(ባሃሩ ይድነቃቸው)
ወ/ሮ አስቴር ማሞ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማእረግ የመልካም አስተዳደር ሪፎርም ክላስተር አስተባባሪና የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር በመሆን ተሾሙ።
የወይዘሮ አስቴር ማሞን ሹመት የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝ ዛሬ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርበው አስፀድቀዋል።
ምክር ቤቱም ሹመቱን በሙሉ ድምፅ ያፀደቀ ሲሆን፥ ወይዘሮ አስቴር ማሞም በምክር ቤቱ ፊት ቃለ መሃላ ፈፅመዋል።
ወይዘሮ አስቴር የመጀመሪያ ድግሪያቸውን በቋንቋና ስነ ፅሁፍ የሰሩ ሲሆን፥ ሁለተኛ ድግሪያቸውን በኦርጋናይዜሽናል ሌደርሺፕ አግኝተዋል።
ከ1991 ዓመተ ምህረት እስከ 1993 ድረስ የዞን ካቢኒ አባል፣ ከ1994 እስከ 1997 የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ፣ ከ1998 እስከ 2002 የኢፌዴሪ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስትር፣ ከ2003 እስከ 2004 በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር በመሆን አገልግለዋል።
እስከ ተሾሙበት ቀን ድረስም የኦሮሚያ ክልል በምክትል ፕሬዚዳንት ማእረግ የፕሬዚዳንቱ የህዝብ ግኑኝነት አማካሪ በመሆን ሰርተዋል።
ወይዘሮ አስቴር ማሞ በአሁኑ ወቅት የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት/ኦህዴድ/ ምክትል ሊቀመንበር ናቸው።
*******
ምንጭ፡- ፋና – መጋቢት 30/2006