የሰንደቅ ዓላማ ቀን የማክበር ሀሳብ ያመነጨው ተፈሪ የማነ ወይስ… ?

የባንዲራ ቀን ማክበር የተጀመረው በ2000 ከሚሊኒየም በዓል አከባበር ጋር ተያያይዞ እንደሆነ ይታወሳል፡፡ በወቅቱ የቀድሞው የው የውጭ ጉዳይ ሚኒተር ስዩም መስፍን ሀሳቡን ያቀረበላቸው ተፈሪ የማነ እንደነበር ገልፀው ምስጋና ቸረውት የነበረ ሲሆን፣ ሌሎች ባለሙያዎች ግን እኛም የሀሳቡ ባለቤት ነን በሚል ቅሬታ አንስተዋል፡፡ የአዲስ ዘመን ጋዜጠኛ አርዓያ ጌታቸው ጉዳዩን እንደሚከተለው ዘግቦታል፡፡

(አርአያ ጌታቸው)

ሰሞኑን ነው። የሰንደቅ ዓላማ ቀን በሚከበርበት ዋዜማ። ወደ ዝግጅት ክፍላችን አንድ ጥቆማ መጣ። «የሰንደቅ ዓላማ ቀን እንዲከበር የሀሳቡ የመጀመሪያ አመንጪዎች እኛ ሆነን ሳለ አቶ ተፈሪ የማነ የተባሉ ግለሰብ ሃሳቡን የራሳቸው አድርገው ወስደውታል» የሚል። የዚህ ቅሬታ አቅራቢዎች ለሚሌኒየም በዓል አከባበር በአዲስ አበባ ደረጃ ተቋቁሞ በነበረው ጽህፈት ቤት ስር ሲያገለግሉ የነበሩ የኪነጥበብ ባለሙያዎች የተሰባሰቡበት የፌስቲቫል ኮሚቴ አባላት ናቸው።

በወቅቱ ኮሚቴውን በሰብሳቢነት ይመሩት የነበሩት አቶ ጌታቸው በለጠ የበዓሉ ሀሳብ የኮሚቴው እንጂ የግለሰቡ አይደለም ይላሉ። ሀሳቡ እንዴት እንደመነጨም የገለጹልን በዚህ መንገድ ነበር «…ኮሚቴያችን በወቅቱ ጥሩ ጥሩ ስራዎችን ሰርቷል። የስራዎቹ ማጠቃለያ ላይ ሲደረስ ‘ በዓሉን በምን አይነት ለየት ባለ መርሀ ግብር እንዝጋው?’ የሚል ሀሳብ ከኮሚቴው አበላት ይነሳል። ውይይት አደረግን። የተለያዩ ሀሳቦችም ተንሸራሸሩ። በመጨረሻ አንድ ሀሳብ የሁሉንም አባላት ቀልብ ገዛ። “አዲስ አበባ ከተማን በብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ አሸብርቀን ለምን የተለየ ድባብ አንፈጥርም?” የሚል። ሀሳቡ ከተንሸራሸረ በኋላ ይበልጥ ተሻሽሎ ‘ ከአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት እስከ ለገሀር ባቡር ጣቢያ ድረስ የሚደርስ ትልቅ ሰንደቅ ዓላማ አሰርተን ሰዎች በሰልፍ ሆነው በጭንቅላታቸው ላይ እየተቀባበሉ ይዘርጋና በዓለም የድንቃድንቅ መዝገብ ላይ አናስመዘግብም?’ የሚል ሆኖ ቀረበ።Ethiopia flag day celebration

«ይሄንን ሃሳብ እያንሸራሸርን ባለንበት ወቅት የእኛን ኮሚቴ ከጽህፈት ቤቱ ያገናኝ የነበረውና የፌስቲቫል ኮሚቴውን የሚመራው አቶ ተፈሪ የማነ መጣ። ሀሳቡን ነገርነው። በጣም ተደስቶም ‘ ይሄ እኮ ትልቅ ሃሳብ ነው። እንዴት በአዲስ አበባ ደረጃ ብቻ ይስተናገዳል። ለምን በብሔራዊ ደረጃ አናስብም?’ አለ። እኛም ‘ በዚህ ደረጃ ለማክበር እድሉ የለንም። ተጽዕኖ ማሳደርም አንችልም’ የሚል ምላሽ ሰጠነው። ‘እድሉን ስጡኝ’ አለን ‘ትችላለህ ሃሰቡን ውሰድና አስፈጽም’ አልነው።

«ጉዳዩንም ይዞ በወቅቱ የኢፌዴሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወደነበሩት አቶ ስዩም መስፍን ጋር ሄደ። ለእርሳቸውም ጉዳዩን አስረዳቸው። እርሳቸውም በጣም ተደሰቱ። ‘ እንዴት ይህ ሃሳብ መጣልህ?’ በማለት ከደስታቸው የተነሳ ደረታቸው ላይ ያለውን የሰንደቅ ዓላማ ፒን ሸለሙት። እርሱም ‘ ከልጅነቴ ጀምሮ ይሄንን እያሳብኩ ነው ያደኩት’ ብሎ የኮሚቴውን ሃሳብ የግሉ አድርጎ ነገራቸው። ፈቃድም ጠየቃቸው። እርሳቸውም ቀጥልበት አሉት» በማለት አቶ ጌታቸው ሃሳቡ እንዴት ከኮሚቴው መንጭቶ እንዴትስ በግለሰቡ እንደተቀማ ይናገራሉ።

ከዚያ በኋላም አቶ ስዩም ግለሰቡን የብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ ቀን ሲከበር ስለ ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ ጥናት መቅረብ አለበት ብለውት ስለነበር መልሶ ለእርሳቸው እንደነገራቸው አቶ ጌታቸው ያስታውሳሉ። እርሳቸውም ቀድሞውንም እየተዘጋጁበት የነበረ ጉዳይ ነውና ያንን ለመስራት ተስማሙ። ጥናቱም ተሰርቶ በፖስታ ታሽጎ ለአቶ ስዩም እንደተላከላቸው ነው የሚናገሩት።

«አቶ ስዩምም እኔ ደራሲን ማረም አልችልም እባክህን በጥንቃቄ ስራው፤ በጣም አመሰግናለሁ። ጥሩ ሃሳብ ነው። ጉዳዩ ጥንቃቄ ይሻልና በጥንቃቄ ስራው በማለት የአደራ መልዕክት በፖስታው ላይ ጽፈው ላኩልኝ። የጥናት ወረቀቱም ተባዝቶ ቀረበ። ከዚያ በኋላ ግን ሚዲያው ሁሉ እየተቀባበለ ‘ በዓሉ እንዲከበር ያደረገ የሃሳቡ ባለቤት እያለ…’ ኮሚቴውን ወደ ጎን ትቶ አቶ የማነ ብቻ መነሳት ቀጠለ። በጣም አዘንን። ይህ ሰው የግል ፍላጎት ካለው ይቀጥል ብለን ተውነው» በማለት የነበረውን ሂደት አስረድተውናል።

በወቅቱ የአዲስ አበባ ሚሌኒየም ጽህፈት ቤትን በዳይሬክተርነት ይመሩ ወደነበሩትና ጉዳዩን ያውቃሉ ወደተባሉት አቶ ኪሮስ ኃይለሥላሴ አቀናን። በጉዳዩ ዙሪያም አነጋግረናቸው « ሀሳቡ የመነጨው ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሚሌኒየም ጽህፈት ቤት ነው» የሚል ምላሽ ነው የሰጡን። እንደ እርሳቸው ገለጻ ለበዓሉ አከባበር የሚሆኑ ወደ 38 የሚደርሱ ፕሮጀክቶችን በመያዝ ነበር ፅህፈት ቤቱ የተከፈተው። ከፕሮጀክቶቹ መካከል ደግሞ አንዱ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም የድንቃ ድንቅ መዝገብ ላይ ማስመዝገብ የሚለው ይገኝበታል።

«…በወቅቱ ከጽህፈት ቤቱ ሰራተኞች በተጨማሪ ስራችንን እንዲያግዙን አስር የሚደርሱ ከተለያዩ ሙያዎች የተሰባሰቡ ባለሙያዎች በኮሚቴ መልከ ተሰባስበው ነበር። ብዙ ስራዎችንም እያማከሩን ሰርተናል። በዚህ መሀል የሰንደቅ ዓላማው ሀሰብ ብልጭታ ከእኛ ጽህፈት ቤት መጣ፤ ነገር ግን ኮሚቴው ይበልጥ አዳበረው። የእኛ ሃሳብ ያን ያህል የተጠናከረ አልነበረም። ቢቀርም ችግር የለውም የሚል አይነት ነበር። አብዛኞቹ የኮሚቴው አባላት የፈጠራ ሰዎች ነበሩና እኛንም የሚማርክ አይነት አድርገው ሀሳቡን አበሰሉት።

« በወቅቱ ታዲያ የዚህን ኮሚቴ ስራ የሚከታተልና የጽህፈት ቤቱ ተቀጣሪ ግለሰብ ነበረ። ይህ ግለሰብ ሃሳቡን ለቀድሞው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የራሱ ሀሳብ አድርጎ ነገራቸው። እርሳቸውም በተለያየ ምክንያት መከበሩ ጥቅም እንዳለው ስላመኑ በሀሳቡ ተስማሙ። ግለሰቡ ግን ሃሳቡ የራሱ እንደሆነ አድርጎ ቀጠለበት። በጽህፈት ቤት ደረጃ ሆነህ ከግለሰብ የመነጨ ሃሳብ እንኳን ቢሆን የመነጨው ሀሳብ የጽህፈት ቤቱ እና የመንግስት እንጂ የግለሰብ የሚሆንበት እድል የለም። በወቅቱም የነበረውን ቅሬታ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አሳውቄ ነበር» ነው የሚሉት አቶ ኪሮስ።

በወቅቱ አቶ ተፈሪን « ተው ሃሳቡ የጽህፈት ቤቱ አሊያም የኮሚቴው ነው ማለት ለምን አልተቻለም?» አዲስ ዘመን ይጠይቃል። አቶ ጌታቸው ምላሽ አላቸው «…ይታወቃል እኮ። በወቅቱስ እንዴት ብለን ይሄ ራዕይ የእኛ ነው እንላለን? ሁላችንም አፍረን ተውነው። ኪሮስም ይሄ የጽህፈት ቤቱ ራዕይ ነው፤ የኮሚቴው ራዕይ ነው ብሎ ጥያቄ ቢያቀርብም ዝም በል ብለው አፍ አፉን አሉት። እኛም ዋናው የበዓሉ መከበር ነው በሚል ጉዳዩን ተውነው።»

በተመሳሳይ አቶ ኪሮስም «በተደጋጋሚ በማኔጅመንት ተነጋግረናል። ነገር ግን ለውጥ አልመጣም። እኛም በዓሉ እስከተከበረ ድረስ እከሌ አመነጨው እከሌ፤ ምን ቸገረን በሚል ተውነው። እኛም እንደ እንቅፋት አንታይ ወደሚል አቋም ነው የሄድነው። ምክንያቱም ደጋግመን መብቱ የጽህፈት ቤቱ ነው በማለታችን ስራውን እንደማደናቀፍ ስለተቆጠረብን ተውነው። ያኔም የተከራከርኩት ሃሳቡ የጽህፈት ቤቱ ነው፤ ጽህፈት ቤቱ ደግሞ የመንግስት ነው ብዬ ነው፤ አሁንም ይሄው ነው ሃሳቤ» ሲሉ የተጓዙበትንና ያላቸውን አቋም ገልጸውልናል።

ዛሬም ድረስ የሀሳቡ አመንጪ የሚባሉትና ቅሬታ የቀረበባቸውን አቶ ተፈሪ የማነን ማነጋገር ነበረብንና ደወልንላቸው፤ እርሳቸውም «ይህንን ጉዳይ አንተ ገና ስትል ሰማሁ» በማለት ወደ ዝግጅት ክፍላችን ድረስ በመምጣት የተነሳባቸውን ቅሬታ «የሀሳቡ አመንጪ ተፈሪ የማነ ብቻ ነው» በማለት ውድቅ አድርገውታል።

«…ሀሳቡን እኔ አመንጭቼ ረጅም ጊዜ ከቆየ በኋላ ነው ኮሚቴው እንደ ኮሚቴ ሃሳቡን የተናገረው። በወቅቱ ያልኳቸው ጉዳዩ በጥንቃቄ ስለሚሰራ መረጃውን ለአቶ ስዩም መስፍን ነግሬያቸዋለሁ። ይሁንታ ያገኘ ጉዳይ ነው፤ ነገር ግን ገና ብዙ ነገሮች ያስፈልጉ ነበር» በማለት ጉዳዩን ለመጀመሪያ ጊዜ ከእርሳቸው እንደመነጨና ለኮሚቴው አባላትም የነገሯቸው እርሳቸው መሆናቸውን ጠቅሰው ይከራከራሉ።

« ነገር ግን ጉዳዩን ያቀረብኩላቸው የኮሚቴው አባላት ነገሩን ካለመረዳት የተነሳ ሶስት ሺ ሜትር ርዝመት ያለው ትልቅ ሰንደቅ ዓላማ እንስራ፤ በድንቃድንቅ መዝገብ እናስመዝግብ በሚል ተገነዘቡት። የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀን ሀሳቡ ግን ይሄ አይደለም። እነሱ ያሏቸው ነገሮች ለበዓሉ ማድመቂያ እንጂ ራሱን የቻለ በዓል አይደለም። ያም ሆነ ይህ ግን ያመነጨሁትን የሰንደቅ ዓላማ ቀን ሀሳብ አላስፋፉም አልረዱምም ብዬ ለመናገር ይከብደኛል። ከዚህ ውጭ ግን የነበራቸው ድርሻ እምብዛም ነው» በማለት የሀሳቡ አመንጪ እርሳቸው እና እርሳቸው ብቻ እንደሆኑ ነው አጽንኦት ሰጥተው የሚናገሩት።

ዝግጅት ክፍላችንም ሀሳቡ የእርስዎ ስላለመሆኑ የተለያዩ ሰዎች እየመሰከሩብዎት ነውና ሃሳቡ የእርስዎ ስለመሆኑ እማኝዎ ምንድነው ሲል ጥያቄ አቅርቦላቸው ነበር።

አቶ ተፈሪም «…በመጀመሪያ በሚሌኒየም ጽህፈት ቤቱ የታደለው ፕሮጀክት ላይ አዘጋጁ ተፈሪ የማነ ነው የሚለው፤ ቀጥሎ በዓሉ ሲከበር የመገናኛ ብዙሀንን ጨምሮ ሁሉም አካል ለእኔ ነው ባለቤትነቱን የሰጡት። ችግር ቢኖር ኖሮ ያኔ ማንሳት አይቻልም ነበር ወይ? ሰባት አመት መጠበቅ ለምን አስፈለገ? ከዚህ በላይ ደግሞ የቁም ነገር መጽሄት ዋና አዘጋጅና ማኔጅንግ ኤዲተር የሆነው ጋዜጠኛ ታምራት ኃይሉ በወቅቱ የኮሚቴውም አባል ስለነበር ሁሉንም ያውቃል። መጠየቅ ትችላለህ። ማወቅም ብቻ ሳይሆን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰንደቅ ዓላማ ቀን ሊከበር ነው ብሎ እኔን ምንጭ አድርጎ የሰራው እርሱ ነው። ጉዳዩን በደንብ ያውቃል።

« በተጨማሪም አቶ ስዩም መስፍን፣ አቶ ደግፌ ቡላ፣ አምባሳደር ተሾመ ቶጋ እና ሌሎች አካላትም መናገር የሚችሉት ሀቅ ነው። ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልም ቢሆን አብረን እንደምንሰራ በመግለጽ የሰጠኝ የምስጋና ወረቀት በእጄ አለ። ከተቋሙ ጋር የተዋዋልኩት የውል ሰነድም እንዲሁ። ይሄ ሁሉ ማስረጃ መሆን አይችል ይሆን?» ሲሉ አቶ ተፈሪ ይጠይቃል።

እኛም ነገሩን ከስር ከመሰረቱ ያውቃሉ ወደተባሉ ግለሰቦች ዘንድ መሄድ ቀጠልን። የቁምነገር መጽሄት ዋና አዘጋጅና ማኔጅንግ ኤዲተር የሆኑትና በወቅቱም የኮሚቴው አባል ወደነበሩት አቶ ታምራት ኃይሉ ደውለን ምላሻቸውን ሰጥተውናል።

«…ሀሳቡ ከአቶ ተፈሪ መምጣቱን አውቃለሁ። እኛ ለጽህፈት ቤቱ ስራ ስንሰራ እቅዱ ውስጥ የሰንደቅ ዓላማ ቀን ስለማክበር የሚል ነገር አልነበረም። ሃሰቡ የመጣው በኋላ ነው። ሃሳቡንም አደራጅቶ በጽሁፍ ይዞ የመጣው እራሱ አቶ ተፈሪ ነው። እርሱ ይዞ መምጣቱም ብቻ ሳይሆን አቶ ስዩም መስፍን እራሳቸው በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርበው የሀሳቡ ባለቤት ተፈሪ ነው ብለው ተናግረዋል። ያን ጊዜ የቀረበ ቅሬታ አልነበረም። እኔ የማውቀው ሀሳቡ ከእሱ መምጣቱን ነው። ከጽህፈት ቤቱ መምጣቱን አላውቅም። የሚሌኒየም ጽህፈት ቤት ነው ኃሳቡን ያመነጨው የሚለው ነገር ወደ ኋላ ተጎትቶ ለምን እንደመጣ እንደ ኮሚቴ አባልም እንደጋዜጠኛም አላውቅም። ሌላ ነገር ከጀርባ ካልገባ በስተቀር» በማለት አቶ ታምራት እውነት ያሉትን መረጃ አቀብለውናል።

አቶ ጌታቸው ሰራሁት ስላሉት ጥናት ጉዳይም አቶ የማነ የሰጡት ምላሽ «አቶ ጌታቸው ያጠኑት ጥናት የሰንደቅ ዓላማ ቀንን በዓል ለማክበር የመጨረሻ ዝግጅት በሚደረግበት ጊዜ የግንዘቤ ማስጨበጫ መድረኮች ያስፈልጉ ስለነበር የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አመጣጥ ታሪክን የሚያሳይ ጥናታዊ ጽሁፍ ነው» ብለዋል። አቶ ታምራት ደግሞ አቶ ጌታቸው ሊታተም ታስቦ ለነበረው መጽሄት አንድ አርቲክል ማቅረባቸውን ገልጸውልናል። መጽሄቱ በበጀት እጥረት ምክንያት አለመታተሙንም እንዲሁ።

አቶ ጌታቸው ለአቶ ስዩም ልኬላቸው እርሳቸውም በጥንቃቄ ይሰራ ብለው መልስ ሰጡኝ ስላሉት የጥናት ወረቀት ጉዳይም አቶ ተፈሪ እንዲህ በማለት ነበር ጉዳዩን «ሀሰት» ነው ያሉት። «…አቶ ስዩም በህይወት ያሉ ምስክር ናቸው። አቶ ጌታቸው ጥናት ወረቀት ልከውላቸው አሉ የተባሉትን ብለው በአድራሻ ወይንም በሌላ መንገድ መልዕክት ልከውላቸው ከሆነ እኔ እቀጣለሁ።»

አቶ ተፈሪን በወቅቱ የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ የነበሩት አቶ ኪሮስ ሃሳቡ የእርስዎ እንዳልሆነ ይልቁንም ባለቤቱ ጽህፈት ቤቱ እንደሆነ በመግለጽ በማኔጅመንት ስብሰባ ላይም ብቻ ሳይሆን ለወቅቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳይቀር ቅሬታ አቅርቤያለሁ ስላሉት ጉዳይ ምን ይላሉ? ብለናቸውም ነበር።

«…አቶ ኪሮስ በወቅቱ አቅርቢያለሁ ያሉት ሂልተን ሆቴል ተካሂዶ በነበረው ስብሰባ ላይ ነው። አቶ ኪሮስ ‘ የተከበሩ አቶ ስዩም ለምንድን ነው ክብሩን ለአቶ ተፈሪ ብቻ የሚሰጡት?’ በማለት ነበር ጥያቄ ያቀረቡት። በወቅቱም አቶ ስዩም ‘ ይሄ የተፈሪ ሃሳብ ስለሆነ እርሱን አመሰግናለሁ’ የሚል ምላሽ ሰጥተዋቸዋል። ከዚያ ቀጥሎ ግን አቶ ስዩም ነገሩን ለማረጋገጥ ወይዘሮ ጊፍቲ አባሲያን፣ አቶ ምስጋና አርጋ እና ሌሎች ባሉበት እንድንነጋገር ተደረገ። ወይዘሮ ጊፍቲም አቶ ኪሮስን ይሄ ሀሳብ የተፈሪ አይደለም ብለህ ታስባለህ? ብለው ጠይቀውት እርሱም እንደዚያ አይደለም ግን ሁላችንም እዚያ ላይ መካተት አለብን ብሎ መልሷል።»

የሰንደቅ ዓላማ ቀን ይከበር በሚለው ሃሳብ አመንጪነት ዙሪያ የተነሳውን የባለቤትነት ጥያቄ ከሞላ ጎደል ከሁለቱም ወገን ያለውን ሃሳብ አስነብበናል። ሆኖም በዚህ ጉዳይ ላይ ከዚህ የተለየ መረጃ አለኝ የሚል አካል ካለ ለማስተናገድ ዝግጅት ክፍላችን ክፍት ነው።

********

Areaya Getachew (MA) is a public relations expert at a foreign embassy. He studied second degree at Addis Ababa University and was deputy editor in-chief of Addis Zemen newspaper.

more recommended stories