የአባይ ወንዝ ተፈጥሯዊ አቅጣጫ ዛሬ በይፋ ተቀየረ።

(ባሃሩ ይድነቃቸው)

ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ አመቺነት የአባይ ወንዝን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ የማስቀየር ስራ ሲከናወን ቆይቷል ።

ይህ ስራ ተጠናቆ ዛሬ ወንዙ በይፋ ተፈጥሯዊ አቅጣጫውን ቀይሯል ።

የወንዙን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ የማስቀየሩን ተግባር ይፋ ለማድረግ በተዘጋጀ ስነ ሰርዓት ላይም የተገኙት የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን እለቱ አባይን በፈለግንበት መስመር የምናስኬድበት ቀን ብለዋል ።A little girl on Blue Nile bridge

“ስር በሰደደ ድህነታችን ምክንያት በፈለግነው ሳይሆን እሱ ባሰኘው መንገድ ሲፈስ ቆይቷል” ያሉት አቶ ደመቀ ፥ “አሁን አባይን በመዳፋችን ውስጥ እንዲገባ አድርገናል” ነው ያሉት ።

አባይ እጣ ፈንታው በእጃችን እንዲሆንና በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ እኛ በመራንበት እንዲጓዝ ማድረጋችን የኢትዮጵያንና የአፍሪካን ህዳሴ የሚያመላክት መሆኑንም ተናግረዋል ።

እንደ አቶ ደመቀ ንግግር እለቱም ከግንቦት 20 ጋር መገናኘቱም ልዩ ትርጉም ያለው ይሆናል ።

በዚህ ታሪካዊ እለት ከአገሪቱ ማህፀን ፈልቆ ኢትዮጵያን የበይ ተመልካች ያደረገው አባይ በኢትዮጵያ መዳፍ ላይ መውደቁ እለቱን የድርብርብ ታሪክ ባለቤት ያደርገዋልም ነው ያሉት ።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት ፥ የዚህ ታላቅ ፕሮጀክት ጠንሳሽ አቶ መለስ ዜናዊ የተሰዉለት ዓላማ የጠራ መሆኑንና የመላውን ህዝብ ድጋፍ ማግኘቱንም ያረጋገጠም ሆኗል ።

አገራዊው ደስታ ሙሉ የሚሆነው ግድቡ ስራ ሲጀመር በመሆኑም ህዝቡ ድጋፉን እንዲቀጥል ጠይቀዋል ።

በግድቡ ግንባታ ሂደት አራት አበይት ክንውኖች አሉ ያሉት የኢፌዴሪ የውሃና ኤኔርጂ ሚኒስትር አቶ ዓለማየሁ የተገኑ ደግሞ ፥ ዛሬም በይፋ የተከናወነው የወንዙን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ የማስቀየር ስራ አንዱ ነው ብለዋል ።

የወንዙ ተፈጥሯዊ አቅጣጫ መቀየር የአይችሉም አመለካከትን በከፍተኛ ደረጃ የሚያከስምና ኢትዮጵያ ወንዙን ማልማት እንደምትችል የሚያሳይም ነው።

አቅጣጫውን ማስቀየር ለምን አስፈለገ ?

ወንዙ የሚገኘው ግድቡ በሚገነባው መሃል ላይ ሲሆን ፥ ወንዙ እየፈሰሰ ግድቡን መገንባት የማይቻል በመሆኑ ነው ተፈጥሯዊ አቅጣጫውን ማስቀየር ያስፈለገው ።

አቅጣጫ የማስቀየሩ ስራ በግንብታው ሂደት አስቸጋሪ ስራ መሆኑን የሚናገሩት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሀይል ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ምህረት ደበበ ፥ ስራውም እጅግ ከፍተኛ ጥረት ውጤት መሆኑን አመልክተዋል ።

የግድቡ ፕሮጀክት ዋና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ስመኘው በቀለ በበኩላቸው ፥ የወንዙን አቅጣጫ የማስቀየሩ ስራ ከተያዘለት ጊዜ በሁለት ሳምንት ቀደም ብሎ መጠናቀቁን በመጠቆም ይህ ስራዎች ከተያዘላቸው ጊዜ ቀደም ብለው በፍጥነት እየተከናወኑ መሆናቸውን እንደሚያሳይ ነው ያመለከቱት ።

በአሁኑ ወቅትም የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ 21 በመቶ መጠናቀቁ ተመልክቷል ።

*************

Source: Fana – May 28, 2013, titled “አባይ ተፈጥሯዊ አቅጣጫውን ቀየረ”.

Daniel Berhane

more recommended stories