ሰማያዊ ፓርቲ| አማራ ብሔር አይደለም፣ ለኦሮምኛ የግእዝ ፊደል ይሻላል

የ‹‹ሰማያዊ›› ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት ከላይፍ መጽሔት ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ መጽሔቱ እንደሚከተለው አቅርቦታል፡፡ (ከላይ ያለው ርዕስ የኛ ነው)Semayawi Party Chairperson - Eng Yilkal Getnet

***********

ላይፍ ፡- ለፖለቲካ ስራ ሙሉ ጊዜን መስጠት በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ አስቸጋሪ አይሆንም?

ኢንጅነር፡- መኖር ስላለብኝ ጥቂት ስራ እሰራለሁ፣ የሚበዛውን ጊዜዬን ግን የማሳልፈው ለፓርቲው ስራ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ነገሮች ለምርጫ አስቸጋሪ ሲሆኑ የምትወስደው ውሳኔ አንዱን በማጠፍ ለአንደኛው ብቻ ራስህን መስጠት ይሆናል፡፡

ላይፍ ፡- የሚመሩት ፓርቲ ሰማያዊ የፖለቲካ ፍልስፍናው በምን ላይ የተመሰረተ ነው?

ኢንጅነር ፡- ጥያቄው ሰፋ ያለ ነው፡፡ በዋናነት ግን የፖለቲካ ፍልስፍናችን በግለሰብ መብት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ሴንተር ራይት ሞደሬት ሊበራሊዝምን የፖለቲካ አመለካከት እናራምዳን ብለን ነው የምናምነው፣ የግለሰብ መብት ከተከበረ የሁሉም መብት ይከበራል እንላለን፣ መብት ከግለሰብ ይጀምራል፡፡ ለምሳሌ ይልቃል ወንድ ነው ስለዚህ ጾታ አለው፣ ይልቃል ቋንቋ፣ ትምህርትና ሞያ ያሉት በመሆኑ ሌላ የተለየ ነገር አያስፈልግም፡፡ የእኔ መብት ከተከበረ የምናገረውም ቋንቋ ይከበራል ማለት ነው፡፡ ቡድንና ግለሰብ እኩል ይታያሉ የሚለው አመለካከት ምክንያታዊ አይደለም፡፡ ከቡድን በፊት ግለሰብ ይቀድማል፡፡ እናም የግለሰቡ መብት ሲከበር የቡድኑ ይከበራል ብለን እናምናለን፡፡ የፖለቲካ ድርጅት በየጊዜው ራሱን እያረመ የሚሄድ እንጂ በቅድመ ድንጋጌ ላይ ተመስርቶ ፖለቲካ ሊሰራ አይችልም፡፡ ለምሳሌ የጎሳ ድርጅት እንጂ የጎሳ ፓርቲ መሆን አይቻልም፡፡ እዚህ አገር ጉዳዩ በጣም ስስ በመሆኑ አንነካውም እንጂ አንድ ሰው የኦሮሞ ድርጅት ነኝ ብሎ ከተነሳ ከኦሮሞ ወዴት መሄድ ይችላል? ምክንያቱም ከመነሻው የተወሰነ ነው፡፡ በጎሳ መደራጀት አሁን እየተፈጠሩ ያሉ ነገሮች መነሻ ነው ብለን እናምናለን፡፡ በቡድን መብቶች መከበር እናምናለን፡፡ ነገር ግን የሁሉ ነገር ማጠንጠኛ በኢትዮጵያችን ውስጥ ጎሳ መሆን ይገባዋል የሚል አመለካከት የለንም፡፡

ላይፍ ፡ ገዢው ፓርቲ ዜጎችን ከመደራጀት ውጪ የማያውቅ የማይመስልበት ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ነው፡፡ የፌደራል ስርዓቱም ክልላዊነት፣ ቡድናዊነትና መንደርተኝነት እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል በማለት የፖቲካ ምሁራን ይተቻሉ፡፡ እናንተ ደግሞ የሁሉ ነገር መነሻ ግለሰብ ነው እያላችሁ ነው፡፡ እነዚህ ጫፎች እንዴት ይታረቃሉ?

ኢንጅነር ፡- ፖለቲካ ለጊዜው በሚፈጠር ንፋስ የሚነሳ መሆን የለበትም፡፡ ሩቅ አሻግረህ በማየትም አሰላለፍህን መቅረጽ ይኖርብሃል፡፡ ጎሰኝነት እዚህ አገር ውስጥ ከሰፋ አንተ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብለህ ብትሄድ ተቃውሞ ሊያጋጥምህ ይችላል፡፡ ይህ በመሆኑ ግን በቃ በማለት ነገሩን ተቀብለህ እንድትሄድ ሊያደርግህ አይገባም፡፡ የጎሰኝነት አመለካከት የመጣው ከቅኝ ገዢዎች ጋር ተያይዞ ነው፡፡ ቅኝ ገዢዎች ተገዢዎቹን ከፋፍለው ለመግዛት ያመቻቸው ዘንድ ተጠቅመውበታል፡፡ እንግሊዞች በዚህ መንገድ ብዙ ርቀት መጓዝ ችለዋል፡፡ ነገር ግን አሁን ይህ አመለካከት ስልጣንና አቅም ያገኘ በመሆኑ አገር እያተራመሰ ይገኛል፡፡ ምንም እንኳን የእኔ እበልጥ የእኔ እበልጥ ፉክክር ነግሶ አገራችንን ሊያጠፋብን የተቃረበ ቢሆንም የግለሰብ መብት መከበር ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል በማለት እየታገልን እንገኛለን፡፡ ኢትዮጵያዊያን ታላቅ ነበርን፣ ኢንተርኔት ውስጥ ገብተህ ስለ ኢትዮጵያ ለማወቅ ብትፈልግ ከአለማችን ጥንታዊ ህዝብ አንዷ ስለመሆኗ ትገነዘባለህ፡፡ ይህ የጎሳ አመለካከት ግን አሁን የተፈጠረና የቅርብ ጊዜ ታሪክ ነው፡፡ህዝቡ ወደቀደመው ታላቅነቱ መመለስ ይኖርበታል፡፡

ላይፍ ፡ – የነበረንን ብሔራዊና የአንድነት መንፈስ ያላላና ወደ ቡድናዊነት እንድናዘነብል ያደረገን ነገር በአንተ ዕይታ ምንድን ነው?

ኢንጅነር ፡- አንዳንድ ሰው ደርግን ብሔራዊ ስሜት የነበረው በማለት ሲያቀርበው እገረማለሁ፡፡ ደርግ አለም የወዛድሮች ትሆናለች የሚል አመለካከት ነበረው፡፡ ኢትዮጵያዊነት በአለም አቀፋዊ ወዛደራዊነት ጥላ ስር ገብቶ ነበር፡፡ ኢህአዴግ የደርግን አለም አቀፋዊ ወዛደራዊነት በብሔር ብሔረሰቦች ለወጠው፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ ይህንን አመለካከቱን ለማስረጽ በብዙ ነገሮች ላይ ዘምቷል፡፡ እኔ ዩኒቨርስቲ የገባሁት ኢህአዴግ ስልጣን በያዘበት ወቅት ነበር፡፡ በትምህርት ቤት ይሰጥ የነበረን የታሪክ ትምህርት አፋለሰ፣ ትልቅ ክብር ይሰጣቸው የነበሩ መመህራንን ከዩኒቨርስቲዎች እንዲባረሩ አደረገ፣ ከዚያ በመቀጠልም በኢትዮጵያ ውስጥ ትልቅ ትርጉም የነበረውን ሽምግልና አጠፋ፡፡ ሕዝቡ ሃይማኖተኛ በመሆኑ ለሃይማኖቱ ላቅ ያለ ግምት ይሰጣል፣ ኢህአዴግ በዚህ ዙሪያ ያሉ ሰዎችን በመያዝ የሃይማኖት ቤቶችን በካድሬዎች እንዲሞሉ አደረገ፡፡ የአገሪቱ አንኳር ነገሮችን በመያዝ ሚዲያውን በመቆጣጠር ለህዝቡ ውሸት መመገብ ጀመረ፡፡ እንግዲህ በዚህ ውስጥ ያለፈ አንድ የ20 አመት ወጣት ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ሽምግልና እና ትምህርት ከሌለው እንዴት ማንነቱን ማግኘት ይችላል? በእነዚህ ነገሮች ላይ በአቋም ደረጃ ተዘምቷል፡፡ የአገሪቱ ምሰሶ የነበሩ ነገሮች አሁን በቦታቸው አይገኙም፡፡ በአንድነት ውስጥ የነበረን ህዝብ በጎሳው እንዲሰባሰብ በማድረግ በህዝቡ መካከል አለመተማመን እንዲሰፍን ተደርጓል፡፡ የፖለቲካው ዋነኛ ኃይል ደግሞ ከጥቅም ጋር እንዲተሳሰር በመደረጉ አንድ ሰው ለምን ኢህአዴግ እንደሆነ ብትጠይቀው ምላሽ አይሰጥህም፡፡ ምክንያቱም ወደዚያ የሚሄደው የስራ ዕድል፣ የትምህርትና ሌሎች ጥቅሞችን እንደሚያገኝ የሚሰበክ በመሆኑ ነው፡፡ ብሔራዊ ስሜት የምንለውን ነገር ይህ መንግስት ያሳሳው በአጋጣሚ ሳይሆን ሆን ብሎ አስልቶ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡

ላይፍ ፡- ነገር ግን ኢህአዴግ የመንግስትነቱን ሚና መጫወት ከጀመረ ወዲህ ማንነታችን ተከበረ፣ በራሳችን ቋንቋ መናገር ጀመርን የሚሉ ቡድኖች ተፈጥረዋል፡፡ ኢህአዴግም የደርግን የአንድነት ፍልስፍና በመተቸት በልዩነታችን ውስጥ አንድነታችን እንዲወጣ አድርጊያለሁ ይላል፡፡

ኢንጅነር ፡- እኔ ምን እንደተገኘ አይገባኝም፡፡ በቋንቋ መናገር የሚባለውም ነገር አዲስ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ኢትዮጵያ ብትሄድ ህዝቡ በአማርኛ ሲናገር ታገኘዋለህ፡፡ አማርኛን ድሮ ይናገር ከነበረው ህዝብ አሁን የሚበልጠው ይናገረው እንዲሆን እንጂ አያንስም፡፡ መጻህፍት ከድሮ ይልቅ አሁን በአማርኛ በብዛት ይጻፋሉ፡፡ ድሮ ብዙ መጽሔት አልነበረም፡፡ አሁን ግን በዛ ያሉ መጽሄቶችን በአማርኛ ማግኘት ይቻላል፡፡ የተወሰኑ የየጎሳዎቹ ልሂቃን የራሳቸውን ጥቅም በማግኘታቸው ብቻ ካልሆነ በስተቀር አዲስ ነገር ተፈጥሯል የሚል ግምት የለኝም፡፡ ኦሮምኛ እኮ በኢህአዴግ ዘመን አልተፈጠረም፡፡ ድሮም ይነገር ነበር፡፡ ነገር ግን ቋንቋውን ለማስፋፋት የላቲን ፊደል ከመጠቀም የግእዝ ፊደልን ብንጠቀም ይሻል ነበር፡፡ ኢህአዴግ ሆን ብሎ ቅኝ ገዢዎች እንዳደረጉት ህዝቡን ለመግዛት እነዚህን ነገሮች ተጠቅሞባቸዋል፡፡ ኢህአዴግን በመጠጋት በአንድ ሌሊት ሚልየነር የሆኑ ሰዎች አሉ፡፡ ግን ደሀው ኢትዮጵያዊ ኦሮምኛ፣ አማርኛ ወይም ሲዳምኛ ይናገር የእርሱ ችግር አይደለም፡፡ ከስንዝር መሬቱ ጋር ተጣብቆ ከመኖር ውጪ ጠብ ያለለት ነገር የለም፡፡ ድሮም ገጠር ውስጥ ኦሮምኛ ይናገር ነበር አሁንም ይናገራል፡፡ ድሮም የከለከለው የለም፣ አሁንም ምንም አላገኘም፡፡ ተራ ፕሮፓጋንዳ እንጂ መሬት የያዘ ምንም ነገር የለም፡፡

ላይፍ ፡- ክልሎች የራሳቸውን አስተዳደር መርጠው ህግ በማውጣት እንዲተዳደሩ ስለመደረጋቸው ይነገራል፡፡ ማዕከላዊ የነበረው የመንግስት አወቃቀር ፌደራላዊ በመሆን ስልጣኑን ለክልሎች መስጠቱን ሰማያዊ ፓርቲ የሚመለከተው እንዴት ነው?

ኢንጅነር ፡- የፌደራል ስርዓት በራሱ መጥፎ አይደለም፡፡ እኛ ኢትዮጵያዊያን ለፌደራል አስተዳደር አዲስ አይደለንም፡፡ በየክልሉ ከድሮ ጀምሮ አስተዳዳሪዎች ነበሩ፡፡ ከ90 ሚልዮን ህዝብ በላይ የሚገኝባትን አገር በአሀዳዊ አስተዳደር ለመምራት መሞከር ትልቅ ችግር ነው፡፡ ክልሎች የራሳቸውን አስተዳደር በመመስረት ስልጣን ከማዕከላዊው መንግስት መጋራታቸው ጥሩ ነገር ነው፡፡ ችግሩ ግን ህዝቡን በጎሳ ከረጢት ውስጥ በመክተት በመከራውና በደስታው ወቅት አንድ የነበረውን ህዝብ ማለያየት ነው፡፡ ዘውዴ ነሲቡ የሚባሉ ሸዋ ውስጥ 130 አመት ኖረው ያረፉ ሰው ሲናገሩ ‹‹እርሱ የሲዳማ፣ የጎጃምና የወለጋ ሰው ነው›› ይሉ ነበር፡፡ ያኔ ሰውን በጎሳው ሳይሆን በሚኖርበት አካባቢ ባለው ተቀባይነት በመነሳት ይጠራ እንደነበር መረዳት እንችላለን፡፡ እኛም ብንሆን የፌደራል ስርአቱን በመቀበል የየክልሉ ሰዎች ክልላቸውን ያስተዳድሩ መባሉን እንደግፋለን፡፡ ድሮም እኮ የሸዋ፣ የትግሬ፣ የኦሮሞ ንጉስ የሚባሉ ነበሩ፡፡ እነዚህ የየክልሉ ንጉሶች የነበሩ ቢሆንም ለንጉሰ ነገስቱ ይገብሩ ነበር እንጂ እንገነጠላለን አይሉም፡፡ ቴክኖሎጂው ባልነበረበት ዘመን የነበሩ ነገስታት ከምንም በላይ ለአገራዊ አንድነት ቅድሚያ ሲሰጡ አሁን ላይ የሚገኙ የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሰር ነን የሚሉ ግን ኦሮሞን እንገነጥላለን ይላሉ፡፡ የኢህአዴግ ፌደራሊዝም የይስሙላ ነው፡፡ ፓርቲው ሶሻሊስት በመሆኑ መሰረቱ ማዕከላዊነት ነው፡፡ ጥቂት የበላይ አመራሮች ሁሉን ነገር የሚወስኑበት ፓርቲ ነው፡፡ ለክልሎች ሰጠሁ ያለውን ስልጣን ጣልቃ በመግባት ብዙ ጊዜ ሲያፍን ተመልክተነዋል፡፡ እንደውም ከኢህአዴግ ዘመን ይልቅ በድሮ ጊዜ የየክልሉ ገዢዎች የተሻለ ስልጣን ነበራቸው፡፡ የራሳቸውን ጦር በማደራጀት ያስተዳድሩ ነበር፡፡ አገራዊ በሆነ አጀንዳ ላይ ግን በህብረት ከሌሎች ጋር ይሰሩ ነበር፡፡ የኢህአዴግ የድርጅት ባህሪና ፌደራሊዝም አብረው መሄድ የሚችሉ ነገሮች አይደሉም፡፡ ይህ የአስመሳይነትና የአታላይነት የፖለቲካ ባህል ነው፡፡ በአጭሩ በእኛ አመለካከት የፌደራል ስርአት ጂኦግራፊውን፣ በውስጡ የሚኖሩ ህዝቦች በስነ ልቦና የተገናኙ መሆናቸውን፣ ቋንቋቸውን፣ ለአስተዳደር ምቹ መሆኑን የመዘነ መሆን ይገባዋል፡፡ በአንድ አገር ውስጥ ክፍላተ ሀገራት እንዲኖሩ በማድረግ ስልጣኑ የክፍላተ ሀገራቱ እንዲሆን እንታገላለን፡፡

ላይፍ ፡- ኢህአዴግ እኔ ባልኖር አገሪቱ ትበታተናለች በማለት ሁልጊዜም ሲናገር ይደመጣል፡፡ የመበታተን ስጋት ተጋርጦባት ለነበረች አገር የመሰረትነው የፌደራል አወቃቀር ፍቱን መድሀኒት ሆኗል ማለቱን እንዴት ይመለከቱታል?

ኢንጅነር ፡- እኛ የምንከተለው የአስተሳሰብ መስመር ከኢህአዴግ የተለየ ነው፡፡ ከጋራ ጉዳይ ይልቅ ልዩነትን በማጉላት አገርን እጠብቃለሁ ማለት አታላይነት ብቻ ነው፡፡ አሁን ባለው እውነታ የብሔረሰብ አስተዳደር አለን በማለት ብትጠይቀኝ ምላሼ የለም ነው፡፡ አገሪቱን እየመሩ የሚገኙት ጥቂት ቡድኖች ናቸው፡፡ ባንኩን፣ መከላከያውንና ሌሎቹን ቁልፍ ቦታዎች እየመሩ የሚገኙት ከአንድ አካባቢ የመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ የብሄር ጭቆና ከየትኛውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ ውስጥ ያለው በዚህ አገዛዝ ነው፡፡ ብዛት ያላቸው ነጻ አውጪ ድርጅቶች የተፈጠሩት እኮ በዚህ ወቅት ነው፡፡ የብሄር ጥያቄ ከተመለሰ እነ ኦብነግን የመሳሰሉ ድርጅቶች እንዴት ሊፈጠሩ ቻሉ፡፡ መከላከያው ውስጥ ምን ያህል የብሄር ብሔረሰብ ተወካዮች በአመራር ቦታው ላይ ይገኛሉ? ፖለቲካን ትንተና ብቻ ማድረግ የለብንም፡፡ መሬት ላይ ያለውን እውነታም ልንመለከትበት ይገባል፡፡

ላይፍ ፡- የአንድ ቡድን የበላይነት ወይም ከአንድ ክልል የወጡ ሰዎች የስልጣን መደላደሉን በመያዝ የወጡበት ክልል ወይም ብሄር ስልጣን መያዝ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል?

ኢንጅነር ፡- የቡድኑን ተጠያቂነት ያሳያል፡፡ ከዚህ በላይም ለማደናገሪያነት ይውላል፡፡ ለምሳሌ ህወሃት ይህን ነገር ተጠቅሞበታል፡፡ አንደኛ ስልጣን የያዙት የእኛ ልጆች ናቸው፡፡ ተዋግተዋል፣ ደምተዋል መስዋዕትነት በመክፈላቸው ስልጣኑን መያዝ አለባቸው የሚል ስነ ልቦና እንዲፈጠር ሆኗል፡፡ የትግራይ ሰዎች ከዚህ በመነሳት ነገሮችን በዝምታ ማየቱ በስሙ እንዲነገድበት ሆኗል፡፡ ነገር ግን ጥቂቶች ይህንን ተገን በማድረግ እየተጠቀሙ ነው፡፡ ህወሃቶች ለትግራይ ህዝብ እኛ ከሌለን ሌላው ያጠፋሃል በማለት ከቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር እንዲቃረን እያደረጉት ነው፡፡ የትግራይ ህዝብ ተጠቅሟል ለማለትም አመራር ላይ ያለው ቡድን በተወሰነ ደረጃ የሚያደርገው ነገር አለ፡፡ ማደናገሪያ ቢኖረውም በዚያ አካባቢ ያለው ሰው ፊት ለፊት ወጥቶ መናገር አለበት፡፡ ሌላው ሰው በእነርሱ ቅር እንዲሰኝ እያደረገ የሚገኘው ነገርም ለዘብተኝነታቸው ይመስለኛል፡፡ አሁን አሁን ግን ይህ ነገር እየተቀረፈ ነው፡፡ በመቀሌ ዩኒቨርሲቲና በአረና ፓርቲ ውስጥ ያሉ አንዳንድ ወጣቶች ብቅ እያሉ ነው፡፡

ላይፍ ፡- በቅርቡ በጉራፈርዳና ቤኒሻንጉል አካባቢ ወደተከሰቱ መፈናቀሎች እንምጣ፡፡ ዜጎች የአንድ ክልል ተወላጆች በመሆናቸው ብቻ እንዲፈናቀሉ ተደርገዋል፡፡ ይህ ነገር በእርስዎ እይታ በምን መንስኤነት የተፈጠረ ነው?

ኢንጅነር ፡- ከጥቂት ቀናት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ለፓርላማው ቀርበው ሲናገሩ እንደሰማሁት ችግሩ የተፈጠረው በአቅም ማነስና በብቃት ችግር አይደለም፡፡ ወይም እዚያ አካባቢ ያሉ ኃላፊዎች በሙስና ከመጨማለቃቸው የተነሳ የተፈጠረ ነው ማለታቸውንም አልቀበልም፡፡ ነገሩ የተፈጠረው በፖሊሲ ደረጃ በደንብ ተጠንቶ ነው፡፡ አንደኛ ይህ ነገር አሁን የተፈጠረ አይደለም፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት ፓርላማ ቀርበው ‹‹ ደቡብ ውስጥ ለመኖር በመጀመሪያ የደቡብን አስተዳደር መጠየቅ ይገባል›› ብለው ነበር፡፡ ስለዚህ ከክልላችን ውጡ የሚለው ነገር ፖሊሲው ከተቀረጸበት እውነታ በመነሳት የተፈጠረ ነው፡፡

ላይፍ ፡- ፖሊሲውን ወይም ንድፉን ያወጣው ማን ነው ?

ኢንጅነር ፡- ህወሃት ነዋ፡፡ አንተ ለመጽሔትህ በደንብ እንድናገርልህ ፈልገህ ካልሆነ በስተቀር ይህ የሚታወቅ ነው፡፡ የተጨቆነ ብሄረሰብ እንዳለ ካመንክ እኮ ጨቋኝ የምትለው አካል የግዴታ ይኖራል፡፡ ከዚህ አንጻር ድርጅቱ አማራን በጨቋኝነት በመፈረጅ የአማራን አከርካሪ እሰብራለሁ በማለት ተነስቷል፡፡ በ1997 ምርጫ ወቅት ኢህአዴግ በዋናነት በከተሞች አካባባቢ ከፍተኛ ሽንፈት ሲያስተናግድ መለስ አሁንም የአማራና የቀድሞ መንግስት ናፋቂዎች እንዳልጠፉ ተረድቻለሁ በማለት መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ እነዚህ ንግግሮች እየዋሉ እያደሩ እንዲህ አይነት ችግሮች እንዲፈጠሩ ምክንያት ሆነዋል፡፡ በአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ላይ ያነጣጠረ ማፈናቀል መከሰቱ ትልቅ ትኩረት ማግኘት ይኖርበታል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዘር ማጥፋት ወንጀል እየተፈፀመ ነው የሚለውን ክስ ለማስቀረት ሲሉ ችግሩ የተፈጠረው በጥቂት ሃላፊነት በማይሰማቸው ሰዎች ነው በማለት ነገሩን ለማድበስበስ ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን ኢህአዴግን ጠንቅቆ የሚያውቅ ሰው አንድ ተራ ባለ ስልጣን ከመሬት ተነስቶ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን እንዲፈናቀሉ ያደርጋል በማለት ለመናገር ይቸገራል፡፡ ሌላው አስገራሚ ነገር በአሁኑ ሰአት አማራ ብቻ ሳይሆን ኦሮሞም ተፈናቅሏል ለማለት ኦሮሞ ነን የሚሉ ሰዎች ከቤኒሻንጉል እንደተፈናቀሉ ሲናገሩ እያደመጥን ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች እስካሁን ድረስ የት ነበሩ ? ኢህአዴግ የመሬት ባለቤቶች ብሄር ብሄረሰቦችና ብሄሮች ናቸው ብሏል፡፡ በኢህአዴግ አመለካከት መሰረት እኔ የመሬት ባለቤት መሆን አልችልም፡፡በኢህአዴግ አስተሳሰብ ሁላችንም በህግ እኩል አይደለንም፡፡ ያለ ብሄርህ በመሄድ መሬት የምትዘው አንተ ማን ነህ? የሚለው አስተሳሰብ የመነጨው ስርኣቱ ከሚከተለው ፖሊሲ ነው፡፡

ላይፍ ፡- አንዳንዶች አቶ ኃይለማርያም በፓርላማው በመቅረብ ችግሩን በማመን በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ኃላፊነቱን የሚወስድ አካል እንደሚኖር መጠቆማቸውን እንደ በጎ ጅምር በመውሰድ መለስ ቢሆኑ ኖሮ ተፈናቃዮቹን መሬት ወራሪዎችና ተስፋፊዎች በማለት ይነቅፏቸው ነበር ይላሉ፡፡ በዚህ አስተያየት ይስማማሉ፡፡

ኢንጅነር ፡- አንዳንድ ሰው እንግዲህ ያለበትን ሁኔታ መቀየር ያስፈልገው ይሆናል፡፡ መለስም እኮ በተወሰነ ደረጃ አቋማቸውን እንደቀያየሩ የመጡበት መንገድ ማሳያ ሆኖ መቅረብ ይችላል፡፡ እንደውም እንደ መለስ ተገለባባጭ አይነት ሰው ተመልክቼ አላውቅም፡፡ ሲመጡ ሊበራል ዴሞክራሲ፣ ነጭ ካፒታሊዝም ነው የምናራምደው አሉ፡፡ መጀመሪያ ማሌለት ነበሩ፡፡ ከዛ 1997 ላይ ታማኝ ጠንካራ ተቃዋሚ ብናገኝ ግማሽ መንገድ ድረስ ተጉዝን እንቀበላለን አሉ፡፡ ነገር ግን የሆነው ከሆነ በኋላ ልማታዊ መንግስት ነን፣ መስመሩም ዴሞክራሲ ነው አሉን፡፡ አሁንም ቢሆን በህይወት ቢኖሩ ኖሮ የማይጠበቅ ነገር ሊናገሩ ይችላሉ፡፡ አውቃለሁ መለስ መሸነፍ የማይፈልጉ እልኸኛ ሰው ናቸው፡፡ ቢሆንም ግን አለም አቀፍ ጫናው የማያምኑበትን እንኳን እንዲናገሩ ሊያደርጋቸው እንደሚችል አምናለሁ፡፡ መለስ ወጥ አቋም የነበራቸው የመርህ ሰው አይደሉም፡፡ ዛሬ ያነበቡትን መጽሀፍ በመያዝ የሚከራከሩ ነገ ደግሞ የትናንቱን በመተው የሚቀየሩ በጓደኞቻቸው ዘንድም ተለዋዋጭ ተደርገው የሚወሰዱ ነበሩ፡፡ በእርግጥ የአቶ መለስ አይነት የትግል መሰረትና መነሳሳት አቶ ኃይለማርያም ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ምክንያቱም የመጡት ከትምህርት አካባቢ ነው ፡፡ ስለዚህ አማራውን ጨቋኝ በማድረግ በመሳል የመከትከት አላማ ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ከዚህ በመነሳት ነባራዊውን ሁኔታ ከግምት በማስገባት የተወለጠ ነገር ተናግረዋል፡፡ መለስም አቅም ሲያጡና የሚገቡበት ሲጠፋቸው እንዲህ ሊናገሩ ይችሉ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን ግን ከንግግር ያለፈ ነገር አለመደረጉ መሰመር ይገባዋል፡፡ ተፈናቅለው ለነበሩ ሰዎች ምን ተደረገ ? ንብረታቸውን በትነውና የልጆቻቸውን ትምህርት አቋርጠው ለሶስት ወራት ያህል ሲንከራተቱ መንግስት ምን ይሰራ ነበር ? የአሁኑ ንግግር ከጫና የመጣ እንጂ አምነውበት የተናገሩት አይደለም፡፡ ኃይለማርያም ምናልባት የአፈጻጸም ችግር በማለት በግልጽ ተናግረው ይሆናል፡፡ መለስ በዚህ ቦታ ቢሆኑ ኖሮ ነገሩን በብልጣብልጥነት ለማለፍ ይሞክሩት እንደነበር ይሰማኛል፡፡

ላይፍ ፡- ሁኔታውን ለማጣራት ወደ ቤንሻንጉል ክልል የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ማምራታችሁንና ለተወሰኑ ሰዓታትም መታሰራችሁን ሰምተናል፡፡ እስኪ በአጠቃላይ ስለተፈጠረው ነገር ይንገሩን?

ኢንጅነር ፡- እውነት ለመናገር ስራ ስትሰራና ስትንቀሳቀስ ለአምስት ሰዓታት ያህል ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ እንድትቆይ መደረግህ ያን ያህል የሚወራለት አይሆንም፡፡ ይህ ግን የሚያሳየው ዜጎች በነጻነት ከቦታ ቦታ ተዘዋውረው መረጃ ማግኘት እንደማይችሉ ነው፡፡ በተጨማሪ ደግሞ በእኛ ላይ እንዲህ አይነት ነገር ያደረጉ ሰዎች እዛ በሚኖሩ ሰዎች ላይ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ እንድናስብ ያደርገናል፡፡ ከዜጎች ጋር በመገናኘታችን ብቻ ይህንን እርምጃ ከወሰዱ መሬታችንን ወስዳችኋል በሚሏቸው ሰዎች ላይማ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ ማሰብ በራሱ ይከብዳል፡፡ ተፈናቃዮቹ በአፋጣኝ ይዞታቸውን እንዲለቁ በመደረጋቸው ዘጠኝ ሺ ብር የምትሸጥ ላም በአንድ ሺህ አምስት መቶ ሸጠዋል፡፡ ተንቀሳቅሰን የተመለከትነው ሶስት ቀበሌዎችን ነው፡፡በአንድ ቀበሌ 58 ሰው በህገ ወጥ መንገድ ስለገባችሁ እንድትለቁ የሚል ወረቀት በይፋ ነው የተለጠፈባቸው፡፡

ላይፍ ፡- የትና ማን ነው የለጠፈው ? ወረቀቱስ ማህተም ነበረው ?

ኢንጅነር ፡- ማህተሙ የቀበሌ ገበሬ ማህበር ነው፡፡ ወረቀቱ ሌላው ቀርቶ ያላችሁን ንብረት ሸጣችሁ እንድትለቁ በማለት ያዛል፡፡ እቃቸውን እንኳን ይዘው የመውጣት መብት አልነበራቸውም፡፡

ላይፍ ፡- ንብረታቸውን እንዲህ በወረደ ዋጋ የገዛው የአካባቢው ማህበረሰብ ነው ?

ኢንጅነር ፡- የሚገዛ በማጣታቸው እኮ ነው ከመጣል ብለው የሸጡት፡፡ ዘጠኝ ሺህ ብር የሚያወጣ ላም በአንድ ሺህ ብር ስለተሸጠ ሸጠው ወጡ በማለት መናገር አይቻልም፡፡ እኔ ጥለው በትነው ወጡ ነው የምለው፡፡ እንዲመለሱ ከተደረገ በኋላ የአማራ ክልል ኃላፊዎች መጡ ተባለ፡፡ ነገር ግን ምንም ያደረጉላቸው ነገር የለም፡፡ ሰዎቹ እኮ ዝርፊያና ድብደባ ጭምር ተፈጽሞባቸዋል፡፡

ላይፍ ፡- ድብደባውን የፈፀሙት ይታወቃሉ ?

ኢንጅነር ፡- ፖሊሶችና የአካባቢው ታጣቂዎች ናቸው፡፡ እኔ ካናገርኳቸው ተፈናቃዮች መካከል 60 ሺህ ብር የተወሰደበትና 60 መሃለቅ የአንገት ወርቅ የተነጠቀች እናት ይገኙበታል፡፡ በሰደፍ የተደበደቡ ሰዎች ቁስላቸው ገና ባለመድረቁ ድብደባው ያደረሰባቸውን ጉዳት መመልከት ይቻላል፡፡

ላይፍ ፡- ያለ ፍላጎታቸው እንዲፈናቀሉ የተደረጉት የአማራ ብሄር ተወላጆች በድጋሚ ያለ ፍላጎታቸው ተገድደው ወደ ቤንሻንጉል እንዲመለሱ ስለመደረጋቸው አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ዙሪያ የተመለከቱት ምንድን ነው ?

ኢንጅነር ፡ እነርሱ ምንም አይነት ስልጣን እዚህ ውስጥ የላቸውም፡፡ በኃይል እንዲወጡ እንደተደረጉ ሁሉ በኃይል እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ሲሄዱም ሆነ ሲወጡ የእነርሱ ፈቃድ አልተጠየቀም፡፡

ላይፍ ፡- ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደተናገሩት ይህንን ድርጊት የፈፀሙ ኃላፊዎችን በማንሳት ብቻ መፈናቀሉ እንዲቆም ማድረግ ይቻላል ብለው ያምናሉ ?

ኢንጅነር ፡- አይቆምም፡፡ አንድ ሰው በኢሳት ተጠይቆ እኮ ‹‹ ምንግዜም ችግር ሲመጣባቸው በእኛ ላይ መለጠፋቸው የተለመደ ካልሆነ በስተቀር ክልሉ ሳያውቀው የተሰራ ምንም ነገር የለም›› ብሏል፡፡ ነገሩ በፖሊሲ ደረጃ ተይዞበት የተሰራ ስለመሆኑ ምንም መከራከርያ አያስፈልግም፡፡

ላይፍ ፡- የአማራው ውክልና አለኝ የሚለው ብአዴን በጉዳዩ ዙሪያ ዝምታን መምረጡን እንዴት ተመለከቱት ?

ኢንጅነር ፡- ቅድም እኮ ብዬሃለሁ፡፡ እዚህ አገር የፌደራል አስተዳደርም ሆነ ስልጣን ያላቸው ፓርቲዎች የሉም፡፡ አገሩን የሚመራው የተወሰነ የፖለቲካ ቡድን ነው፡፡ ጣልያን በወረራው ወቅት የተወሰኑ የጎሳ መሪዎችን በመሾም ቅኝ ግዛቱ ሊያደርግን ሞክሮ ነበር፡፡ ሌላው አማራ የሚባል ጎሳ(ብሄር) መኖሩን አማሮች የምትላቸው ሳይቀሩ አያምኑም፡፡ ለምሳሌ እኔ ጎጃም ነው የተወለድኩት፣ ከጓደኞቼ ጋር ስንጨዋወት እስላም አማራ እንላለን እንጂ አማራ ጎሳ ስለመሆኑ አናውቅም፡፡ እኔ አማራ የሚባል ጎሳ ስለመኖሩ የሰማሁት ዩኒቨርስቲ ከገባሁ በኋላ ነው፡፡ አማርኛ ተናጋሪው በብሔረሰብ የሚያምን አይደለም፡፡ እንደው ከአንዳንድ አክራሪዎች ጋር እንዳታጣለኝ እንጂ አማራ የሚባል ጎሳ(ብሄር) ስለመኖሩ የሚያሳይ ማስረጃ የለም፡፡ ልክ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ ከዚህ ወጣ እዚህ ገባ እንደሚባለው አይነት ማስረጃ የለም፡፡ አማራ የሚለውን ቃል የሚጠቀሙበት እስላም ክርስቲያን ለማለት ነው፡፡ ይህ የህብረተሰብ ክፍል ከበሮ ተመትቶ አገር ተወረረች ሲባል ሆ ብሎ ተነስቶ ጦርነት ይገጥማል፡፡ባህሉ፣ ሃይማኖቱና አመለካከቱ ሁሉ በኢትዮጵያዊነት የታጠረ ነው፡፡ ይህንን የሚያደርገው የተለየ ጥቅም በማግኘቱ አይደለም፡፡ ከኩርማ መሬት ውጪ በየትኛውም ስርዓት ተጠቃሚ አልሆነም፡፡

ላይፍ ፡- ምናልባት ግን መፈናቀሉ በዋናነት አማራው ላይ ያነጣጠረው አማራውን የሚወክል ድርጅት ባለመኖሩ ይሆን ?

ኢንጅነር ፡- እኔ እንዲህ አይነት ድርጅት መኖር አለበት ብዬ አላምንም፡፡ የእነዚህ ሰዎች አስተሳሰብ ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ በጎሳው ለማያምን ሰው የሆነ የጎሳ ድርጅት ማቋቋም ተገቢ ነው ብዬ አላስብም፡፡ አማራው በጎሳ እንዲታጠር ከተደረገም ኢትዮጵያ አለቀላት ብዬ ነው የማምነው፡፡

ላይፍ ፡- በቅርቡ የቀድሞው የህወሃት አንጋፋ ታጋይ አቶ ስብሃት ነጋ ኢህአዴግ የአፍሪካ ምርጡ ፓርቲ ነው በማለት መናገራቸው ተሰምቷል፡፡ በእርስዎ ደረጃ ኢህአዴግ ግን የት ያስቀምጡታል ?

ኢንጅነር ፡- በመጀመሪያ ደረጃ ኢህአዴግ የሆነ የፖለቲካ መስመር የሚከተል ድርጀት አይደለም፡፡ ከህወሃት አንስቶ ዝብርቅርቅ ያለ መስመር የሚከተል አንድ አይድኦሎጂ የሌለው ነው፡፡ ቀደም ብዬ ለመጠቆም እንደሞከርኩት ብሄራዊ ስሜት፣ ታሪክን፣ ባህልንና ማንነትን ያዋረደ ነው፡፡ ጉልበት በእጁ በማስገባቱም ሁሉንም አዳክሞ እየገዛ ነው፡፡ አዎን ከዚህ አንጻር ከሆነ ስብሃት እንዳሉት የአፍሪካ ምርጡ ፓርቲ ነው፡፡

**************

Daniel Berhane

more recommended stories