(ብርሀኑ ወልደሰማያት)
ኢትዮ ቴሌኮም በአዲስ አበባ በ75 ቦታዎች ላይ የሚሰተዋለውን የኔትወርክ ችግር ሙሉ በሙሉ መፍታቱን አስታወቀ።
የተቋሙ የኮርፖሬት ኮሚኒኬሽን ዳይሬክተሩ አቶ አብዱራሂም አህመድ በሰጡት መግለጫ፥ ተቋሙ በአዲስ አበባ በ75 ቦታዎች ላይ ሲያካሂድ የነበረው የማስፋፋያ ስራ በመጠናቀቁ ችግሮች እየቀነሱ ሲሆን፥ በ600 ቦታዎች ላይ እየተከናወነ ያለው የማስፋፋፊያ ስራ በመጪው ሰኔ ሲጠናቀቅም ችግሩ ሙሉ በመሉ ይፈታል ብለዋል።
ተቋሙ በአዲስ አበባ በ722 ቦታዎች ላይ የማስፋፊያ ጥራትን ማረገጋጥ የሚያሰችሉ ስራዎችን እያከናወነ ነው ያሉት ዳይሬክተሩ፥ በተለይ አሰኮ፣ ኮልፌና አካባቢው፣ አሮጌው አውሮፕላን ማረፊያና ሀና ማሪያም አካባቢ ያለው የኔትወርክ አቅም ከእጥፍ በላይ ማደጉን ጠቁመዋል።
የኖኪያ አካባቢ በሚል ይጠሩ የነበሩና ኢትዮ ቴሌኮም ችግራቸው ተፈቷል ያላቸው 75 አካባቢዎች ቢኖሩም አሁንም ችግር መኖሩ ይነሳል።
አቶ አብዱራሂምም ችግሮች ሙሉ በሙሉ እንዳልተፈቱ ገልፀው፥ የከተማዋ የኔትወርክ ችግር እስከጪው ሰኔ በሚከናወነው ማስፋፊያ እንደሚፈታ ተናግረዋል።
በመላው ሀገሪቱ እየተከናወነ ያለው የማስፋፋያ ስራም በመጪው ዓመት መጨረሻ ሲጠናቀቅ የሀገሪቱን የሞባይል ሽፋን ወደ ሶስት እጥፍ ያሳድገዋል ብለዋል።
በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመኖሪያ ቤት ስልክ ጋር ተያይዞ ያለውን የአገልግሎት አሰጣጥ ችግር ለመፍታትም እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
በሌላ በኩል ተጠቀሚውን እያወዛገቡ ያሉት ከውጭ የሚላኩ ሀሰተኛ የጽሁፍ መልእክቶችን ሙሉ በሙሉ ማስቆም አልተቻለም ያሉት አቶ አብዱራሂም፥ ሆኖም በመረጃ በማስደገፍ ሲያጭበረብሩ የተገኙትን ማስቆማቸውን ተናግረዋል።
********
ምንጭ፡- ፋና – ሚያዚያ 1 ፣ 2006 – ‹‹ኢትዮ ቴሌኮም በአዲስ አበባ በ75 ቦታዎች ላይ የኔትወርክ ችግርን ሙሉ በሙሉ መፍታቱን አስታወቀ››