የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ ተጠናቀቀ

በዕለቱ በተያዙት አጀንዳዎች ዙሪያ ተወያይቶ በማፅደቅ ሥራውን የጀመረው ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በገጠር የበጋ ሥራዎች አፈፃፀምና የመኽር ሥራ ዝግጅትን ከክልሎች በቀረቡት እና ከማዕከል በተካሄዱ የሱፐርቪቪን ሪፖርቶች ላይ ተመስርቶ ገምግሟል፡፡

በ9ኛው የኢህአዴግ ጉባኤ በአፅንኦት ተገምግሞ በየደረጃው የሚገኘው አመራር ሚናውን በተገቢው መንገድ በሚወጣበት እና የአርሶአደሩን ተሳትፎ ማዕከል ባደረገ አኳኋን በፍጥነት እንዲሻሻል አቅጣጫ የተቀመጠበት ዋነኛው ጉዳይ የግብርና ምርትና ምርታማነት የነበረ መሆኑን በማውሳት የበልግ አፈፃፀምና የመኽር ዝግጅቱን ፈትሿል፡፡EPRDF logo

የበልግ ሥራ በሚዘወተርባቸው ክልሎች የነበረው አፈፃፀምና በሂደቱም የተገኘው ልምድ የመኸር ምርትና ምርታማነት ከማሳደግ አንፃር አወንታዊ ውጤት በሚያመጣ አግባብ መፈፀሙን አረጋግጧል፡፡ ለመኽር ወቅት በመካሄድ ላይ ያለው የዝግጅት ሥራም በተለያየ ደረጃ የሚገኝ መሆኑን በማረጋገጥ በደረሰበት ደረጃ ያለው አፈፃፀም ከበጋ ወራት ተግባሮች በተገኙት ተሞክሮዎች እየጎለበተ የመጣ በመሆኑ ተስፋ ሰጪ መሆኑን አረጋግጧል፡፡

በቀጣይም የግብአት አቅርቦቱ የአርሶአደሩን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገና በወቅቱና በሚፈለገው መጠን ማቅረብ በሚችልበት አግባብ ርብርብ እንዲደረግ አሳስቧል፡፡ ምርታማነትን ከማሳደግ አንፃር በየአካባቢው ሞዴል አርሶአደሮች የደረሱበትን የምርታማነት ደረጃ ለመድረስ ያበቁዋቸው ልምዶች በተገቢው እየተቀመሩ በሁሉም አርሶአደር ዘንድ ወደ ሞዴሎች ለመድረስ ቢያንስ ልዩነቱን ለማጥበብ በሚያስችል ደረጃ ለመንቀሳቀስ በቂ ተነሳሽነትና ክህሎት በሚፈጥር አግባብ በከፍተኛ ትኩረት መፈፀም እንዳለበትም አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡

የከተማ ሥራዎች አፈፃፀም ላይ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ልማትና የመልካም አስተዳደር ጉዳዮችን በተመለከተ በየክልሉ ያለውን ሁኔታ ፈትሿል፡፡ የስራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትኩረት ሰጥቶ በመሰራት ላይ መሆኑን በማረጋገጥ በ9ኛው ጉባኤ ላይም የተሰመረበትን የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ከማበረታታት አንፃር የሚታዩትን ማነቆዎች በፍጥነት ለመፍታት መወሰድ ያለባቸው ተጨማሪና ተጨባጭ እርምጃዎች በፍጥነት እንደሚወስዱ የጋራ አቋም ይዟል፡፡

በዘርፉ አንቀሳቃሾች ዘንድ እየጎለበተ የመጣው ምርትን በጥራት የማምረትና ቁጠባን የማሳደግ እንዲሁም ብድርን በወቅቱ የመመለስ ሁኔታ የዘርፉን ጤንነት በመጠበቅ ልማታዊ ኢንዱስትሪ ከመገንባት አንፃር አወንታዊ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስቧል፡፡ ወጣቶች በተለያዩ የሥራ መስኮች በመሰማራት በጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፍ ለመሰማራት የሚስፈልገውን የ20% መነሻ ካፒታል በመያዝ ረገድ መጠናከር ያለበት አወንታዊ መሻሻል መታየቱን ገምግሟል፡፡ ይኸው ጅምር መበረታትት እና ከመንግስት የሚቀርበው የብድር አቅርቦት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስቧል፡፡

በከተሞች በህዝቡ ተሳፎ ላይ የተመሰረተው የመልካም አስተዳደር እንቅስቃሴ ለማድረግ በተያዘው ዕቅድ መሰረት በተለይም በአዲስ አበባ ፈጣን ለውጥ እንዲመዘገብ ታስቦ ሰፊ እንቅስቃሴ በተካሄደባቸው ስራዎች አበረታቸ ውጤት መገኘቱን ስራ አስፈፃሚው ገምግሞ ወደፊትም በህዝቡ ተሳትፎ የታቀደውን ግብ ለመምታት እንደሚቻል እምነት እንዳለው ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አመልክቷል፡፡

ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው የድርጅቱ 9ኛ ጉባኤ በተሳካ ሁኔታ መከናወኑን አይቶ ከዛው ተከትሎ የተካሄደው የአካባቢ፣ አዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤትቶች ምርጫ ሰፊ የህዝባዊ ተሳትፎ በተረጋገጠበትና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ በዕቅዱ መሰረት ተሳክቶ መጠናቀቁን ገምግሟል፡፡ በተያያዘም ስራ አስፈጻሚው ለጉባኤውና ለምርጫው ስኬት አስተዋጽኦ ያደረጉ አካላትና መላ የሀገራችን ህዝቦች ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ በሳዮት በጎ እንቅስቃሴ እና ለድርጅታችን ላደረጉት ድጋፍ ምስጋናን አቅርቧል፡፡

ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በተነሱት ጉዳዮችና ሌሎች ተያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ዙሪያ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ትላንት ማምሻውን ስብሰባውን አጠናቋል፡፡

***********

Source: EPRDF

Daniel Berhane

more recommended stories