የህዳሴ ግድብ ተቃዋሚ አሜሪካዊ ድርጅት ሆርን አፌይርስን አስጠነቀቀ

የኢትዮጲያን ግድቦች በመቃወም የሚታወቀው ‹‹ኢንተርናሽናል ሪቨርስ›› የተባለው ድርጅት የታላቁ የኢትዮጲያ ህዳሴ ግድብ ሥራ ቆሞ ከግብጽ ጋር ድርድር መካሄድ አለበት በማለት በመጋቢት 22/2006 ላወጣው መግለጫ፤ በሆርን አፌይርስ-የእንግሊዝኛው ገጽ(HornAffairs-English) ላይ በሚያዝያ 6/2006 የተሰጠውን ምላሽ አወገዘ፡፡

በዳንኤል ብርሃነ የተፃፈው ምላሽ፤ የድርጅቱን መግለጫ አንድ በአንድ እየነቀሰ ድርጅቱ የህዳሴ ግድብ ዓለም-አቀፍ የባለሙያዎች ፓነል ሪፖርትን አጣምሞ ማቅረቡን ያመላከተ ቢሆንም፤

የድርጅቱ ኤግዘኩይቲቭ ዳይሬክተር ጃሰን ራይኒ በሰጡት ምላሽ ላይ ግን ‹‹ኢንተርናሽናል ሪቨርስ የግብጽን ዘመቻ ተቀላቀለ›› የሚለውን ሐረግ እና ‹‹የኢንተርናሽናል ሪቨርስ ግብፃዊ ፋይናንሰሮች እና ኤክስፐርቶች ይጨነቁበት›› የሚለውን ሐረግ ብቻ መዝዘው በማውጣት፤ ሕግ ባለበት ሀገር ብትኖሩ ኖሮ በስም ማጥፋት እንከሳችሁ ነበር ብለዋል፡፡

ዳይሬክተሩ የኢንተርናሽናል ሪቨርስ መግለጫ ዋና ሀሳብ ላይ ለቀረበው ዝርዝር ትችት አንዳችም ምላሽ ያልሰጡ ቢሆንም፤ ‹‹በግብጽ ነዋሪ ከሆነ ግለሰብ ባለፉት ሰባት ዓመታት አንድም ዶላር አልተቀበልንም›› እንደገናም በግብጽ መንግስት አንረዳም ካሉ በኋላ ሆርን አፌይርስ በይፋ ማስተባበያ እንዲሰጥ ወይም ማስረጃ እንዲያቀርብ ጠይቀዋል፡፡

የህዳሴ ግድብን በተመለከተ መከሰስ የሚያኮራ ቢሆንም፤ ከድርጅቱ ሀላፊዎች ጋር በስካይፕ(Skype) ለመከራከር ላቀረብነው ጥያቄ ምላሽ ለመጠበቅ እንዲሁም በአንድ ጉዳይ ላይ ክስ የመመስረቻ ግዜ(statute of limitations) ረዘም ያለ ከመሆኑ እና ከተዛማጅ ጉዳዮች አንፃር፤ በአሜሪካ ሕግ እና በኢንተርኔት አሠራር ላይ ኤክስፐርት ከሆኑ ኢትዮጲያውያን የተሟላ ምክር ለማግኘት የሚቀጥሉትን ሁለት ቀናት በመውሰድ፤ ከዚያ በኋላ ሙሉ ምላሽ በሆርን አፌይርስ የእንግሊዝኛው ገጽ (HornAffairs-English) ላይ የምንሰጥ መሆኑን እንገልፃለን፡፡

ኢንተርናሽናል ሪቨርስን ያስቆጣው እና ለዛቻ ያበቃው ጽሑፍ – በብሔራዊው የህዳሴ ግድብ የኤክስፐርቶች ፓነል ‹‹ሊነበበው የሚገባው›› በሚል አድናቆት እንደተቸረው ይታወሳል፡፡

የኢትዮጲያን ዐብይ የልማት ፕሮጀክቶች ከሚቃወሙ ተቋማት እንዲህ ዓይነት ቀጥተኛ ምላሽና ዛቻ የተሰነዘረበት የመጀመሪያው ሀገራዊ ሚዲያ ሆርን አፌይርስ እንደሆነ ይገመታል፡፡
***********

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories