ኢትዮጵያ የሳተላይት ባለቤት የሚያደርጋትን ስምምነት ተፈራረመች

(ሃብታሙ ድረስ)

ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት 5 ዓመታት ከ20 እስከ 25 ኪ.ግ ክብደት ያለው መካከከለኛ ሳተላይት ባለቤት የሚያደርጋትን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመች፡፡

ስምምነቱ የተፈረመው በእንጠጦ ኦብዞርቫቶሪና ምርምር ማዕከልና ፊንላንድ ከሚገኘው የኖርዲክ ሀገራት ስፔስ ሳይንስ ቴክኖሎጂና ሳይንስ ተቋም ጋር ነው፡፡

የስምምነቱ ዓላማ ደግሞ መሬትና ህዋን የሚመለከት ሳተላይት በትብብር መገንባትና ማምጠቅ ነው፡፡

የእንጦጦ ኦብዘርቫቶሪና ምርምር ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሰለሞን በላይ በስምምነቱ ወቅት እንዳሉት ኢትዮጵያ የራሷን ሳተላይት ማምጠቋ ለእርሻ ስራ፣ ለተፈጥሮ ሃብት መቆጣጠሪያ፣ የአየር ንብረት ለመተንበይ፣ ስለማዕድን፣ ስለከተማ ልማትና ሌሎችም አገልግሎቶች ይጠቅማታል ብለዋል፡፡

የኖርዲክ ሀገራት ስፔስ ሳይንስ ቴክኖሎጂና ሳይንስ ተቋም ዋና ስራ አስፈጻሚ ሚስተር ሳሊ አህመድ በበኩላቸው ተቋማቸው ያለውን የ50 አመታት ልምድ በመጠቀም በኢትዮጵያ ውጤታማ ስራ ለማከናወን መዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡

የእንጦጦ ህዋ ሳይንስ ኦብዘርቫቶሪ ተቋም ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተፈራ ዋልዋ ኢትዮጵያ ለህዋ ሳይንስ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው ብለዋል፡፡

የአሜሪካ፣ አውሮፓ፣ ቻይናና ሌሎች ሀገራት ተመራማሪዎች ከኢትዮጵያ ጋር በዘርፉ ለመስራት ፍላጎት ማሳየታቸውንም አቶ ተፈራ ገልጸዋል፡፡

*******
Source: ኢቲቪ፣ ነሐሴ 26፣ 2006

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories