በባህር ዳር አንድ የፖሊስ አባል 12 ሰዎችን ገደለ

በባህር ዳር ከተማ ልዩ ስሙ አባይ ማዶ በተባለ አከባቢ ፥ አንድ ግለሰብ 12 ሰዎችን ገደለ ፡፡ከስፍራው የደረሰን መረጃ ግለሰቡ ሰክሮ እንደነበር ነው የሚያመለክተው ።

የባህር ዳር ከተማ ፖሊስ ኮሚሽን መምሪያ ሀላፊ ኮማንደር ደረጀ አቻምየለህ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደገለፁት ፥ ግለሰቡ በውል ባልታወቀ ምክንያት በመንገድ ላይ በከፈተው ተኩስ ከሞቱት 12 ሰዎች በተጨማሪ ሌሎች ሁለት ሰዎች ክፉኛ ቆስለዋል ።

በሰዓቱም ግለሰቡን በቁጥጥር ስር ለማዋል ፖሊስ ክትትል ሲያደርግ እንደነበርና በመጨረሻም ራሱን በወንዝ ውስጥ በመወርወር ህይወቱን እንዳጠፋ ነው ያመለከቱት ።

ድርጊቱን የፈፀመው ግለሰብ የፖሊስ አባል መሆኑን የገለፁት ኮማንደሩ ፥ ድርጊቱን የፈፀመበት ምክንያት ግለሰባዊ እንደሆነ አመልክተዋል ።

ትናንት ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ በተፈፀመው ድርጊት ከሞቱት መካከል ሴቶች ፣ ህፃናትና አዛውንቶች ይገኙበታል ።ከተገደሉት ግለሰቦች መካከልም የሰባቱ የቀብር ስነ ስርዓት በደብረ አባይ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያን በጋራ ተፈፅሟል ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤት ግድያውን አስነዋሪ የጭካኔ ተግባር ሲል አውግዞታል:: ለሟች ቤተሰቦችም መፅናናትን ተመኝቷል::በቀብር ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ አያሌው ጎበዜም የክልሉ መንግስት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን በመግለፅ ለሟች ቤተሰቦች መፅናናትን ተመኝተዋል ።

የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ በግለሰቡ ድርጊት ህይወታቸውን ባጡ ዜጎች ህልፈተ ህይወት ምክንያት የተሰማውን ሀዘን ገልጿል ፡፡በእንዲዚህ አይነቱ ወንጀልም በህብረተሰቡና በፖሊስ መካከል ለአመታት የቆየው መልካም ግንኙነትም አይሻክርም ብሏል በመግለጫው ፡፡የፖሊስነት ሙያዊ ዲስፕሊን በጎደላቸው መሰል ፖሊሶችም ይህ አይነት ክስተት ደግም እንዳይፈጠር እንደሚሰራም ያለውን ቁጥርጠኝነት አረጋግጧል ፡፡ፖሊስ በጉዳዩ ላይ እያደረገ ያለውን ምርመራ እንዳጠናቀቀም ተጨማሪ መረጃ እንደሚሰጥ አስታውቋል::

**************

Source: Fana – May 13, 2013. Originally titled ” በባህር ዳር አንድ ግለሰብ ባልታወቀ ምክንያት 12 ሰዎችን ገደለ”.

Daniel Berhane

more recommended stories