በኢትዮጵያ የአእምሮ ህክምና ባለሞያዎችን በብዛት ለማፍራት የአማኑኤል አዕምሮ ህክምና ሆስፒታልን ጨምሮ በአምስት ዩኒቨርስቲዎች ስልጠና ሊሰጥ ነው፡፡
የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ስልጠናውን ከሚሰጡ ከባህርዳር፣ሀዋሳ፣ መቀሌ፣ሀረማያ፣ ጅማ ዩንቨርስቲ እንዲሁም የአማኑኤል የአዕምሮ ህክምና ሆስፒታል ተወካዮች ጋር በጋራ ለመስራት በሚያስችላቸው የመግባቢያ ሰነድ ላይ ትናንት ተፈራርመዋል፡፡
የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ደኤታ ዶክተር ከበደ ወርቁ እንደተናገሩት በስምምነቱ መሰረት ተቋማቱ ለአዕምሮ ህሙማን ቀላል የህክምና አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎችን ያሰለጥናሉ፡፡
ባለሙያዎቹም 160 በሚጠጉ የጤና ተቋማት ውስጥ የሕክምና አገልግሎቱን እንዲሰጡ እንደሚደረግ የገለጹት ዶክተር ከበደ ከፍተኛ ህክምና ለሚያስፈልጋቸው ደግሞ ወደ ከፍተኛ ባለሙያዎች የሚገኙበት የጤና ተቋማት እንዲያስተላልፉ ይደረጋል፡፡
የህክምና ባለሙያዎች ስልጠና ከ2003 በፊት ከአለም ጤና ጥበቃ ድርጅት ጋር በመተባበር ቢጀመረም በሰው ሀይል እጥረት ምክንያት የሚፈለገውን ያህል ርቀት መሄድ እንዳልተቻለ ሚኒስትሩ ዴኤታው ተናግረዋል፡፡
አሁን ባለው እንቅስቃሴ በቀጣይ አምስት አመታት ውሰጥ ችግሩን ሙሉ ለሙሉ እንደሚፈታ እምነት አለን ብለዋል፡፡
*********
ምንጭ፡- ኢዜአ – የካቲት 15/2006፤ ‹‹በኢትዮጵያ በአምስት ዩኒቨርስቲዎች የአእምሮ ህክምና ስልጠና ሊሰጥ ነው››