የሰማያዊና የ8ቱ ፓርቲዎች አባላትና የሰልፉ ተሳታፊዎች በመታወቂያ ዋስ ተፈቱ

(የሰማያዊ ፓርቲ ዘገባ)

በሰላማዊ ሰልፉ ወቅት ታፍሰውና ደብደባ ተፈጽሞባቸው ከታሰሩ በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበው ‹‹ህገ መንግስቱን በመናድ፣ መስቀል አደባባይ ላይ ንብረት በማውደም፣ በሁከትና ብጥብጥ›› እና በመሳሰሉት ክሶች ተከሰው እስከ 14 ቀን ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸው የነበሩት የሰማያዊና የሌሎች የ9ኙ ፓርቲዎች አመራሮች፣ አባላትና የሰልፉ ተሳታፊዎች በመታወቂያ ዋስ እንዲፈቱ ተወሰነ፡፡

ከእስረኞቹ መካከል ከፍተኛ ድብደባ ደርሶባቸው አዲስ አበባ ፖሊስ (ሶስተኛ) ታስረው የነበሩት ‹‹ህገ መንግስቱን በመናድ›› ክስ 14 ቀን፣ ፖፖላሬ ታስረው የነበሩት ‹‹መስቀል አደባባይ ላይ ንብረት በማውደም›› 7 ቀን፣ እንዲሁም ቤላ እስር ቤት ታስራ የነበረችው ወይንሸት ንጉሴ ‹‹ሁከትና ብጥብጥ በመፍጠርና ህዝቡን በመረበሽ›› 7 ቀን፣ እንዲሁም ኮተቤ ታስረው የነበሩት እነ ፍቅረማሪያም በተመሳሳይ ‹‹ሁከትና ብጥብጥ በመፍጠር›› 10 ቀን ተቀጥሮባቸው የነበር ቢሆንም ከቀጠሯቸው ቀን ቀድም በመታወቂያ ዋስ እንዲፈቱ ተወስኗል፡፡

በሶስተኛ፣ ፖፖላሬ፣ ቤላና ኮተቤ የነበሩት እስረኞች ከትናንት ጀምሮ በመታወቂያ ዋስ እንዲወጡ ቢወሰንም ፖሊስ አንዳንድ እስረኞችን በተለይ ፖፖላሬና ሶስተኛ ታስረው የነበሩትን ነጥሎ ለማስቀረት ባደረገው ጥረት የመታወቂያ ዋስ አምጥተው እንዲፈቱ የተነገራቸው እስረኞች ‹‹አብረውን የታሰሩት ካልተፈቱ አንወጣም›› በማለታቸው ሳይፈቱ አድረዋል፡፡

ዛሬ ታህሳስ 2/2007 ዓ.ም ደህንነቶች ሶስተኛ ታስረው የነበሩትን መርከቡ ሀይሌ፣ ሳሙኤል አበበ፣ ምኞት መኮንን እና ሜሮን አለማየሁ እንዲሁም ፖፖላሬ ታስረው የነበሩትን ዮናስ ከድርና ተስፋዬ መርኔ ‹‹አብራችሁን ካልሰራችሁ አትወጡም!›› ብለዋቸው እንደነበር ታውቋል፡፡ ሆኖም በመታወቂያ ዋስ እንዲወጡ የተነገራቸው እስረኞች ‹‹እነሱ ካልወጡ እኛም አንወጣም›› በማለታቸው በአራቱም እስር ቤቶች የሚገኙት ሁሉም ታሳሪዎች የመታወቂያ ዋስ አቅርበው እንዲለቀቁ ተወስኗል፡፡

በሌላ በኩል በቅስቀሳ ወቅት ተይዞ ጉለሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ ጣቢያ ታስሮ የሚገኘው ሲሳይ ሰይፉ እንዲሁም ወረዳ 9 የሚባለው እስር ቤት የታሰሩት ባህረን እሸቱና ማቲያስ መኩሪያ በመታወቂያ ዋስ እንዲፈቱ የተባሉት አመራች ከተከሰሱበት ‹‹ህገ መንግስቱን በመናድ›› የሚል ክስ ባነሰው ‹‹ባልተፈቀደ ሰልፍ በመቀስቀስ›› በሚል የተከሰሱ ቢሆንም እስካሁን አልተፈቱም፡፡

********

ምንጭ፡- ሰማያዊ ፓርቲ – ታህሳስ 02-2007

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories