ስለታሪካችን ለምን የተቀራረበ አረዳድ አልኖረንም?

(የሺሃሳብ አበራ – የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት)

ታሪክን እንደ የግለሰቦች ግንዛቤ እና አረዳድ መተርጎም ሳይንሱ የሚከተለው ባህሪ ቢሆንም የሚኖረን አተያይ ብዙ መራራቁ ግን ተገቢነት የለውም ይላሉ የታሪክ ተመራማሪው ዶክተር አሰፋ ባልቻ፡፡

ታሪካችን የጋራ ሀገር ለመገንባት መሰረት ቢሆንም፤ የአውሮፓውያን የመከፋፈል ስልት የጋራ ታሪካችንን በመንደር እንድንከልለው አድርጎን ቆይቷል፡፡ ይህ ደግሞ ለሀገር የጋራ እድገት አደጋ ነው፡፡

ኢትዮጵያ የሚለው ጥንታዊ ስያሜያችን ደብዝዞ አቢሲኒያ ተብሎ ሰሜኑ የሃገራችን ክፍል እንደገዥ መደብ ተደርጎ እንዲቆጠር በነጮች ተቀናብሮ ቀርቧል፡፡

ይህ ደግሞ የጨቋኝ እና የተጨቋኝነት ስሜት እንዲዳብር አድርጓል ይላሉ በአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ ጉዳዮች የታሪክ ተመራማሪ የሆኑት ፕሮፌሰር ሹመት ሲሻኝ፡፡

እንደ ፕሮፊሰሩ በሀገር ምስረታ ታሪክ ውስጥ ግጭት መፈጠሩ የግድ ነው፡፡ ነገር ግን ግጭቱ ለብሄራዊ ሀገር ግንባታ በመሆኑ ዛሬ ላይ የተፈጠሩ መጥፎ የታሪክ አጋጣሚዎችን ሁሉ ለወቅታዊ ፖለቲካ ፍጆታ መቸብቸብ ዋጋ የለውም ይላሉ፡፡

የገዥ እና የተገዥነት የታሪክ ትርክት በአውሮፓውያን ሴራ የተጠነሰሰ ሀገር የማላላት ስትራቴጂ ነው ይላሉ ፕሮፊሰሩ፡፡

ታሪክ በሙያተኛ መፃፍ ይገባዋል፡፡ የታሪክ ባለሙያዎች ማህበር መስርተን የኢትዮጵያን የ 3 ሺ ዓመት ታሪክ ለማጥናት ብሎም ለማቃናት ጥረት ላይ ነን ያሉት ደግሞ በባህዳር ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ተመራማሪው ዶክተር ጥጋቤ በዜ ናቸው፡፡

ዶክተር ጥጋቤ የታሪክ ትምህርት ትኩረት መነፈጉ ታሪክ በመሰለኝ እንዲፃፍና ከዕውነታው አፈንግጦ ወቅቱን እንዲመስል ተደርጓል፡፡ ስለዚህ ታሪክን በታሪክነቱ ብቻ መተርጎም ወሳኝ ነው ይላሉ፡፡

ፕሮፊሰር ሹመት ሲሻኝ የውጭ ሀገር የታሪክ ተሞክሯቸውን ያነሳሉ፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ የትኛውም ሀገር የራሱን ታሪክ እንደ ጋራ ትምህርት (ኮመን ኮርስ) ይሰጣል፡፡ በየአካባቢው የታሪክ መዛግብት አሉ፡፡

ያለታሪክ ሀገር ዓይን የላትም፡፡ በመሆኑም ሀገሪቱ ታሪኳን ልትንከባከበው፣ልታሳድገውና ትውልዶችን ለማቆራኘት ልትጠቀምበት ይገባል ይላሉ፡፡

የኢትዮጵያን የታሪክ ጉዞ የሚገመገም የምሁራን ጉባዔ በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ይገኛል ፡፡

*********

ምንጭ፡- የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት፣ ሰኔ 09/2009

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories