የህዳሴው ግድብ በ2006 መጨረሻ የሙከራ ስራ ይጀምራል

(ማርታ ዘሪሁን)

የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን ዛሬ ግንቦት 7/2005 ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኢንዱስትሪ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የ2005 ዘጠኝ ወራት የስራ አፈጻጸም ሪፖርቱን አቅርቧል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የተያዙና በኮርፖሬሽኑ እየተከናወኑ ያሉ አብዛኞቹ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የአፈጻጸም ደረጃ ከ50 በመቶ በታች መሆኑን መነሻ በማድረግ ለኮርፖሬሽኑ ኃላፊዎች ጥያቄዎች አንስተዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄኔራል ክንፈ ዳኘው አስፈላጊ የግንባታ ቁሳቁስ በማቅረብና አጠቃላይ በምህንድስና ስራዎች የሚታየው መዘግየት በእንፋሎት ሃይል ማመንጫ፣ በስኳር፣ በማዳበሪያና በሌሎች ፋብሪካዎች ግንባታ ላይ ተፅእኖ እየፈጠረ ነው ብለዋል፡፡

የገንዘብ አቅም ማነስና ከውጭ ለሚገቡ እቃዎች በገቢዎችና ጉሙሩክ የቀረጥ ሂደት ላይ ችግር ማጋጠሙንም በምክንያትነት አንስተዋል፡፡

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ግን ለግንባታው አስፈላጊ ቁሳቁስ እየቀረበለትና አጠቃላይ የምህንድስና ስራዎች እየተከናወኑለት በመሆኑ በጊዜው እንደሚጠናቀቅ ብርጋዴር ጄኔራል ክንፈ አብራርተዋል፡፡

የግድቡን ግንባታ የሚያከናውነው ሳሊኒ ኮንስትራክሽን የቅድመ ሃይል ማመንጫ ስራ በጥቅምት 2007 ለማስጀመር ሲያቅድ ኮርፖሬሽኑ ደግሞ በታህሳስ 2006 እንዲሆን አቅዶ ነበር፡፡ ሁለቱን እቅዶች በማጣጣም በነሐሴ 2006 ዓ/ም የቅድመ ሃይል ማመንጫ ስራ እንዲጀምር መታቀዱን ገልጸዋል፡፡

ምክር ቤቱ የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን በተለይም ዘመናዊና ደረጃውን የጠበቀ አሰራር በመዘርጋትና የተቋሙን ሠራተኞች ሙያዊ አቅምና አመለካከት በመገንባት ስራ ውጤታማ መሆኑን ገምግሟል፡፡

ሆኖም በግዙፍ ፕሮጀክቶች አፈጻጸም ላይ የሚታየውን መዘግየት ሊያስተካክል እንደሚገባ የቋሚ ኮሚቴው አሳስቧል፡፡

የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን በዘጠኙ ወራት በተቋራጭነትና በጥቃቅንና አነስተኛ የተደራጁትን ጨምሮ ከ31 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል ፈጥሯል፡፡

 ***********

Source: ERTA – May 15, 2013.

Daniel Berhane

more recommended stories