አውቶሞቢሉ ቴዲ አፍሮን ለሁለተኛ ጊዜ አሳሰረው

ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ከስምንት ዓመታት በፊት በታላቁ ቤተ መንግሥት ጣይቱ ጎዳና ወደ ሸራተን ሆቴል በማሽከርከር ላይ እያለ፣ ደጉ ይበልጣል የተባለ የጎዳና ተዳዳሪ ገጭቶ ገድሏል ተብሎ ለፅኑ እስራት ቅጣት የዳረገው ቢኤምደብሊው አውቶሞቢል፣ በድጋሚ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አሳሰረው፡፡

ቴዲ አፍሮ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን መርማሪ ቡድን ሙሉ ቀን ታስሮ የዋለው፣ ተሽከርካሪው ወደ አገር ውስጥ ሲገባ ታክስ አልተከፈለበትም ተብሎ መሆኑ ታውቋል፡፡

የባለሥልጣኑ መርማሪ ቡድን ተሽከርካሪው ቀረጥ ሳይከፍልበት መግባቱን ካወቀ በኋላ ባደረገው ክትትል፣ በቁጥጥር ሥር ያዋለው ቴዲ አፍሮን ሳይሆን፣ አውቶሞቢሉን ከቴዲ አፍሮ የገዛውን ግለሰብ መሆኑም ታውቋል፡፡

Photo - Ethiopian singer Teddy Afro
Photo – Ethiopian singer Teddy Afro

ግለሰቡ ለጊዜው የታሰረ ቢሆንም፣ በተደረገበት ምርመራ ተሽከርካሪውን የገዛው  ከቴዲ አፍሮ መሆኑን በመግለጹ፣ እሱን በመልቀቅ በወቅቱ በውጭ አገር የነበረውን ቴዲ አፍሮን ሲጠባበቅ መቆየቱም ታውቋል፡፡

መስከረም 28 ቀን 2007 ዓ.ም. ወደ ኢትዮጵያ መመለሱ የተገለጸው ቴዲ አፍሮ እንደደረሰ ከመርማሪ ቡድኑ የስልክ ጥሪ የደረሰው ቢሆንም፣ በተለያዩ ምክንያቶች ወዲያውኑ ሳይሄድ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በጠዋት መሄዱም ታውቋል፡፡

ቴዲ አፍሮ የተፈለገበት ጉዳይ ከተነገረው በኋላ ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ተገልጾለት፣ ከሰዓት በኋላ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱ መርማሪ ቡድኑን ለምን እንዳቀረበው እንዲያስረዳ ጠይቆ፣ ከላይ የተገለጸውን አውቶሞቢል ቀረጥ ሳይከፍል ወይም የጉምሩክ ሥነ ሥርዓት ሳይፈጽምበት ሲጠቀም በመገኘቱ መሆኑን አስረድቷል፡፡

በነጭ ጫማ፣ ግሬይ ካኪ ሱሪ፣ ዥንጉርጉር ሹራብ፣ ጥቁር መነጽርና እንደተለመደው ከፊቱ በኩል ከፍባለው ፍሪዝ ፀጉሩ ፍርድ ቤት የቀረበው ቴዲ አፍሮ፣ ተሽከርካሪውን የገዛው በሕጋዊ ደረሰኝ ቀረጥ ከፍሎ መሆኑን አስረድቷል፡፡ መርማሪ ቡድን ግን ሰነዱ የሐሰትና የተጭበረበረ መሆኑን በማስረዳት ለተጨማሪ ምርመራ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቆ ነበር፡፡

ፍርድ ቤቱ የሁለቱን ተከራካሪ ወገኖች ምላሽ ካዳመጠና ከመረመረ በኋላ መርማሪ ቡድኑ ቴዲ አፍሮ ሳይታሰር ምርመራውን ማድረግ እንደሚችል ያመነበት መሆኑን በማስረዳት፣ በ30,000 ብር ዋስ እንዲለቀቅ ትዕዛዝ በመስጠት በዕለቱ ሊፈታ ችሏል፡፡ ቴዲ አፍሮ አራዳ ችሎት በነበረበት ጊዜ ነፍሰ ጡር ባለቤቱ ወ/ሮ አምለሰት ሙጬ፣ ወላጅ እናቱ፣ ጓደኞቹና አድናቂዎቹ ተገኝተዋል፡፡

*****

ምንጭ፡- ሪፖርተር፣ ጥቅምት 5፣2007

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories