አንድነት ፓርቲ:- በአምቦ ዳኖ ወረዳ አማራዎችን ዒላማ ያደረገ ማፈናቀል ተፈፀመ አለ

የአንድነት ፓርቲ ልሳን የሆነው ‹‹ፍኖተ-ነፃነት›› በምዕራብ ሸዋ ዞን አምቦ ዳኖ ወረዳ የአማራ ተወላጆችን ዒላማ ያደረገ ሕገ-ወጥ የዜጎች ማፈናቀል ተፈፀመ አለ፡፡

የዜናውን ትክክለኛነት ከገለልተኛ ምንጭ ማረጋገጥ ባንችልም የፍኖተ-ነፃነት ዜና እንደሚከተለው ይነበባል፡፡ (በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ መረጃ በተቻለ ፍጥነት እናቀርባለን)፡፡

*************

የፍኖተ-ነፃነት ዜና

ተፈናቃዩቹ ከጎንደር አካባቢ ተነስተው ከዛሬ 20 ዓመት በፊት ወደ ምዕራብ ሸዋ ዞን አምቦ ዳኖ ወረዳ በመውረድ በእርሻ ስራ የተሰማሩ ገበሬዎች ናቸው፡፡ከ1996ዓ.ም ጀምሮ በተለያየ ደረጃ ‹‹ክልላችንን ለቅቃችሁ ውጡ››ሲባሉ ቆይተዋል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ማስፈራሪያው ወደ ግድያ፣ድብደባና ወከባ በማደጉ ለአቤቱታ አካባቢያቸውን ጥለው አዲስ አበባ ለመግባት ተገደዋል፡፡ከተፈናቃዩቹ መካከል የተወሰኑት ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተ/ብርሃን ጽ/ቤት በማምራት አፈ ጉባኤውን ለማናገር ቢሞክሩም ሊያገኟቸው አልቻሉም፡፡የአፈ ጉባኤው ጸሐፊ ጉዳያችሁ ታይቷል ወደ መጣችሁበት ተመለሱ››ያለቻቸው ቢሆንም ተፈናቃዩቹ ‹‹ብንመለስ ሊገድሉን ስለሚችሉ አንመለስም››የሚል አቋም ይዘዋል፡፡

ከ26 የሚልቁ ሰዎች በአደባባይ ድብደባ ደርሶባቸው እጅና እግራቸው እንደተሰበረ የሚናገሩት ተፈናቃዩቹ‹‹አቶ ጌጡ ክብረት የተባለ ግለሰብ በገበያ ቦታ በገጀራ ተቆራርጦ ህይወቱ ማለፉን በሀዘን ስሜት ተውጠው ይናገራሉ፡፡

በአዲስ አበባ ማረፊያ ባለማግኘታቸው ለችግር መጋለጣቸውን የሚገልጹት ተፈናቃዩቹ ወደ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ጽ/ቤት በመምጣት ‹‹ፍትህ እንድናገኝ ለኢትዩጵያ ህዝብ ሰቆቃችንን አሰሙልን››በማለት ተማጽነዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ አቶ ስዩም መንገሻ ‹‹ህገ መንግስቱ በግልጽ እያንዳንዱ ዜጋ በፈለገው ክልል በመሄድ ንብረት ማፍራት እንደሚችል ቢደነግግም መሬት ላይ ያለው እውነታ ግን ህገ ወጥና አስቸጋሪ ነው››ብለዋል፡፡

*********

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories