የH1N1 ኢንፍሉዌንዛ ቫይረስ በአዲስ አበባ አራት ለሞት ዳረገ

የH1N1 ኢንፍሉዌንዛ ቫይረስ በአዲስ አበባ ያለውን ቀዝቃዛ አየር ተከትሎ መከሰቱን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

በተለምዶ የአሳማ ጉንፋን በሚባለው የኢንፍሉዌንዛ ቫይረስ እስካሁን 32 ተጠቂዎች የተገኙ ሲሆን አራቱ ለሞት ተዳርገዋል፡፡

የኢፌዴሪ የጤና ሚኒስቴር በጉዳዩ ላይ ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጠ ሲሆን በመግለጫው ላይ አቶ አህመድ ኢማኖ ፡ ዶ/ር ዳዲ ጂማ እና ዶ/ር መራዊ አራጋው በH1N1 ኢንፍሉዌንዛ ክስተት እና የመከላከል ቅድመ ጥንቃቄ ላይ ማብራሪያ አቅርበዋል።

የH1N1 ወረርሽኝ እ.ኤ.አ. ከ2009 ጀምሮ በአዲስ መልክ በሰወች ላይ የመጣ ሲሆን በወቅቱ በአለም ጤና ድርጅት አለም አቀፍ ወረርሽኝ ተብሎ ታውጆ ነበር፡፡ ወረርሽኙ በጊዜው በሌላው አለም ጉዳት ካደረሰ በሁዋላ ክትባት ተሰርቶለት በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡

ጉንፋኑ በተለያዩ ሀገራት በቅዝቃዜ ወራት የሚነሳ ሲሆን በሰሜን ንፍቀ ክበብ ከህዳር-ሚያዝያ፤በደቡብ ከሚያዝያ-መስከረም፤ ለምድር ወገብ በቀረቡ አካባቢዎች ግን በየትኛውም ወራት ይነሳል፡፡ በበሽታው ከመጠቃት በፊት በሚሰጡ አመታዊ የጉንፋን ክትባቶች ወይም ከተጠቁ በሁዋላ በሚሰጥ የጉንፋን ህክምና መከላከል የተቻለ ሲሆን የጉንፋኑ አደገኝነት መጠንም ወርዷል፡፡

Photo - Ministry of Health officials

በH1N1 ኢንፍሉዌንዛ ላይ በጤና ሚኒስቴር ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ከተገለፁት ነጥቦች ዋና ዋናዎቹ፦

* በአለም ላይ በአመት 3-5 ሚልየን ሰወች በኢንፍሉዌንዛ የሚጠቁ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ወደ 500ሺህ ያህሉ ለሞት ይዳረጋሉ። ለሞት የሚዳረጉትም በተለይ ከ 65 አመት በላይ የሆኑ አረጋውያን፣ ከ 2 አመት በታች የሆኑ ህፃናት እና በጉንፋኑ የሚባባስ የጠና የውስጥ ደዌ ያለባቸው ናቸው።

* በሀገራችን በአሁኑ የአየር ፀባይ ወቅት በላብራቶሪ ያረጋገጥናቸው 32 ተጠቂዎች አሉ። ከእነዚህ ውስጥ 4ቱ የሳምባ እና የስኩዋር አይነት የጠና በሽታ ያለባቸው በመሆኑ እንደሞቱ ታውቋል።

* የበሽታው መተላለፊያ መንገድ የአጭር ርቀት የትንፋሽ ልውውጦችና የአፍንጫ ፈሳሽ ንክኪዎች ሲሆን የበሽታው ምልክቶችም እንደ ማንኛውም ጉንፋን ቢሆኑም ጠንከር ያሉ ሊሆኑ ይችላሉ። የመከላከያ መንገዶቹም እንደ ማንኛውም ጉንፋን በማስነጠስ ወቅት መጠንቀቅ እና እጅን በተደጋጋሚ መታጠብ የመሳሰሉት ናቸው።

* እንደዚህ አይነት ህመም ሲያጋጥም እረፍት ማድረግና ብዙ ፈሳሽ መውሰድ፤ ህመሙ ተባብሶ የመተንፈሻ ችግር ካጋጠመ እና ትኩሳቱ ከሶስት ቀናት በላይ ከቆየ የህክምና እርዳታ ማግኘት ያስፈልጋል።

* የጤና ባለሙያዎች በሌላው ግዜ ከሚተገብሩት የጥንቃቄ ስርአት Standard Infection Prevention Protocol የተለየ ልዩ ጥንቃቄ የማያስፈልግ መሆኑን ተረድተው ሳይረበሹ ተግባራቸውን መከወን ይገባቸዋል።

* በዚህ በሽታ ዙርያ በአዲስ አበባና አካባቢዋ ባሉ የጤና ተቋማት የግንዛቤ ማስጨበጫና የአቅም ማጎልበት ስራዎች ተሰጥተዋል።

* ለዚህ በሽታ የሚሆኑ የመመርመሪያ ኬሚካሎች በሽታው ከጀመረበት ግዜ ጀምሮ ላሉት 6 አመታት አሉን።

* በየግዜው ለሚፈጠሩ አዳዲስ ክስተቶች ከምናደርገው የላብራቶሪ አቅም ግንባታ በተጨማሪ ከአሜሪካው የጤና ማእከል (ሲዲሲ-አትላንታ) ጋር አጋርነት መስርተን የደም ናሙናዎችን ለተጨማሪ ምርመራ እንልካለን። የዚህ የኢንፍሉዌንዛ በሽታ የደም ናሙናዎችንም ለተጨማሪ ምርመራ ልከን ውጤት እየጠበቅን ነው።

* የኢንፍሉዌንዛውን መከስት መጀመሪያ የተዘገበው በሆርን አፌርስ መሆኑ ይታወሳል፡፡
***********

Fetsum Berhane is an Ethiopian resident, economist researcher and a blogger on HornAffairs.

more recommended stories