በቀውስ የሚታመሰው የአፍሪካ ቀንድ እና የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ

(ዮሐንስ ገበየሁ)

የአፍሪካ ቀንድ ከሀብታሞቹ የነዳጅ ባለቤቶች የባህረ ሰላጤው አገሮች ጋር በቀይ ባህርና በባቤል መንደብ ወሽመጥ አማካይነት ይገናኛል፡፡ ሀብታሞቹ የባህረ ሰላጤው አገሮች ከምዕራቡ ዓለም ኢኮኖሚ ጋር በሆርሙዝና ባቤል መንደብ ወሽመጦች የሚያገናኝ ነው፡፡ የኤደን ሰላጤና ቀይ ባህር በተባሉ ስትራቴጂካዊ ቦታዎች በየዓመቱ 700 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር የንግድ ልውውጥ የሚደረግበት ከመሆኑም በላይ ሜድትራኒያን ባህር፣ የስዊዝ ቦይና ቀይ ባህርን ከህንድ ውቅያኖስና ምዕራባዊያን ገበያዎችን ከእስያና ከመካከለኛው ምሥራቅ ገበያ ጋር በማገናኘት ትልቅ የንግድ መተላለፊያ ሆኖ ያገለግላል።

ረጅም የሆነ ማለትም 2,500 ማይል የባህር ዳርቻ ያለው በመሆኑ ምክንያት፣ አሸባሪ ቡድኖችና የባህር ላይ ወንበዴዎች እንደፈለጉት እንዲንቀሳቀሱና እንዲፈነጩ የሚፈቅድ አመቺነት አለው። የአሸባሪዎችና የባህር ላይ ወንበዴዎች ያለማንም ሃይ ባይ የአሜሪካንና የምዕራባዊያንን ጥቅም በመፃረር በአካባቢው መንቀሳቀስ፣ ለዓለም አቀፋዊ የፀረ ሽብር ጦርነት ምክንያት በመሆን ኃያላኑ በአካባቢው ጣልቃ እንዲገቡ በር ከፍቷል። ቀጣናው የዓባይ ምንጭ ነው። እስያን፣ አውሮፓንና መካከለኛው ምሥራቅን ከማገናኘቱ በተጨማሪ፣ ዓረቦች ወደ ተቀረው አፍሪካና ዓለም ለመግባት ዋና በራቸው በመሆን የሚያገለግል ነው።

ከላይ በተጠቀሱት መልካምድራዊ፣ ጆኦ-ፖለቲካዊ፣ ስትራቴጂካዊ ምክንያቶች ከፍተኛ የሆነ የፖለቲካ፣ ዲፕሎማሲ እና የጸጥታ ተለዋዋጭነት ያለው፣ የሃያላኑ ጣልቃ ገብነት የሚስታዋልበት፣ ተደጋጋሚ ድርቅ የሚያጠቃው፣ ሽብርተኝነት እና የባህር ላይ ውንብድና የተስፋፋበት፣ ብዝሃነት መለየው የሆነ፣ አያሌ ቁጥር ያለው ስደተኛ እና ተፈናቃዮች የሚወጡበትና የሚገቡበት፣ የእርስ በእርስ ጦርነት በማያቋርጥ ሁኔታ ለዘመናት ሲዘንብበት የኖረ የአለማችን ክፍል ነው።

አገራችን ኢትዮጵያ በዚሁ ያልተረጋጋ አካባቢ የምትኖር ነገር ግን የሰላም እና መረጋጋት ደሴት ተብላ በቀጠናው ተንታኞች የምትታወቅ አገር ናት። ኢትዮጵያ በእርግጥ ቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ የአፍሪካ አገር፣ የጥቁር ህዝቦች ምልክትና ኩራት፣ የኩሩ ህዝብ እናት፣ የሰው ልጅ መገኛ ናት። አገራችን ምድረ-ቀደምት ብትሆንም በምን ጥንካሬ፣ በምንስ ታምርና ጥበብ ለዘመናት እራሷን አስጠብቃ የሰላምና መረጋጋት ደሴት ልትሆን በቃች የሚለው ጥያቄ የብዙ ተመራማሪዎች ጥያቄ ሆኖ የሚቀጥል ቢሆንም በዚህ ጽሁፍ የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ ለነጻነቷ መጠበቅ ያበረከተውን ሚና እና በአፍሪካ ቀንድ ቀጠናዊ ቀውስ ውስጥ ብሔራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ የሚያደርገውን ጥረት ለመተንተን ይሞከራል።

ኤድሞንድ ኬለር ‘‘The Politics of State Survival: Change and continuity of Ethiopian Foreign Policy’’ በሚል ባቀረበው ጽሁፍ የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ የአገሪቱን ህልውና ለማስጠበቅ ትልቁ መሳሪያና ጥበብ መሆኑን ይጠቁማል። ሌሎች በመስኩ ጥናት ያደረጉ ተመራማሪዎችም ይህንኑ ይጋራሉ። እንደ ብዙዎቹ ምልከታ ከሆነ የኢትዮጵያ መሪዎች እና ህዝቦች ለዘመናት ጠብቀውት የቆየ ማንነት ያላቸው በመሆኑ ካልደረሱባቸው የማይደርሱ ከደረሱባቸው ግን አፈርድሜ ሳያበሉ የማይለቁ መሆኑን የተለያዩ የታሪክ መዛግብትን በማጣቀስ ያስረዳሉ።

ኢትዮጵያ በተለይም በ19ኛ ክፍለ ዘመን መጨረሻ እና በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ከቅርብና ከሩቅ የተቃጡባትን ወረራዎች በመመከት War is diplomacy by another means እንዲሉ የዲፕሎማሲ ጠበብት፤ ዲፕሎመሲው አልሰራ ሲል መሳሪያ በመምዘዝ ነጻነቷን ጠብቃ የቆየች አገር ናት። ለመጀመሪያ ጊዜ የነጭ የበላይነትን ቅስም ሰብሮ የኢትዮጵያን ሏላዊነት ያስጠበቀው እንዲሁም በዘመኑ በቅኝ ግዛት ስር ሲማቅቁ ለነበሩ የዓለም ህዝቦች የነጻነት ተምሳሌት የሆነው የአድዋ ድል፣ ጦርነት ዲፕሎማሲን በሌላ መንገድ ማስኬጃ መሆኑን ያረጋገጠ፣ አገራችን የታፈረች እና ክብሯን ጠብቃ የኖረች አገር እንድትሆን ካበቁ ክስተቶች ዋነኛው ነው።

ከዚህ ክስተት ወዲህ የአገርን ልዋላዊነት የሚፈትኑ ቀጠናዊና አለም አቀፋዊ ክስተቶች የተከሰቱ ቢሆንም አገራችን ኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅሟን ለማስጠበቅ በሳል የዲፕሎማሲ ክንውኖችን ስታደርግ ኖራለች። ይህ በሳል የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴ አገሪቷ በቀውስ ውስጥ ባለ ቀጠና ውስጥ የመረጋጋትና የሰላም ደሴት እንድትሰኝ አድርጓታል። የአገራችን ዲፕሎማሲ በመልካም ጉርብትና፣ ሰጥቶ መቀበል፣ በጋራ ተጠቃሚነት፣ በሌሎች አገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ባለመግባት፣ የጋራ ደህንነት እና ሌሎች የአለም አቀፍ ግንኙነት ወርቃማ መርሆች እየተመራ ነው አገራችን ውጥንቅጡ በወጣ ቀጠና ውስጥ የሰለም ደሴት ለመሆን ያበቃት።

የኢትዮጵያ አለም አቀፍ ግንኙነት መሰሶዎች ተብለው የሚታወቁት ዴሞክራሲን ማስፈንና መገንባት፣ ልማትን በፍታዊነት እና ዘላቂነት ማረጋገጥ እና መልካም አስተዳደርን እውን ማድረግ ከአገሪቱ ውስጣዊ እና ውጫዊ ከባቢ ጋር የተገናዘቡ ናቸው። ሲጀምር ማንኛውም ተጋላጭነት ከውስጥ እንደሚመነጭ ይህንን ተጋላጭነት ከምንጩ ለማድረቅ ደግሞ ከላይ የተጠቀሱትን ግቦች አልሞ መስራት እንደሚያስፈልግ ብቻ ሳይሆን የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ከጎረቤት አገራት የጋራ ተጠቃሚነት ጋር በሚናበብ መልኩ የውስጥን ሁኔታ ከውጫዊ ሁኔታዎች በተለይም ከጎረቤት አገራት ሁኔታ ጋር በማሰናሰል መከወን እንደሚያስፈልግ ውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችን ያትታል፣ ዲፕሎማሲያችን ደግሞ በዚሁ መሰረት ይተገብራል፣ ይንቀሳቀሳል፣ ያስፈጽማል።

ልማትና ዴሞክራሲዊ ግንባታን እውን ማድረግ ማዕከሉ ያደረገ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችን አገራችን ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን ጎረቤቶቿን ጭምር የሚጠቅም እና የቀጠናውን ሁኔታ መቀየር በሚችል መልኩ መቃኘት እንዳለበት ተቀምጧል። በሌላ አገላለጽ፣ ኢትዮጵያ ቀጠናውን አስመልክቶ የምታራምደው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በጋራ ልማት፣ ተጠቃሚነት እና ትብብር ላይ የተመሰረተ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል። ልማትን፣ ዴሞክራሲን እና መልካም አስተዳደርን እውን ማድረግ ከቀጠናው እና አለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታ ተለይቶ መታየት የሌለበት ጉዳይ መሆኑን በግልጽ አስምጧል የውጭ ጉዳይ ፖሊሲው።

ይህ በግልጽ የሚያሳየን የአገሪቱ ውጭ ጉዳይ ፖሊሲና ዲፕሎማሲ ብልህ የሆነ አገራዊ፣ ቀጠናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ኑባሬዎችን ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆኑን ነው። ዓለም አቀፉ የኃይል አሰላለፍ ምን ያህል ተጽኖ ሊኖረው እንደሚችል በመገንዘብ Brian Schmidt (2008: 16) የተባለ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ተንታኝ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኒዎ-ክላሲካል ሪያሊስቶች ቅኝት የሚመራ መሆኑን እንዲህ ሲል ያስቀምጣል ‘‘neo-classical realists argue that domestic factors are needed to explain how systemic factors are translated into foreign policy decisions.’’ ዲፕሎማሲያችን ከላይ የተጠቀሰውን አስተምሮ ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆኑን የዲፕሎማሲ ታሪካችን ዳሰሳ ያመለክታል። በአጭሩ ለማስቀመጥ የኢትዮጵያ ቀጠናዊ ዲፕሎማሲ የውስጥ አቅምን እና ቀጠናዊና አለም አቀፋዊ የኃይል አሰላለፍና ስርጭትን ከግምት ውስጥ ያስገባ ነው።

የአፍሪካ ቀንድ ከመጥበሻው ወደ ሳቱ የሚባል ሁኔታ ላይ ነው የሚገኘው። ያልተሳካ (failed) ሶማሊያ፣ በእርስ በርስ ጦርነት ምክንያት በመፍረስ ላይ ያለ ደቡብ ሱዳን፣ ዳርደንበሯን ማስከበር የተሳናት (Porous) ኬንያ፣ አክራሪ እስላማዊ ሱዳን የቀጠናው መገለጫዎች ናቸው። ይህ የአገራቱ ሁኔታ ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ላላቸው እንደ አልሻባብ ላሉ አሸባሪ ቡድኖች ለም መሬት በመሆን ቀጠናው የአሸባሪዎች መፈልፈያ እንዲሆን እረድቷል።

ኃያላኑ የከተሙባት ጅቡቲ እና በትቢት የሚወጠረው የኤርትራ አገዛዝ የቀጠናው ሌላ ድባብ ናቸው። ያልተሳኩ አገራት፣ የወደቁ አገራት፣ ድርቅና ርሃብ፣ የእርስ በርስ ጦርነት፣ በቀጠናው ያለ የውጭ ጣልቃ ገብነት፣ የቀጠናው ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እና የሽብርተኝነት አደጋ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲን እና የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴን ለመወሰን የሚረዱ ኑባሪዎች ናቸው።

ኢትዮጵያ በዚህ ውጥንቅጡ በወጣ ቀጠና ውስጥ የምትኖር አገር በመሆኗ ደህንነቷን ለማረጋገጥ (maximizing its security) ትሰራለች ይህ ደግሞ ተንታኞች defensive realism/neo-classical realism ብለው የሰየሙት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አቅጣጫ ነው። በርካታ አገራት ባልተረጋጋ የአለም ቀጠና ውስጥ ራሳቸውን በማጠናከር፣ የውስጥ አቅማቸው ከውጫዊ ሁኔታ ጋር እንዲጣጣም በማድረግ ለውጫዊ ሁኔታው ምላሽ የሚሰጡበት አኳኋን ነው።

አገራችን ኢትዮጵያ ከጎረቤቶቿ ጋር በመሰረተ-ልማት፣ በንግድ፣ በባህል፣ በቋንቋ፣ በተፈጥሮ ሃብት፣ በመልካ ምድር፣ በሃይማኖት የተሳሰረች መሆኗን በመገንዘብ ይህንኑ የትስስር ገመድ በመጠቀም ከቀጠናው አገራት ጋር ያላትን ግንኙነት በማዳበር ላይ ትገኛለች። ይህም በአገራት መካከል መተማመን እንዲሰፍን የሚረዳ የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴ ነው።

በዚህም መሰረት ኢትዮጵያንና ጅቡቲን የሚያገኛኝ የባቡር ሃዲድ ገንብታለች፣ ኢትዮጵያንና ሱዳንን ለማገናኘት የየብስ ትራስፖርት ስራ ጀምሯል፣ ኢትዮጵያንና ኬንያን የሚያገናኝ የየብስ ትራንፖርት በመገንባት ላይ ይገኛል። በርበራ-አዲስ አበባ ኮሪደርን እውን በማድረግ ሶማሊያ-ላንድን ከኢትዮጵያ ጋር ለማገናኘት እየተሰራ ነው። ከደቡብ ሱዳን ጋር የሚያገናኝ መንገድ ለመገንባት ሁለቱ አገራት ተስማምተዋል በተጨማሪም ጁባን ከአዲስ አበባ ጋር ለማገናኘት የሚያስችል ፕሮጀክት በኢጋድ አስተባባሪነት እየተዘጋጀ ነው።

ኢትዮጵያ ለጅቡቲ፣ ኬንያና ሱዳን ኤሌክትሪክ ትሸጣለች፣ ለጅቡቲ የመጠጥ ውኃ ታቀርባለች። ከጅቡቲና በቅርቡ ከሱዳን የወደብ አገልግሎት እና ከሱዳን ደግሞ የነዳጅ አቅርቦትን ትገዛለች። ይህ ምጣኔ ሃብታዊ ትስስር በየነ-ጥገኝነትን (interdependence) በማስፈን አንዱ ካላንዱ መኖር እንደማይቻል እና የጋራ ተጠቃሚነት ዋነኛው የዲፕሎማሲያችን መርህ መሆኑን በተግባር ማሳየት ችሏል።

ጎረቤት አገራትን በሰላምና ደህንነት፣ በንግድ እና ቴክኒካዊ ድጋፍ መስኮች አገራችን በመርዳት ላይ ትገኛለች። ኢትዮጵያ በሶማሊያ እና ሌሎች አጎራባች አገራት ጠንካራ መንግስት እንዲመሰረቱ ከፍተኛ የሆነ የቴክኒክ ድጋፍ፣ የምጣኔ ኃብት ትብብር እና ሌሎችን ድጋፎች ታደርጋለች። በኢትዮጵያ እና በጎረቤት አገራት መካከል ያለው የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማዳበር በተለይም የህዝብ ለህዝብ ትስስሩን በማጠንከር በጽኑ መሰረት የቆመ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን እውን ለማድረግ እንዲረዳ የጎረቤት አገራት ቀጣይ የአገር ተረካቢዎችን በትምህርት፣ ስልጠናና ሌሎች ድጋፎች አማካኝነት ወደ አገራችን መጥተው ትምህርት እና ስልጠና እንዲያገኙ፣ አገራችን ኢትዮጵያ እና ህዝቦቿ ከጎረቤት አገራት ህዞቦች ጋር የሚያስተሳስሯት ሰፊ የሆነ የባህል፣ የተፈጥሮ ኃብት፣ የቋንቋ እና የታሪክ ሰንሰለት እንዳለ ለማሳየት እና ለማስገንዘብ ጥረት እየተደረገ ነው።

በዚህም መሰረት እ.ኤ.አ. በ2015 ወደ 325 የሚሆኑ የሶማሊያ ተማሪዎች በተለያዩ የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ አስፈላጊው ትብብር ተደርጎላቸዋል። ከ2015 በፊትና በኋላም በተለያየ ቁጥር የሶማሊያ ተማሪዎች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ከፍተኛ ትምህርትን ተከታትለዋል። እ.ኤ.አ. በ2017 8,000 የሚሆኑ ኤርትራዊን የመጀመሪያ ደረጃ ትምርታቸውን፣ 2200 የሚሆኑ ህጻናት የቅድመ-መደበኛ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ። እ.ኤ.አ. እስከ 2016 ድረስ 1,500 የሚሆኑ የኤርትራ ስደተኞች በአገራችን የተለያዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ነጻ የትምህርት እድል ተጠቃሚ ሆነዋል። 3000 በላይ የሚሆኑ ደቡብ ሱዳናዊያን በኢትዮጵያ ነጻ የትምህርት እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን የተገኙ መረጃዎች ያስረዳሉ። ከ900 በላይ ጅቡቲያዊያን በኢትዮጵያ የተለያዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የነጻ የትምህርት እድል እየተከታተሉ መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል።

ከፍተኛ ቁጥር ያለው የጎረቤት አገር ስደተኞችን በመቀበል አገራችን አገራችሁ በማለት ስደተኞችን አቅፋ ደግፋ መኖሯ ሞልቷት ተርፏት ሳይሆን የረዥም ጊዜ ትብብር ሁልጊዜም በህዝብ ልብና እዕምሮ የሚገነባ መሆኑን ስለምታውቅ ነው። በዚህ ረገድ 811, 555 የሚሆኑ ስደተኞችን፤ የሶማሊያ (246859) ፣ ደቡብ ሱዳን (349086) ፣ ኤርትራ (167619) ፣ ሱዳን (40779) ፣ የመን (1616) እና የሌሎች የጎረቤት አገራት (5596) ስደተኞችን በማስተናገድ ላይ ናች።

ኢትዮጵያ ከጎረቤቶቿ ጋር ደንበርና ደንበር ተሻጋሪ ኃብቶችን ትጋራለች። የአባይ ውሃን ከሱዳን እና ግብጽ፣ ኦሞን ከኬንያ ጋር፣ ሸበሌና ጁባን ከሶማሊያ ጋር የምትጋራ ሲሆን ሁሉም ወንዞች ከኢትዮጵያ የሚመነጩ ናቸው። ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ኃብቶች የሚመነጩት ከኢትዮጵያ ስለሆነ ብቻየን ልጠቀም በማለት Doctrine of Territorial Sovereignty/Harmon Doctrineን በመምዘዝ ውኃን በብቸኝነት ልጠቀም አላለችም። ይልቁንስ የውሃው የጋራችን ነው የኢትዮጵያ ልማት የአልቦ ድምር ውጤት ሳይሆን ሌሎችን በተለይም ጎረቤት አገራትን በሚጠቅም መልኩ የጋራ ተጠቃሚነትን እውን በሚያደርግ መልኩ መሆን እንዳለበት በማመን በፍትሀዊ ተጠቃሚነት መርህ ዲፕሎማሲዋን እየመራች ትገኛለች።

አገራችን ኢትዮጵያ የጎረቤቶቿ ብሎም የዓለም የጋራ ጸጥታና ደህንነት የሚረጋገጠው በጋራለጋራ ስንሰራ ነው የሚል የማይናወጥ ዲፕሎማሲያዊ አቋም አላት። በዚህም ምክንያት የተመድ እና የአፍሪካ ህብረት መስራች አባል ነች፣ የመንግስታቱ ሊግ አባል፣ የተለያዩ ቀጠናዊና አለም አቀፋዊ ድርጅቶች አባል፣ በተለያዩ የሰላም ማስከበር ተልኮዎች በግንባር ቀደምትነት ትሰለፋለች። በተመድ እና በአፍሪካ ህብረት የሰላም አስከባሪ ተልኮዎች ከፍተኛ የሆነ መስዋትነትን ከፍላለች ለአለም ሰላም ኃላፊነቷን ተወጥታለች፣ በመወጣት ላይ ትገኛለች። በኮሪያ፣ ኮንጎ፣ ሩዋንዳ፣ ቡርንዲ፣ ላይቤሪያ፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን እና ሶማሊያ በተደረጉ ዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ተልኮዎችን በኃላፊነት መንረፈስ ፈጽማለች። በአሁኑ ሰዓት 8321 ሰላም አስከባሪ ወታደሮችን፣ ፖሊሶችን እና ወታደራዊ ባለሙያወችን ለአለም የጋራ ሰላም በማሰማራት ከዓለም በቀዳሚነት ትጠቀሳለች።

ለማጠቃለል ያክል አገራችን ኢትዮጵያ ይህንን ሁሉ እያደረገች ከምንም በላይ የውስጥ ሰላም፣ መረጋጋትና ጥንካሬ አንዲት አገር በውጭ የሚኖራትን የዲፕሎማሲ ተክለ-ሰውነት የሚወስን መሆኑን በመገንዘብ የሚደረጉ የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴዎች ይህንኑ ለማምጣት ያለሙ ናቸው። የውስጥ ሰላም፣ መረጋጋት እና ጥንካሬ ሊመጣ የሚችለው ዲሞክራሲ እና የዲሞክራሲ ስራዓት ሲገነባ እና ፍታዊና ቀጣይነት ያለው የምጣኔ ኃብት ልማት ሲሰፍን መሆኑ ግልጽ ነው። ልማትና ዴሞክራሲ የማንንም ብሄራዊ ጥቅም የማይጎዱ ይልቁንም የጋራ ተጠቃሚነት የሚያሰፍኑ መሆኑን በዲፕሎማሲ እና በተግባር ማሳየት በመቻሏ፣ በህዝቦች መካከል የጋራ መግባባትን በአንጻራዊነትም ቢሆን በመገንባቷ፣ አገሪቱ ያላትን ተነጻጻሪ ጥቅም (comparative advantage) ከግምት ውስጥ በማስገባት ኢንቨስተሮችን መሳብ በመቻሏ ይህም ለምጣኔ ሃብት ጡንቻ መጎልበት አስተዋጽኦ በማድረጉ፣ በተግባር የተፈተነ አገር ወዳድ የጦር ኃይልና ደህንነት ያላት አገር በመሆኗ፣ ጥብቅ ዲስፕሊን፣ ታታሪነትና የአገር ፍቅር ያለው ህዝብ ባለቤት በመሆኗ፣ በዲፕሎማሲ የካበተ ልምድ ካላቸው የቀጠናው አገራት አንዷ በመሆኑ ምክንያት ዲፕሎማሲያችን በቀጠናዊ ቀውስ ውስጥ የአገሪቱን ብሄራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በቅቷል።

********

Guest Author

more recommended stories