ኢሕአዴግ ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ለመደራደር ዝግጁ መሆኑን ገለጸ

(የኢትዮጲያ ዜና አገልግሎት – ኢዜአ)

የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) በአገር ውስጥ ዕውቅና ካገኙ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ለመከራከርና ለመደራደር ዝግጁ መሆኑን ገለጸ።

ድርጅቱ ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር የሚያደርገው ክርክርና ድርድር በቀጣዩ ሣምንት መካሄድ ይጀምራል።

የኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የድርጅቱ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ድርጅቱ እንደ ገዢ ፓርቲ በጋራ ከመስራት አኳያ የነበረበትን ውስጣዊ ክፍተት በመለየት በአገራዊ የጋራ ጉዳዮች ዙሪያ ይበልጥ ተቀራርቦ ለመስራት ተዘጋጅቷል።

ቀደም ሲልም አብሮ ለመስራት ፍላጎቱ ካላቸው ተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር የጋራ ምክር ቤት መስርቶ ሲሰራ መቆየቱንም አውስተዋል።

ሠላማዊ እስከሆኑ ድረስ ኢሕአዴግ በኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባናል ከሚሉ ማናቸውም ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር አብሮ ይሰራል ብለዋል።

ኢሕአዴግ በሚያቀራርቡ ጉዳዮች ውይይትና ድርድር ያደርጋል፤  በሚለያዩባቸው ጉዳዮች ደግሞ  ከፓርቲዎቹ ጋር ክርክር ያካሂዳል።

በዚህም ፓርቲዎቹ ለሕዝቡ “አለን” የሚሉትን ሀሳብ አቅርበው ህዝቡ አጀንዳቸውን በግልጽ እንዲያይና እንዲወስን የሚያስችለው ግንዛቤ ይይዛል ነው ያሉት።

Photo - Shiferaw Shegute, head of EPRDF secretariat
Photo – Shiferaw Shegute, head of EPRDF secretariat

ኢሕአዴግ ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ለመደራደር ያቀረበው ግብዣ አዲስ እንዳልሆነ አቶ ሽፈራው ጠቅሰው፤ ደርግን አሸንፎ በመሰረተው የሽግግር መንግሥት የተለያዩ ፓርቲዎች ተሳትፎ እንዲኖራቸው መጋበዙን በማሳያነት አንስተዋል።

ሕገ-መንግሥቱን በማርቀቅና በማጽደቅ በኩል የነበረው ተሳትፎም አቶ ሽፈራው በማሳያነት ያቀረቡት ሌላው ጉዳይ ነው።

እናም አሁን የቀረበው የእንደራደር ግብዣ አዲስ አለመሆኑን አስምረውበታል።

የአሁኑን የተለየ የሚያደርገው ሠላማዊ እስከሆኑ ድረስ ‘መመሪያውን ፈረሙ አልፈረሙ’ የሚል ድንበር አይበጅላቸውም ነው ያሉት።

ኢሕዴግም ሆነ ተፎካካሪ ፓርቲዎቹ የድርድር ሥርዓቱ ምን ሊሆን እንደሚችል የየራሳቸውን ሃሳብ ማቅረብ እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ ጉዳይ ፍላጎት ያላቸው ኢሕአዴግን ጨምሮ ፓርቲዎች ብቻ እንዳልሆኑ ግን ግንዛቤ ሊያዝ እንደሚገባ ነው የተናገሩት።

የተለያዩ የኅብረሰተብ ክፍሎች፣ ምሁራንና የሲቪክ ማኅበራት መኖራቸውን ገልጸው፤ ኢሕአዴግ ከእነዚህም ጋር በአጋርነት መስራት እንደሚፈልግ ይፋ አድርገዋል።

የፖለቲካ አቋምና ክርክር ሳይሆን በአማካሪነት፣ አዳዲስ ሃሳቦችን በማመነጨትም ይሁን ክፍተቶችን በማመላከት አሊያም ህዝብና አገርን በመወከል በፐብሊክ ዲፕሎማሲ ይሁን በምርምር ሥራ አብሮ መስራትን ያካትታል።

የኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴም ይህንኑ አቋሙን በቅርቡ ግልጽ አድርጓል።

የዴሞክራሲ ተሳትፎን ለማጎልበትና የተሟሟቀ የዴሞክራሲ እንቅስቃሴ እንዲኖር ለማድረግ ኢሕአዴግና መንግሥት ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር በቅርቡ ድርድርና ውይይት እንደሚያካሂዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በሳምንቱ መግቢያ መናጋራቸው ይታወሳል።

ድርድሩ ታዳጊ የሆነውን አገራዊ የዴሞክራሲ ተሳትፎ ከማጎልበት አኳያ የሚታይ ሲሆን፤ በእንቅስቃሴውም የመገናኛ ብዙኃን፣ የሲቪክ ማኅበራትና የሕዝብ አደረጃጀቶች እንደሚታቀፉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስረድተዋል።

ከፓርቲዎቹ ጋር የሚደረጉ ድርድሮችን የሚከታተል ማዕከል በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት እንደተቋቋመም ተናግረዋል።

በኢሕአዴግ በኩል ለድርድሩ ዕቅድ ወጥቶ ዝግጅት መደረጉን ገልጸው፤ ለድርድሩ በግንባሩ ምክትል ሊቀመንበር የሚመራ ኮሚቴ እንደተቋቋመ መናገራቸው የሚታወስ ነው።

በአገር አቀፍ ደረጃ በምርጫ ቦርድ ዕውቅና ያላቸው 23 ፓርቲዎች በውይይቱ ተካፋይ እንደሚሆኑ ይጠበቃል።

*********

* የኢትዮጲያ ዜና አገልግሎት – ኢዜአ፣ ጥር 6/2009

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories