በትግራይ የብረታ ብረት ማቅለጫና ሌሎች 15 ፋብሪካዎች ሊገነቡ ነው

የብረታ ብረት ማቅለጫን ጨምሮ 15  የማምረቻ ፋብሪካዎችን በተለያዩ አካባቢዎች ለማስገንባት ዝግጅት ማጠናቀቁን የትግራይ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ   አስታወቀ። ለግንባታው 1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ካፒታል መድቧል።

የኢትዮጵያ ብረት ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን በበኩሉ የተለያዩ ክብደት ያላቸው ብረት ብረት ማቅለጥ የሚችሉ ስድስት ፋብሪካዎችን በ6 ወራት ውስጥ ገንብቶ ለማስረከብ ከክልሉ ጋር መስማማቱን አስታውቋል።

በክልሉ የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ሓላፊ አቶ ጥላሁን ታረቀኝ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንዳሉት የክልሉን የተፈጥሮ ሃብት ነባራዊ ሁኔታ መሰረት በማድረግ  የማምረቻ ፋብሪካዎቹ  በዘንድሮ ዓመት ይገነባሉ።

”ፋብሪካዎቹ የግብርናውን ምርት ለማቀነባበር የሚያስችሉና ለኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ መደላድል የሚፈጥሩ ናቸው”ብለዋል።

የክልሉ የተፈጥሮ ሃብት መሰረት በማድረግ ትልልቅ አራት የማምረቻ ፋብሪካዎች በአላማጣ፣ መቀሌ፣አድዋና ሁመራ ይገነባሉ ሲሉም ተናግረዋል።Tigrai - Mekele Hawlti

ባለፈው በጀት ዓመትም ክልሉ በ223 ሚልዮን ብር ወጪ በማምረቻ ኢንዱስትሪ ፣ፋብሪካዎች የፕሮዳክሽን ስራዎች ሊያሰሩ የሚችሉ ማሽኖች ያቀፉ አምስት የማምረቻ ፋብሪካዎች መገንባት መቻሉንም አስታውሰዋል።

ከአምስቱ የማምረቻ ፋብሪካዎች በተገኘ ተጨባጭ ልምድና  በተፈጠረ ፍላጎት መነሻነት ከክልሉ በተገኘ የገንዘብ ምንጭ እነዚህ ትልልቅ የማምረቻ ፋብሪካዎችን ለመገንባት ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱን አስታውቀዋል።

ከግንባታ እስከ አጠቃላይ የቴክኖሎጂ ሽግግር ያሉት ስራዎች በዋናነት በኢትዮጵያ ብረት ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን  እንደሚከናውን የገለፁት አቶ ጥላሁን  የገንዘብ  አቅርቦቱን ታዛ በተባለው የክልሉ የካፒታል ዕቃ የፋይናንስ አክስዮን ማሕበር እንደሚሸፈን ገልጸዋል።

የአክስዮን ማሕበሩ ምክትል ስራ አስፈፃሚ አቶ አማኑኤል ገብረ ትንሳኤ በበኩላቸው አገሪቱ መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለማሰለፍ በክልሉ በኢንዱስትሪው ዘርፍ ብዙ ጥረቶች እየተደረጉ ነው ብለዋል።

አቶ አማኑኤል እንዳሉት ኢንዱስትሪው ዘርፍ የኢኮኖሚ መሪነቱን እንዲረከብ አክስዮን ማህበሩ የማንፋክቸሪንግ ዘርፍ በፋይናንስ ለመደገፍና ዕድገቱን ለማቀላጠፍ የተቋቋመ ማሕበር ነው።

”በዕቅዱ መሰረት አንድ የማንፋክቸሪንግ ዕቃ ዋጋው ከ100 ሺህ በላይ ከሆነ የካፒታል ዕቃ ፋይናንስ ይባላል” ያሉት አቶ አማኑኤል የነዚህ የማምረቻ ኢንዱስትሪ ተጠቃሚዎችም ከተለያዩ የትምህርት ተቋማት ተመርቀው የሚወጡ ተማሪዎች እንደሆኑም ተናግረዋል።

ከዩኒቨርስቲዎች፣ ከኮሌጆች፣ ከቴክኒክና ሙያ  የተመረቁ እንዲሁም በህጋዊ ደረጃ የተደራጁና ዕውቅና ያገኙ ማህበራት እንደሚሆኑም አብራርተዋል።

ፋብሪካዎቹ በአማካይ ለ1500 ዜጎች የስራ ዕድል እንደሚፈጥሩና እነዚህ በጥቃቅንና አነስተኛ መልክ መንግስት ያደራጃቸው ዜጎች የፋብሪካውን የኢንቨስትመንት ወጪ በአምስት ዓመት ውስጥ ሙሉ በሙሉ በመክፈል  የፋብሪካው ባለቤት የሚደርግ አሰራር የተከተለ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ብረት ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን የማንፋክቸሪንግና ማሽን ተከላ ኢንዱስትሪ ዋና ስራ አስኪያጅ ሻለቃ ተሰማ ግደይ በበኩላቸው እስከ አምስት ቶን ብረት የማቅለጥ ዓቅም ያላቸውን ስድስት የብረታ ብረትና ብረት ያልሆኑ ቁሶች ማቅለጫ ፋብሪካዎችን ለመገንባት ተቋሙ ከክልሉ ጋር የኮንትራት ስምምነት መድረሳቸውን ገልጸዋል።

የግንባታስራውን በስድስት ወራት አጠናቆ  ለማስረከብ ተቋሙ ወደ ተግባር መግባቱንም አሰታውቀዋል።

የብረታ ብረት ማቅለጫ ፋብሪካዎች በየአከባቢው የወዳደቀ ብረቶችና ያረጁ ተሽከርካሪ አካላትን  አሰባስቦ ዳግም ጥቅም ላይ የማዋል ስራ እንደሚያከናውኑ ጠቁመው የእነዚህ ምርት  በአዲስ ዲዛይን ጥሬ ዕቃነት መለወጥ ያስችላል ብለዋል።

ስራ የጀመሩትም ሆኑ በቅርቡ ግንባታቸው ለሚጀመሩ የማንፋክቸሪንግ የማምረቻ ማዕከላት ከ75 በመቶ ሂደቱን የጨረሰ የምርት ግብአት የሚያቀርቡ መሆናቸውን አብራርተዋል።

ባለፈው ዓመት ስራ የጀመሩት አምስት የማምረቻ ፋብሪካዎች ለ500 ሰዎች የስራ ዕድል ፈጥረዋል።

***********

ምንጭ፡- ኢዜአ፣ ጥር 15-2007

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories