(ስዩም ተሾመ)
የሀገር ብልፅግና እንዲረጋገጥ በሁሉም የሕይወት ዘርፎች ቀጣይነት ያለው እድገት እና መሻሻል ሊኖር ይገባል። ይህን ማድረግ የሚቻለው የእድገትና መሻሻል መንፈስ በማሕብረሰቡ ዘንድ ማስረፅ ሲቻል ነው። የእድገት እና መሻሻል መንፈስን የሚፈጠረውና በማሕብረሰቡ ዘንድ የሚሰርፀው ዜጎች በሚያደርጉት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ልዩነት ሲኖር ነው። በመሆኑም፣ የእድገት እና መሻሻል መንፈስ እንዲኖር በግለሰብ’ም ሆነ በቡድን በሚደረጉ ማህበራዊ፣ በፖለቲካዊና ኢኮኖሚዊ እንቅስቃሴዎች ዘንድ ልዩነት ሲኖርና ልዩነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ መቀጠል ሲቻል ነው።
ከሁሉም የሕብረተሰብ ክፍሎች ጥቅም፣ በአጠቃላይ ከሀገር ብልፅግና እና እድገት አንፃር ሲታይ፣ ልዩነት ምንግዜም ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም። ምክኒያቱም፣ እያንዳንዱ የሕብረተሰብ ክፍል በእራሱ የሕይወት ፍልስፍና እና መርህ ላይ ተመስርቶ በሚንቀሳቀስበት ወቅት ለራሱም ሆነ ለሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች አዲስ ልምድና ተሞክሮ ያስገኛል።
የተወሰነ የሕብረተሰብ ክፍል የሚከተለው አቅጣጫ ለራሱና ለሀገሪቱ ብልፅግናን ከማምጣት አንፃር ጠቃሚ ወይም ጎጂ ሊሆን ይችላል። የሄዱበት አቅጣጫ ጠቃሚ ሆኖ ከተገኘ ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች እንዲከተሉት ምክንያት ይሆናል፣ ጎጂ ሆኖ ከተገኘ ደግሞ ለራስና ለሌሎች ትምህርት ይሰጣል። አንዳችን የምንከተለው የሕይወት መንገድ ትክክለኝነቱን ለሌላችን ለማረጋገጥ በምናደርገው የማያቋርጥ ጥረት ሁሌም አዲስ ተሞክሮና ልምድ መቅሰም ያስችለናል። በዚህ መልኩ፣ ሁላችንም በግላችን ‘መልካምና ትክክል ነው’ ብለን በመረጥነው መንገድ ስንጓዝ ለውጥና መሻሻል መንፈስ በሕብረተሰቡ ውስጥ ይሰርፃል። ስለዚህ፣ ልዩነት ባለበት ሁልግዜም አዲስ ነገር አለ። አዲስ ተሞክሮ እና ተጨማሪ ዕውቀት ባለበት እድገትና መሻሻል አለ። በተቃራኒው ልዩነት በሌለበት ማህብረሰብ ወይም ሀገር የለውጥና መሻሻል መንፈስ አይኖርም፣ እድገት እና ብልፅግናን ማረጋገጥ አይቻልም።
ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው ልዩነት ሊገለፅ የሚችለው የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች በሚያደርጉት ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚዊ እንቅስቃሴዎች፣ እንዲሁም እንቅስቃሴያቸውን ከሚመሩበት የሞራል እሴቶች አንፃር ነው። ይህም አንድ ግለሰብ ወይም ቡድን ከሌላው ጋር በሚያደርገው ግንኙነት የሚገለፅ ይሆናል። አንድ ግለሰብ ከሌላ ግለሰብ/ቡድን፣ እንዲሁም አንድ ቡድን ከሌላ ቡድን/ግለሰብ ጋር የሚያደርገው ግንኙነት የሚመራበት ማህበራዊ ሥርዓት ‘የፖለቲካ ሥርዓት’ የምንለው ሲሆን ግንኙነቱ የሚመራበትን መርህ የሚያስቀምጠው እና የሚቆጣጠረው የፖለቲካ ሃይል አካል ያለው “መንግስት” ነው።
ስለዚህ፣ በምናደርገው ማህበራዊ እንቅስቃሴ ልዩነት እንዲኖር ከተፈለገ የፖለቲካ ሥርዓቱ የዜጎችን ‘ነፃነት’ ማክበርና ማስከባር ይኖርበታል። በአጠቃላይ፣ በማህብረሰቡ ውስጥ የለውጥና መሻሻል መንፈስ እንዲሰርፅ፣ በማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ሕይወት እድገትና ብልፅግና እንዲረጋገጥ፣ የሀገሪቱ የፖለቲካ አስተዳደር ልዩነትን በአግባቡ ማስተናገድ የሚችል መሆነ አለበት።
***********
* ጸሐፊው ስዩም ተሾመ በአምቦ ዩኒቨርሲቲ ወሊሶ ካምፓስ መምህር ሲሆኑ፤ በ seyee123@gmail.com ኢሜይል አድራሻ ሊያገኟቸው ወይም ሌሎች ጽሑፎቻቸውን http://ethiothinkthank.com ላይ ሊያነቡ ይችላሉ፡፡
ከብሔራዊ ባይቶ ኣባይ ትግራይ (ባይቶና) አመራር ኪዳነ አመነ ጋር የተደረገ ቃለ-ምልልስ ክፍል 2 - ለውጥ…
ከብሔራዊ ባይቶ ኣባይ ትግራይ (ባይቶና) አመራር ኪዳነ አመነ ጋር የተደረገ ቃለ-ምልልስ ክፍል 1 - ለትግራይ…
የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ትብብር (ትዴት) አመራር መኮንን ዘለለው ከሆርን አፌይርስ ጋር ያደረጉት ቃለመጠይቅ (ክፍል 2)- ስለትዴት…
የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ትብብር (ትዴት) አመራር መኮንን ዘለለው ከሆርን አፌይርስ ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ (ክፍል 1) -…
(የማነ ካሣ) እንደሚታወቀው አቶ በረከት ስምዖን እና አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) ከጥረት ኮርፖሬሽን ጋር በተያያዘ…
(መርስዔ ኪዳን - ሚኔሶታ) ኣብራክ የተባለውን የሙሉጌታ ኣረጋዊ መጽሓፍ ኣነበብኩት። ኣገራችን ከሊቅ አስከደቂቅ በዘውጌ ብሄርተኝነት…