ኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት የሚሰነዘሩባትን የሳይበር ጥቃቶች የመመከት አቅሟ በአስተማማኝ ሁኔታ እየዳበረ መምጣቱን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ አስታወቀ።
የአገርና የህዝብ ቁልፍ መረጃዎች ምስጢርነታቸው እንዲጠበቅ እየገነባ ያለው “ዳጉ” የመረጃ ልውውጥ ሥርዓት በቀጣዩ ዓመት ሥራ እንደሚጀምርም ይፋ አድርጓል።
የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ብርጋዴር ጀነራል ተክለብርሃን ወልደአረጋይ እንዳሉት ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ካለችው ሁለንተናዊ ዕድገት ባሻገር በቴክኖሎጂውም ጠንካራ መሰረት በመገንባት ላይ ትገኛለች።
ኤጀንሲው እስካሁን ያልነበሩና ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ ከባድ የሳይበርና የመሰረተ ልማት የጥቃት ሙከራዎችን ጭምር ይበልጥ የመመከት አቅሙን ለማዳበር እየሰራ መሆኑን ነው ብርጋዴር ጀነራል ተክለብርሃን ለኢዜአ ያስረዱት።
ኢንሳ የመንግሥት ተቋማት የራሳቸው የመረጃ ልውውጥ ሥርዓት /ኢ-ሜይል/ እንዲኖራቸው የማድረግ ሥራ እያከናወነ ይገኛል።
ከአፋር ባህላዊ የመረጃ ልውውጥ ሥርዓት ስያሜውን ያገኘው “ዳጉ” የተሰኘው ይኸው አዲስ ቴክኖሎጂ በአሁኑ ወቅት ሥራው ተጠናቆ በሙከራ ትግበራ ላይ እንደሚገኝና በ2007 ዓ.ም መጀመሪያ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ እንደሚገባ ተናግረዋል።
በአገሪቱ በሚገኙ የገንዘብ፣ የኤሌክትሪክ ኃይልና የቴሌኮም ተቋማት ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ኢንሳ በመከላከል በኩል ከፍተኛ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝም ሀላፊው ገልፀዋል፡፡
**********
*ምንጭ፡- ኢዜአ፣ ግንቦት 10፣ 2006 – ርዕስ ‹‹ኢትዮጵያ የሳይበር ጥቃቶችን የመመከት አቅሟ አስተማማኝ ሆኗል – ኢንሳ››.
Send Newsletterdaily