ቡና የሀገራችን መለያ (ብራንድ) መሆን አለበት

(ስንታየሁ ግርማ)

አለም በምርትና በገበያ በጥብቅ በተሣሠረችበት በዘመነ ግሎባላይዜሽን ሀገራት ሁሉ አንፃራዊ ብልጫቸውን በመለየት እና በማስተዋወቅ ይወዳደራሉ፡፡ ሀገራት እራሳቸውን ለመሸጥ ከባድ ውድድር ያደርጋሉ፡፡ በውድድሩ አሸናፊ በመሆን ልዩ መለያቸውን(ብራንድ) በመለየት በቅንጅት ይንቀሣቀሣሉ፡፡ የተለየ መለያቸውን(ብራንድ) የማያስተዋውቁ ሀገሮች ደግሞ ሌሎች እነሱን በአሉታዊ መልኩ እንዲገልፁሏቸው መፍቀድ ነው፡፡

ታዋቂው የአለም 3ኛ ቢልየነር ዋረን ቡፌት ስለመለያ ጠቀሜታን ሲያስረዱ ልዩ መለያህን ለመገንባት ሃያ ዓመታት ይፈጃል፡፡ ለማፍረስ ደግሞ አምስት ሰከንድ ይበቃል፡፡ ስለዚህ በድርጅታችን የሚያደርስ የገንዘብ ጉዳት በጣም ከፍተኛም ቢሆን እታገሳለሁ፡፡ በድርጅቱ ገፅታ ላይ በሚደርስ ጉዳት ግን ምህረት ሊኖረን አይገባም ይላሉ፡፡ ዋረን ቡፌት የድርጅታቸውን መለያ ይበልጥ ለመገንባት የአለም ኢኮኖሚ ቀውስንም እንደመልካም አጋጣሚ ተጠቅመውበታል፡፡

እ.ኤ.አ. በ2008 የተፈጠረው የአለም ኢኮኖሚ ቀውስ አንዱ ምክንያት ፍትሃዊ ያልሆነ የግብር አከፋፈል ነው የሚል እምነት አላቸው ለዚህም ራሳቸውን እንደምሣሌ ያቀርባሉ፡፡ ዋረን ቡፌት የአሜሪካ የግብር ምጣኔ ገቢ በጨመረ ቁጥር የግብር ምጣኔው እየቀነሰ መሄድ (Regressive Tax Rate) በሀብታምና በድሃ መካከል ያለው ልዩነት እየሰፋ የመጣው ይላሉ፡፡ ቡፌት እሳቸው 15 በሆነ የግብር ምጣኔ ታክስ ሲከፍሉ ፀሀፊያቸው 35 በመቶ የሆነ የታክስ ምጣኔ መክፈላቸው ፍትሃዊነት የጐደለው ነው በማለት ይተቻሉ፡፡ ብልህ የሆኑ ሠዎች፣ ኩባንያዎችና ሀገሮች ቀውስን ሳይቀር የድርጅታቸውን ተቀባይነት ለማሣደግ ይጠቀሙበታል፡፡

ሀገራት ምህረት በሌለው የዘመነ ሉአላዊነት(ግሎባላይዜሽን) ተወዳዳሪ እና አሸናፊ ለመሆን የተለያዩ የመለያ(ብራንድ) የማስተዋወቅ ሥራዎችን ይሠራሉ፡፡ ይህንን ለማድረግ በሀገር ደረጃ ከሁሉም የተሻለ ተቀባይነት ያለው ምርትን(አገልግሎትን) በመለየት በቅንጅት ይሠራሉ፡፡ መንግስት የግል ባለሀብትና ሲቭል ማህበራቱ በጋራ የሚሠሩበትን ስርዓት ይዘረጋሉ፡፡ መለያቸውን በየጊዜው የባለድርሻ አካላትን በማሣተፍ ይገመግማሉ፡፡ የብራንድ ባለሙያዎች እንደሚሉት የተለያዩ መለያዎችን መጠቀም ሀገራትን መለያ በቀላሉ ሸማቹ እንዳይረዳው ያደርጋል፡፡ ቱሪዝም የሴክተሩ መለያ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ የሀገር መለያ ማድረጉ አዋጭነቱ አመርቂ አይደለም ይላሉ፡፡

ግብፅ ለምሣሌ እራሷን በቱሪዝም ለማስተዋወቅ በምታደርገው ጥረት የግብፅ የተለዩ የምግብ ዓይነቶችን በማቅረብ እጥረት ያለበት በመሆኑ ቱሪስቶች ምሬታቸውን እንደሚገልፁ ተዘግቧል፡፡ ስለዚህ ለሀገራት ዋነኛ መለያ መሆን ያለበት አንፃራዊ ብልጫ በያዙበት ልዩ ምርት(አገልግሎት) መሆን እንዳለበት ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡ ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ መለያ መሆን ያለበት ቡና፣ ጤፍ፣ አትሌቲክስ ወዘተ የሚለው በቂ ትንታኔ ተሠርቶበት ወደሥራ ቢገባ ሀገሪቱን በአለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ አድርጐ የበለጠ ተጠቃሚ ያደርጋታል፡፡

Photo – President Obama at Ethiopian National palace, women in traditional dress serving coffee

በፀሀፊው እምነት የኢትዮጵያ መለያ መሆን ያለበት ቡና ነው፡፡ ምክንያቶች ደግሞ ኢትዮጵያ የቡና መገኛ ሀገር ናት፡፡ ቡና የሚለውም ሆነ Coffee የሚለው የእንግሊዘና ቋንቋ በቀላሉ ሊያያዝ የሚችል ነው፡፡ በአለም ላይ በየቀኑ 2.25 ሚሊዮን ስኒ ቡና ይጠጣል፡፡ በየዓመቱ 100 ቢሊዮን ዶላር የቢዝነስ ልውውጥ ይካሄድበታል፡፡ ከነዳጅ ቀጥሎ ከፍተኛ መሆኑ ነው፡፡ ቡና አነቃቂ እና በቀላሉ በሌሎች ምርቶች ሊተካ የማይችል በመሆኑ ሸማቹን የመያዝ አቅሙ ከፍተኛ በመሆኑ ከሌሎች የግብርና ምርቶች በአንፃራዊ መልኩ የሚያጋጥመው የመዋዥቅ ምጣኔ አነስተኛ ነው፡፡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት እድሜያቸው ከ18 ዓመት በላይ ከሆኑ አሜሪካኖች መካከል 5ዐ በመቶ በየቀኑ ቡና ይጠጣሉ፡፡

በፍጥነት በማደግ ላይ ካሉ ሀገሮች መካከል የቻይና ህዝብ አሥር በመቶ በየቀኑ ቡና የመጠጣት ሱስ ቢይዘው ተጨማሪ ገበያ ማለት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ በሀገራችን ያሉ ቻይናውያን ቡናን እንዲለምዱ ማድረግ ይቻላል፡፡ የተለያዩ የቡና ቀኖችን በመሰየም በስምፓዚየሙ፣ በየወርክሾኘ በየጉባኤዎች ወዘተ ቡናን ማስተዋወቅ ይረዳል፡፡ ታዋቂ አትሌቶች እና ሠዎች ቡናን እንዲያስተዋውቁ በማድረግ የኢትዮጵያ መለያ(ብራንድ) ማድረግ ይቻላል፡፡ የሚተዋወቀው ምርት/አገልግሎት/ አዋጭ እንዲሆን ከተፈለገ ምርት(አገልግሎት) በአለም ህብረተሰብ ተቀባይነት ያለው መሆን አለበት፡፡ ቡና በቢሊዮን የሚቆጠር የአለም ህዝብ ተቀባይነት ያለው በመሆኑ የሀገር መለያ ከመሆን አኳያ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የኢትዮጵያ ቡና ልዩ ጣዕም ያለው መሆኑ በአለም ዓቀፍ ታዋቂ መገናኛ ብዙሃን ተዘግቧል፡፡ ብዙ ጥናቶች የቡናን ጠቀሜታዎች አስቀምጠዋል፡፡

ሲጠቃለል በአለም አቀፍ ደረጃ ቡናን ለማስተዋወቅ የሚከተሉትን የህዝብ ግንኙነት መሣሪያዎች መጠቀም ጥሩ ነው፡፡

1. ታዋቂ ሠዎች በተለይ አትሌቶች በአለም አቀፍ ሚድያዎች ቡናን እንዲያስተዋውቁ ማድረግ፣

2. ታዋቂ የአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ስለኢትዮጵያ ቡና የፃፉትን መጠኑንና ጥራቱን ሞኒተር በማድረግ ጥቅም ላይ ማዋል ለምሣሌ ጥሩ የሚዘግቡትን ወደ ቡና አምራች ቦታዎች በመውሰድ እንዲጐበኙ ማድረግ፣

3. የተለያዩ ትላልቅ ሁነቶችን በማዘጋጀት ቡናን ማስተዋወቅ፣

4. የመንግስት ባለሥልጣናት እና አምባሳደሮች በውጭ ሀገር ሲንቀሳቀሱ ቡናን እንዲያስተዋውቁ ማድረግ ለቡና ገበያ ሁኔታዎች እንዲመቻቹ የማሳመን ሥራ እንዲሠሩ ማድረግ፣

5. ዋጋቸው ተመጣጣኝ በሆነ እና ተቀባይነት ባላቸው ሚድያዎች የማስተዋወቅ ሥራ መስራት፣

6. የሀገር(የመንግስት) የሚኒስትሮች እና የቱሪዝም ድርጅቶች፣ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን የቡናና ሻይ ልማት እና ግብይት ባለሥልጣን ድረ-ገፆች፣ ማህበራዊ ሚዲያዎች ቡናን እንዲያስተዋውቁ ማድረግ፣

7. ለቡና አምራቾች ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ከሚሰሩ አለም አቀፍ ተቋማት ማለትም እንደ ኦክስፋምና የመሳሰሉት ጋር አብሮ መስራት፣

8. ራስን ማስተዋወቅ ከፍተኛ የቴክኖሎጂ እድገትንና ብቃትን የሚጠይቅ በመሆኑ ከዓለም አቀፍ የህዝብ ግንኙነት ተቋማት ጋር በጋራ መስራት፣

ይህንን ለማድረግ ባለድርሻ አካላትን ያሣተፈ እና በጥናቱ ላይ የተመሠረተ የሀገር መለያ(ብራንድ) መለየት እና መግባባት ላይ መድረስ ያስፈልጋል፡፡ የሀገር መለያ(ብራንድ) ለመለየት በሀገር አቀፍ ደረጃ ሥራውን የሚመራ ግብረ ሀይል ማቋቋም አስፈላጊ ነው፡፡ ዋሊ ኦሊንስ በእንግሊዝ የብራንድ ባለሙያ ናቸው፡፡ እሳቸውን እንደሚሉት ከሆነ ሀገርን ማስተዋወቅ ሰባት ደረጃዎች ማለፍ አለበት፡-

1. ከመንግስት፣ ከኢንዱስትሪ፣ ከጥበብ፣ ከትምህርት እና ከሚዲያ የተፈጠረ ግብረ ሃይል በማቋቋም መርሃ ግብር እንዲቀረፅ ማድረግ፣

2. ሀገሪቱ በራስ ዜጐች እና በውጭ አለም ሰዎች እንዴት እንደምትታይ በጥናት መለየት፣

3. የተገኘውን ውጤት ከተፅእኖ ፈጣሪ ሠዎች ጋር የምክክር መድረክ በማድረግ እና በማወዳደር የሀገሪቱን ጠንካራ እና ደካማ ጐን መለየት፣

4. ኘሮፌሽናል ባለሙያዎች እና አማካሪዎችን በመጠቀም የብራንድ ስትራቴጂ የሚመራበትን ማዕከላዊ ሃሣብ መፍጠር፣ ማዕከላዊ ሀሣቡ በጣም ጠንካራና በቀላሉ ሊያያዝ የሚችል ሀሣብ ሆኖ የሀገሪቱን የተለየ ልዩ ገፅታ የያዘ መሆን አለበት፡፡ ሌሎች ኘሮግራሞች በዚሁ የሚመሩ መሆን አለባቸው፡፡

5. ማዕከላዊ ሀሣብ ሎጐን ጨምሮ የሚተላለፍበትን ዘዴዎች መለየት፣

6. የተቀረፀው ማዕከላዊ ሀሣብ ከቱሪዝም፣ ከኢንቨስመንት ለመሣብ እና ከኤክስፖርት እንዴት እንደሚቀናጅ እና ለእያንዳንዱ አድማጭ፣ ተመልካች(ሸማች) ተስማሚ የሚሆን መልዕክት መቅረጽ እና መተግበር፣

7. ከግብር ሀይሉ ጋር የሚያገናኝ ስርዓት መዘርጋት ናቸው፡፡

**************

Guest Author

Guest Author

Recent Posts

ኪዳነ ኣመነ – እንደህዝብ አንድ ሆነናል ያስቸገረን የህወሓት አስተሳሰብ ነው

ከብሔራዊ ባይቶ ኣባይ ትግራይ (ባይቶና) አመራር ኪዳነ አመነ ጋር የተደረገ ቃለ-ምልልስ ክፍል 2 - ለውጥ…

5 years ago

ኪዳነ አመነ – ለትግራይ ታላቅነት ሼምለስ ሆነን እንሰራለን

ከብሔራዊ ባይቶ ኣባይ ትግራይ (ባይቶና) አመራር ኪዳነ አመነ ጋር የተደረገ ቃለ-ምልልስ ክፍል 1 - ለትግራይ…

5 years ago

መኮንን ዘለለው – ትዴት ኢትዮጲያዊ ማንነት ብቻ እንዳለ ነው የሚያምነው (video)

የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ትብብር (ትዴት) አመራር መኮንን ዘለለው ከሆርን አፌይርስ ጋር ያደረጉት ቃለመጠይቅ (ክፍል 2)- ስለትዴት…

5 years ago

መኮንን ዘለለው – ኢሳት የትግራይ ህዝብ እንዲጠፋ ነው የሰራው (Video)u

የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ትብብር (ትዴት) አመራር መኮንን ዘለለው ከሆርን አፌይርስ ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ (ክፍል 1) -…

5 years ago

የበረከት ስምዖንና ታደሰ ካሳ መታሰር -ሕጋዊ ወይስ ፖለቲካዊ እርምጃ?

(የማነ ካሣ) እንደሚታወቀው አቶ በረከት ስምዖን እና አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) ከጥረት ኮርፖሬሽን ጋር በተያያዘ…

5 years ago

ኣስተያየት በ’ኣብራክ’ ልብወለድ ድርሰት ላይ

(መርስዔ ኪዳን - ሚኔሶታ) ኣብራክ የተባለውን የሙሉጌታ ኣረጋዊ መጽሓፍ ኣነበብኩት። ኣገራችን ከሊቅ አስከደቂቅ በዘውጌ ብሄርተኝነት…

5 years ago