሃት/ኢህአዴግ ከፍተኛ አመራር የሆኑት አቦይ ስብሃት ነጋ “ከሁላችንም በተሻለ ኢህአዴግን ያለ ስጋት የመተቸት ዕድል ያላቸው እሳቸው ብቻ ናቸው” ብዬ ነበር። ነገር ግን፣ እንደ ችግር ለጠቀሷቸው የብሔራዊ መግባባት አለመኖር ሆነ ለትምክህት፣ ጠባብነት እና አክራሪነት አመለካከቶች መስፋፋት ዋናው ምክንያት አብዛኞቻችን ልክ እንደ እሳቸው የመናገር ነፃነት ማጣታችን ነው። ስለዚህ ችግሮቹ ዘላቂ መፍትሄ የሚያገኙት እኛም እንደ እሳቸው ሃሳብና አመለካከታችንን በነፃነት መግለፅ ስንችል ነው።

እኔም ሆንኩ ሌሌሎች ልክ እንደ አቦይ ስብሃት የራሳችንን የፖለቲካ አቋምና አመለካከት፥ የወደፊት ተስፋና ስጋት በመንግስት ሚዲያዎች ላይ ያለ ፍርሃት የማንፀባረቅ ዕድል ሊኖረን ይገባል። ይሁን እንጂ፣ እንኳን እንደ እኔ ያለው ተራ ፀኃፊ ቀርቶ ሌሎች ከፍተኛ ባለስልጣናት ራሳቸው ከተለመደው የፓርቲ አቋም ትንሽ ወጣ ያለ ሃሳብና አስተያየት ለመስጠት ድፍረት/ነፃነት ያላቸው አይመስለኝም።

በአጠቃላይ፣ እርስ-በእርስ ለመነጋገር ሁላችንም እኩል የመናገር ነፃነት ሊኖረን ይገባል። እኩል ካልተነጋገርን አንግባባም፤ እኛ ካልተግባባን ብሔራዊ መግባባት አይኖርም። የተለያየ ቋንቋ፣ ባህል፣ ታሪክ፣ እምነት፣ ሃይማኖት፣…ወዘተ ያላቸው ብሔሮች፥ ብሔረሰቦችና ህዝቦች፣ የተለየ የፖለቲካ ልምድ፣ አቋምና አመለካከት ያላቸው የፖለቲካ ልሂቃን በነፃነት የሚነጋገሩበት የጋራ መድረክ በሌለበት እንዴት መግባባት ይቻላቸዋል?

ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ባልተከበረበት ሀገር፤ “በማያዳምጡ ተናጋሪዎች” እና “በማይናገሩ አድማጮች” መካከል ሊኖር የሚችለው ብሔራዊ መግባባት ሳይሆን “ግራ-መጋባት” ነው። መደማመጥ በሌለበት መነጋገር ራስንና ሌሎችን ግራ-ከማጋባት የዘለለ ፋይዳ የለውም።

አቦይ ስብሃትን ጨምሮ ሁላችንም ብሔራዊ መግባባት እንጂ ግራ-መጋባትን የምንሻ አይመስለኝም። አሁን ላይ በግልፅ እንደሚስተዋለው ግን በሀገራችን ብሔራዊ መግባባት የለም። እርስ-በእርስ ተነጋግሮ ከመግባባት ይልቅ ሳይደማመጡና ሳይነጋገሩ በባዶ በሚጯጯሁ ሰዎች መካከል ምን ዓይነት መግባባት ሊኖር ይችላል?

አሁን በሀገራችን ያለው ሁኔታ ከግራ-መጋባት በስተቀር ለብሔራዊ-መግባባት ፍፁም አመቺ አይደለም። በሕገ-መንግስቱ መሠረት ዜጎች ሃሳብና አመለካከታቸውን ያለ ማንም ጣልቃ-ገብነት የሚገልፁበት ነፃና ገለልተኛ የሆነ መድረክ በመፍጠር፤ ብሔራዊ መግባባት እንዲሰፍን፣ ብሎም እንደ ትምክህት፥ ጠባብነትና አክራሪነት ያሉ ፅንፈኛ አመለካከቶች በሕብረተሰቡ ውስጥ እንዳይስፋፉ ለማድረግ ስር-ነቀል የሆነ ለውጥ ያስፈልጋል። ገዢው ፓርቲ ይህን ደረጃ ስር-ነቀል ለውጥ ለማምጣት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማድረግ እስካልጀመረ ድረስ በሀገራችን ላይ ከብሔራዊ መግባባት ይልቅ ግራ-መጋባት ጥላውን እንዳጠላ ይቀጥላል። ስለዚህ ጥያቄው “ብሔራዊ መግባባት ወይስ ግራ-መጋባት?” የሚል ነው።

*********

Seyoum Teshome is a Lecturer at Ambo University Woliso Campus and head of Management Department. He was born in Arsi, Assela, in 1979 and studied Management at Harameya University and MBA at Mekelle University. He also blogs at http://ethiothinkthank.com

more recommended stories