የህወሓት መግለጫ ጭማቂ – 8  ነጥቦች

የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ በመስከረም የመጨረሻ ሳምንት የጀመረውን ግምገማ ትላንት ጨርሷል። በተለይ ባለፉት አራት ሳምንታት የነበሩት ተከታታይ የሂስና ግለሂስ መድረኮች የድርጅቱን ሊቀመንበርና የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን በመቀየር እንደተጠናቀቀ HornAffairs – English በተከታታይ ሲዘግብ ቆይቷል።

የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽ/ቤት የግምገማውንና የአመራር ሽግሽጉን መጠናቀቅ አስመለክቶ ዛሬ የአቋም መግለጫ አውጥቷል።

1) የአቋም መግለጫው የድርጅቱን ቁመና እንዲህ ሄሶታል:-

“ካለፉት ጥቂት ኣመታት ወዲህ ስትራቴጂካዊ ኣመራሩ እየተዳከመ ተልእኮውን ለመወጣት የሚያስችል ቁመና፣ ኣመለካከትና ኣደረጃጀቱ በየጊዜው እየተሸረሸረ፣ ህዝባዊነቱ እየቀነሰ፣ የህዝብን ችግር በማያወላዳ መልኩ ሳይፈታ በትንንሽ ድሎች የሚረካ ሆኖ በመገኘቱ ምክንያት የመፍትሔ አካል ከመሆን ይልቅ የችግር ምንጭ መሆን የጀመረበት ሁኔታ በስፋት መታየት ከጀመረ ውሎ አድሯል፡፡”

2) የግምገማውን አካሄድ አስመልክቶም እንዲህ ብሏል:-

“ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ስደረጉ ከነበሩት የይስሙላ ግምገማዎች በዓይነቱና መልኩ በተለየ ችግሮቹን በሚገባ ለመለየት ያስቻሉት መተጋገል አካሂዷል፡፡”

“ወደ ግምገማ ሲገባ አሁን በስራ ላይ ያለውና ተተኪው አመራር በጋራ ትኩረት ሰጥቶ ያየው ጉዳይ ከገባበት የአመራር አዙሪት ውስጥ ለመውጣት በተለመደው መንገድ መሄድ በፍፁም የማይዋጣ መሆኑን በመገንዘብ ከተለመደው ግምገማ ለመውጣት ያስችላል ተብሎ የታመነበትና ስፋትና ጥልቀት ያለው ክርክር የጋበዘ የድርጅቱን ኣጠቃላይ ሁኔታና የኣመራሩን ድክመት በሚገባ የፈተሻ ሰነድ ለኣመራሩ ቀርቦ ሰፊ ውይይትና ክርክር ተደርጎበታል፡፡”

Photo -  Fetlework Gebregziabher and Debretsion Gebremichael, TPLF chairpersons
Photo – Fetlework Gebregziabher and Debretsion Gebremichael, TPLF chairpersons

3) በግምገማው የአመራሩን ዝንባሌ እንዴት እንደታየ መግለጫው ሲያትት:-
“አመራሩ የሃሳብና የተግባር አንድነት የጎደለው፣ ፀረ ዴሞክራቴክ ተግባርና አስተሳሰብ ውስጥ በስፋት የተነከረ፣ በተልዕኮ ዙርያ በመተጋገልና በመርህ ላይ የተመሰረተ አመራር የማይሰጥ፣ ህዝብንና አላማን ከማስቀደም ይልቅ የራሱን ክብርንና ጥቅም የሚያስቀድም መሆኑ ታይቷል፡፡ ለህዝብ ያለው ወገንተኝነት እየተሸረሸረ፣ ከኣገልጋይነት ይልቅ ራሱን እንደ ተገልጋይ እየቆጠረ፤ መዋቅራዊ ለውጥ በሚያመጡ ስኬታማ የህዝብ ዙርያ መለስ እንቅስቃሴ ከመጠመድ ይልቅ በተደማሪ ለውጦች የሚረካና በውሸት ሪፖርት ራሱን መሸለም የሚቃጣው አመራር እየሆነ በአጠቃላይ ራሱን ወደ ጥገኛ ገዢ መደብ የመሸጋገር አዝማሚያ የተጠናወተው መሆኑን በትክክል አስፈቀምጧል።”

“ሁሉንም የልማት ሃይሎች በተደራጀ መልኩ በመምራት ረገድ የነበረውን ሰፊ ክፍተትንም ኣይቷል፡፡ ወጣቶች ፣ ምሁራን፣ ሴቶችና ሌሎችም የሞያ የማሕበራትና መሰል ኣደረጃጀቶች የለውጥ ባለቤት ሆነው የሚውጡበትን ዕድል በማምከን ድርጅቱን በቀጣይነት የሚመራ ብቁ ሃይል እንዳይፈጠር እንቅፋት የሆነ ኣመራር መሆኑንም በሚገባ ተረድቷል፡፡ ህዝቡ በድርጅቱ ላይ የነበረዉን እምነት እንዲሸረሸርም ትልቅ አስተዋፅኦ ኣድርጓል፡፡”

4) የሂስና ግለ-ሂስ መድረኩን አካሄድን አስመልክቶም:-

“ለተፈጠረው ችግር ማእከላዊ ኮሚቴው በኣጠቃላይ ተጠያቂ ቢሆንም የችግሩ የከፋ መገለጫ የህወሓት ስራ ኣስፈፃሚ ኮሚቴ እንደ ኣካልም ሆነ እንደ ግለሰብ ኣመራሩ መሆኑን በመውሰድ ጥልቅ የሂስና ግለ ሂስ መድረክ ኣካናውኗል፡፡ የሂስና ግለሂስ መድረኩ አላማ በግለሰብ ኣመራር አባላት ላይ ያተኮረ ሳይሆን ድርጅቱ ካለዉ ስትራተጂካዊ ፖለቲካዊ ተልእኮ አንፃር እያንዳንዱ አመራር ሃላፊነቱን የተወጣበትን ደረጃ እና ልክ በትክክል ለመገንዘብ እና አስፈላጊዉን የእርምት እርምጃ ለመዉሰድ ያለመ ነበር፡፡ ሂደቱም በግልፅነት ፣ በሙሉ ተሳትፎና በቁጭት መንፈስ የተከናወነ ሲሆን በመጨረሻም መላዉ አመራር ዘንድ በተደረሰበት ድምዳሜ ዙርያ የጋራ መግባባት የተያዘበት ሁኔታ ተፈጥራል፡፡”

“ማእከላይ ኮሚቴዉ የሂስና ግለሂስ ሂደቱን ካከናወነ በኃላ በድርጅቱ ስትራቴጂክ አመራር ዘንድ በስፋት ይስተዋል የነበረዉን የሃሳብና የተግባር አንድነት ችግር ስር ነቀል በሆነ መልኩ ለመፍታት የሚያስችል መግባባት ላይ የተደረሰበት የአመራር ሽግሽግ በማድረግ የተሃድሶው ስትራቴጂክ አመራር ተጠናክሮ የወጣበት የተመቻቸ ሁኔታ ፈጥሯል።”

5) የድርጅቱ አባላት፣ አርሶ አደሮችና የከተማ ነዋሪዎች ባስተላለፈው መልዕክት ላይ እንዲህ ብሏል።

“ባለፉት ዓመታት ጥያቄዎችህን በመፍታት ረገድ የህወሓት አመራር ከፍተኛ ድክመት አሳይቶም ጭምር በትዕግስት እና በተስፋ መጠበቃችሁ ድርጅቱ ይገነዘባል፡፡ ማእከላይ ኮሚቴው ችግሩን በሚገባ ተረድቶ የናንተን ጥያቄዎችንና ፍላጎቶች ለመፍታት፣ በህዝብ ዘንድ በብዙ መልኩ ተሸርሽሮ የነበረውን አመኔታ ለማሳደስ የሚተጋ፣ በሃገር ኣቀፍ ደረጃ ሊኖረን የሚገባውን ገንቢ ሚና ለማስቀጠል ዝግጅነቱ፣ ተኣማኒነቱና ፅናቱ ያለው፤ ስኬቶቻችንን ለማስቀጠል የቆረጠና ቀጣዩን ጉባኤ ኣሳታፊ በሆነ መልኩ ለማከናወን የሚያስችል ስራዎችን የሚሰራ ኣመራር እንደሚሆን ኣንጠራጠርም፡፡”

“የጉባኤ ዝግጅታችን መላው አባላችን፣ ምሁራን፣ ወጣቶች ፣ ሴቶችና ቡዙሃን ማሕበራትን በነፃነት ባሳተፈ መልኩ እንዲካሄድና በተመረጡ የህዝብ አጀንዳዎች ላይ አተኩሮ ለማካሄድ የሚያስችል ዙርያ ምላሽ ዝግጅት የሚደረግ ይሆናል።”
 
6) የክልሉ ምሁራንና ልማታዊ ባለሃብቶች በሰጠው ተስፋም እንዲህ ይላል:-
 
“የህወሓት/ኢህአዴግ አመራር በሚፈለገው ደረጃ የተመቻቸ ሁኔታ ባለመፈጠሩ ምክንያት በክልላችሁና በሃገራችሁ ጉዳይ ላይ በሚገባው ደረጃ ያላሳተፍናችሁ መሆኑን ተገንዝቧል። በመሆኑም ጥያቄያችሁን ለመመለስ የራሳችሁን የተሟላ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ህወሓት/ኢህአዴግ ምሁሩና ባለሃብቱ በመሰላችሁ አደረጃጀት ውስጥ ሁናችሁ ተዋናይ የምትሆንበት ተቋማዊ መሰረት በማስቀመጥ ከልቡ የሚሰራ ይሆናል፡፡ በጥናትና ምርምርም ሆነ በልማት የክልላችንም ሆነ የሃገራችን ልማትና ዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ባለቤት የምትሆኑበት ሁኔታ ይመቻቻል።”
 
7) የኢህአዴግ እህትና አጋር ድርጅቶች ባስተላለፈው መልዕክት:-
 
“በልማትና በመልካም አስተዳደር ዙርያ ህዝባችን ለከፍተኛ ምሬት የዳረጉ ዘርፈ ብዙ ችግሮች በኣመራሩ ድክመት የተፈጠሩ መሆናቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ድርጅታችን ህወሓት/ኢህአዴግ በአገር ደረጃ በሚደረጉ የፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎቻችን በማሳካት ረገድ ሲጫወት በመጣው ሚና ላይ ኣሉታዊ ተፅእኖ መፍጠሩንም በሚገነባ ይገነዘባል፡፡ የኣመራር ድክመት በህወሓት ውስጥም ሆነ በክልላችን በሚደረጉ የልማትና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ጥረቶች ላይ ጉዳት ከማድረሱ በተጨማሪ በእህትና በአጋር ድርጅቶች መካከል ለበርካታ ኣስርት ኣመታት የነበረውን በመርህ እና በትግል ላይ የተመሰረተ ውህደት፣ ለዙርያ መለሽ ስኬት ያበቃን የአመለካከትና የተግባር ኣንድነት በየጊዜው እየተሸረሸረ እንዲመጣና በጋራ ዓለማ ዙርያ በአንድ ልብና መንፈስ ከመንቀሳቀስ ይልቅ በንትርክና በጥርጣሬ መተያየት ያጠላበት እንዲሆን በማድረግ በኩል የራሱን ኣሉታዊ ኣስተዋፅኦ እንደደረገ በትክክል ኣስቀምጣል፡፡”
 
“ሁሉንም አቅሞቻችን፣ የህዝባችንን ፍትሓዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚያስችሉ የጠሩ ፖሊሲዎቻችን ሲኬታማ ኣፈፃፀም ላይ ከማድረግ ይልቅ የፌዴራል ስርዓት ጠላቶች ባጠመዱልን ወጥመድ ውስጥ ገብተን የሃገራችንን ኢትዮጵያ ህልውና ፈተና ላይ እንዲወድቅ በማድረግ ረገድ በህወሓት ኣመራር ዘንድ የታየው ድክመት የማይናቅ ሚና እንደነበረው በግልፅ ይረዳል፡፡ የፈዴራል ስርዓቱን ለመናድ ከውስጥም ከውጭም የተሰባሰቡ ጥገኛ ሃይሎችን በጋራ የመመከት ኣቅማችን እየተመናመነ በተመሳሳይ ፕሮግራምና ልማታዊ መስመር ዙርያ የተሰለፉ ሃይሎች የጋራ ትግላቸዉ መደነቃቀፍ የጀመረበት ሁኔታ ተፈጥራል፡፡ በኢህኣዴግ ኣባል ድርጅቶች ውስጥ ለሚታዩ ችግሮች ዋነኛው ተጠያቂነት ለየድርጅቱ ኣመራር የሚተው ቢሆንም በህወሓት ኣመራር ውስጥ ይታዩ የነበሩ ኣዝማሚያዎች ለብዙ ኣስርተ ዓመታት በእሳት ጭምር ተፈትኖ የመጣውንና ለሃገራችን ኢትዮጵያ ልማትና ዴሞክራሲ እውን መሆን ምክንያት የሆነው አብዬታዊና ዲሞክራሲያዊ አንድነት በመሸርሸር ረገድ የማይናቅ ድርሻ እንዳነበረው ማእከላዊ ኮሚቴው ባደረገው ግምግማ ኣረጋግጧል፡፡” 
 
“ህወሓት ከእህት እና አጋር ድርጅቶች ያለውን ግንኙነት በመርህና በመተጋገል ላይ በመመስረት የሚታደስበት የነበሩ የርስ በርስ መጠራጠሮች ለመፍታት የሚያስችሉ ኣቅጣጫዎችን የሚከተል ይሆናል፡፡”
 
8) ለኢትዮጵያ አርሶ አደሮች፣ ላብአደሮች፣ ልማታዊ ባለሃብቶች ባቀረበው ጥሪ የሚከተለውን ብሏል።
 
“ህወሓትና የትግራይ ህዘብ ከሌሎች እህትና ኣጋር ድርጅቶች እንዲሁም ከመላው የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር በመሆን ለእኩልነትና ለፍትሓዊ ተጠቃሚነት የከፈሉት እጅግ ከፍተኛ መስዋዕትነት ሳይበቃውና ተከታታይ ገዢዎች ያሲረፉበት ቁስል በወጉ ሳያገግም ለሌላ የተቀናጀ ጥቃት የሚጋለጥበት ሁኔታ ከመፍጠር ኣንፃር የህወሓት ኣመራር ውስጥ የታየው ድክመት የማይናቅ ኣስተዋፅኦ ኣድርጓል፡፡”
 
“አሁንም ቢሆን ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓታችን ያመጣቸዉን ትሩፋቶች ጠብቆ የተሻለ ብልፅግና የሰፈነባት እና ህዳሴዋ የተረጋገጠ ኢትዮጵያን እዉን ለማድረግ በሚደረገዉ እንቅስቃሴ ዉስጥ ድርሻዉን ኣጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ ከዉጭም ከዉስጥም የሚቃጡብንን አፍራሽ ጥቃቶች ለመመከት ከመላዉ የሃገራችን ህዝቦች ጋር በቅርበት ይሰራል፡፡ በአሁኑ ሰአት በየአካባቢዉ እየተከሰቱ ያሉ ግጭቶች በሰላማዊ መንገድ የሚፈቱበትና የህዝቦች የዴሞክራሲና የመልካም አስተዳደር እንዲሁም የልማት ጥያቄ በተገቢዉ መንገድ ለመመለስ በሚደረገዉ ርብርብ ዉስጥ ድርሻዉን ለማበርከት ዝግጅነቱን ይገልፃል፡፡ ህወሓት/ኢህኣዴግ የጋራ ሃገራችንን በሆነችው ፌዴራላዊት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ለልማትና የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ላይ የተጫወተውን ገንቢ ሚና ኣጠናክሮ ለመወጣት የሚያስችለውን ኣቅጣጫዎች ከህዝቦች ጋር በመመካከር የሚያከናውን ይሆናል፡፡ ዲሞክራሲያዊ አንድነታችሁን አጠናክራችሁ አፍራሽ አጀንዳዎቻችውን ለማሳካት ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨት የሚዳክሩ ጠላቶችን በጋራ እንድንመክት ጥሪውን ያቀርባል።” 

**********

የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ መግለጫን ሙሉ ይዘት ለማግኘት ይህን ሊንክ ይጫኑ

Daniel Berhane

more recommended stories