(ታጋይ ካሕሳይ ቃሉ)
በዚሁ ወር መጀመሪያ ሳምንት በትግራይ ኦንሊይን (Tigray online) ድረ-ገፅ ላይ በአቶ እውነቱ ዘለቀ የተባሉ ፀሃፊ “ያን ያህል ወጥ መርገጥ ምን የሚሉት ድፍረት ነው”[PDF] በሚል ርእስና ቀደም ብሎ በእንግሊዝኛ ቋንቋ “Gedu Andargachew; A fifth column on the loose” በሚል ርእስ በአቶ ብርሀነ ካሕሳይ ተፅፎ ለተዘረጋው ፅሁፍ መልስ ለመስጠት ታስቦ የወጣውን ፅሁፍ ተመለከትኩ፡፡ የፅሁፉ መነሻ የአቶ ብርሀነ ፅሁፍ ይሁን እንጂ አይጋ ፎረምና እሳቸው እየተጠቀሙበት ያለው የትግራይ ኦንላይን ድረ-ገፆች፣ የውራይና መፅሄት፣ በዋናነት ደግሞ የትግራይ ህዝብና መሪ ድርጅቱ ህወሓት ላይ ያነጣጠረ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ሆኖ ነው ያገኘሁት::
በዚህ ሳያበቃ በተመሳሳይ ስም ደግሞ ከሶስት ቀን በኋላ በአይጋ ፎረም ላይ የወጣና “የግለሰቦችን ስም በማጠልሸት የህብረተሰቡ መሰረታዊ ችግሮች መፍትሄ ያገኝ ይሁን”[PDF] በሚል ርእስ ሃምሌ ወር በአይጋ ፎረም ለወጣው “የፖለቲካ ኤልኒኖ በኢህአደግ” በሚል ርእስ በአቶ ሰላምወርቅ በሚባሉ ፀሃፊ የለወጣ ፅሁፍ ምላሽ ለመስጠት የወጣ ፅሁፍን አነበብኩ::
የአቶ እውነቱ ፅሁፍ ብዙ ነገር የነካካ ስለነበረ ምናልባት የተወሰነ ነገር ይገኝበት እንደሆነ በማሰብ የተጠቀሱት ፅሁፎች በሙሉ ወደ ኋላ በመሄድ እውነታውን መፈተሽ የተሻለ እንደሆነ በማመን ሁሉም ለማየት ሞከርኩ፤ የነበረኝን እውቀትና ያገኘሁዋቸው ነገሮች ግን የተገላቢጦሽ ሆኑብኝ እናም ለዘመናት እየተዋሸና መልስ ስለማይሰጥበት እውነት እየመሰለ እየሄደ በመሆኑ ይህቺን ለመፃፍ ወሰንኩኝ::
በመጀመሪያ ግን መነሻ በሆነው የአቶ ብርሃነ ካሕሳይና አቶ ሰላምወርቅ ፅሁፎች ያለኝ አቋም ልግለፅ:: በመጀመሪያና ከሁሉም በላይ የአቶ ብርሀነ ፅሁፍ ማለትም በይዘቱ ላይ ያለው የትግራይ ህዝብ እምነትና ፍላጎት ያልሆነውን እንደተጠበቀ ሆኖ ሊነግሩን የፈለጉት ለኛ የትግራይና የአማራ ህዝቦች ከሆነ ለምን በእንግሊዝኛ ቋንቋ መፃፍ አስፈለጋቸው? ወይስ አማርኛና ትግርኛ መፃፍ አይችሉም ካልቻሉ ደግሞ ተወልደው አድገዋል እንዴት ሊባል ይችላል? ስለሆነም በኔ እምነት ለጊዜውም ቢሆን መምሰል ይቻል ይሆናል መሆን ግን አይቻልም:: ሌላው የአቶ ብርሀነ ችግር በአማራ ክልል እየታዩ ያሉ ችግሮች አንድ ሁለት ብለው አስቀምጠዋል ትክክል ነው ይሁን እንጂ አብዛኞቹ ችግሮች በአገር ደረጃ የሚታዩና ለመፍታትም ጥረት እየተደረገ መሆኑ ሁላችን የሰማነው ነው:: ችግሩ ያለው በመፍትሄነት ያስቀመጡት ሃሳብ ላይ ልዩነት አለኝ:: ምክንያቱም የነዚህ ችግሮች መከሰት አቶ ገዱ ድርሻ ሊኖራቸው ካልሆነ እሳቸው ብቻ ናቸው ማለት አይቻልም::
ስለሆነም ችግሮቹ ከስረመሰረታቸው ለመፍታት የአቶ ገዱ ከስልጣን መውረድና ኣለመውረድ ብቻውን መፍትሄ አይሆንም ዋናው መፍትሄ ችግሮቹ የተያዙበት መንገድና የታያዘው አቅጣጫ ነው:: ኦህዴድ ስለወረዱ ብአዴንም መውረድ አለባቸው ከሆነ ትክክል አይደለም:: የየራሳቸው ነፃነት ያላቸው ድርጅቶች በመሆናቸው የሚወስዱት እርምጃም ሊለያይ ይችላል ዋናው ነገር ነገሮችን የሚይዙበት መንገድ በኢህአደግ ደረጃ በጋራ ያስቀመጡት አቅጣጫ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ነው::
ለኔ ትርጉም ያለው ጉዳይ ብአዴን ጉዳዩን የያዙበት መንገድ ችግሮቹን ከስረ መሰረቱ የሚፈታ መስሎ አልተሰማኝም ለዚህም ማሳያ የሚሆነኝ በሚከተሉት ነጥቦች ላይ ግልፅ አይደለሁም
1/ በቕማንት ህዝብ ማንነት ላይ በኢትዩጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የተሰጠው አቅጣጫና አቶ እውነቱም በፅሁፋቸው በሚገባ የገለፁት ችግር አፈታቱ ላይ ያለው ግልፅነት አሁን ደግሞ በተፈጠረው ግርግር የተዳፈነ መሆኑ
2/ ጎንደር ላይ የነበረው ሰልፍና የነበረው አላማ ፀረ ህገ-መንግስትና የአንድን ብሄር ማንነት የሚያንቋሽሽ ከመሆኑ በተጨማሪ መንግስት የለም የሚል መልእክት ያስተላለፈና ቀጥሎ የመጣው ብጥብጥና ውድመት የልብ-ልብ የሰጠ ሆኖ ሳለ ተጠያቂነት የሌለውና በሰላም የተጠናቀቀ እውቅና የሌለው ሰለፍ እየተባለ ሲወደስ መስማት በብአዴንና በክልሉ መንግስት ያለው አካሄድ በህገ-መንግስቱ ትግበራ ላይ ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑ
3/ የወልቃይት ጉዳይ በተመለከተ የወልቃይት ህዝብ ምን ይላል ለጊዜው እንተወውና ችግር ካለም እንዴት መፈታት እንዳለበትና ማንን እንደሚመለከት በግልፅ በህገ-መንግስቱ ሰፍሮ እያለ የወልቃይት አስመላሽ ኮሚቴ ተብሎ በጎንደር የተደራጀ ሃይል ቢሮ ከፍቶ የጎንደር ህዝብ እየቀሰቀሰ ሰልፍ (ህገወጥ ሰልፍ) እስከማድረግ ሲሄድ ብአዴንና የክልል መንግስት ምን ሲያደርጉ እንደነበረ ሳይመለስ አሁንም ይህ ጉዳይ የአማራ ክልል ጉዳይ ሳይሆን የትግራይ ክልል ጉዳይ ስለሆነ እጃችሁን አንሱ በሚል ተግባብተው ከሄዱ በኋላም በክልል አጀንዳ ሆኖ መቀጠሉ:: ከዛም አልፎ በተሃድሶ ስብሰባ የትግራይ ክልል ካልመለሰው እስከ ፈደራል እንወሰደዋለን የሚል ዛቻ አዘል ውይይት እየተካሄደ መሆኑ::
4/ በክልሉ በተፈጠረው ብጥብጥ የደረሰው ጉዳት ለሁሉም ደርሷል ያሳዝናልም:: ግን እኮ የክልሉ መንግስና መሪ ድርጅቱ ተጠያቂ ናቸው:: የሚያሳዝነው ግን የትግራይ ተወላጅ የሆኑ ሰዎችና ንብረታቸው እየታደነ ሲገደልና ሲቃጠል አልነበረም እንዴ? ከ8000 በላይ ትግርኛ ተናጋሪ አይደለም እንዴ የተፈናቀለው? ህዝብን በማገልገል ስራ የተሰማራው ሰላም ባስ አይደለም እንዴ የተቃጠለው? እና ይህ ህዝብ አገሬ ነው ወገኔ ነው ብሎ አይደለም እንዴ እዛ አከባቢ የሰፈረው? እና ለዚህ ይቅርታ አይጠየቅም እንደቀላል ነገር ይቅርታ ለመጠየቅ የሚያስችል ነገር አልሰራንም ተብሎ የታለፈው:: ዋናው ነገር የሞተውና የተባረረው ህዝብ ቁጥር ሳይሆነው የተገደለበትና የተባረረበት መንገድ ትግሬ ይውጣልን የሚል መፈክር ተይዞና ተቀስቅሶበት በመሆኑ እኮ ነው:: ብአዴንስ የወልቃይት የማይመለከተው አጀንዳ ከሚያደርግ የውስጥ ችግሩ በመፍታት ላይ ማተኮር አልነበረበትም? እዚህ ላይ ራሳቸው ተፈናቃዮቹ እንደገለፁት ወንድም የሆነው ሰፊው የአማራ ህዝብ የትግራይ ተወላጆች እንዳይጎዱ ያደረገው ትብብርና ኋላም ሽማግሌዎቹን ትግራይ ድረስ በመላክ ላሳየው ድጋፍ አሁንም በህዝቦች መሃል ያውን ትስስር እኛ ምንም ብናወራና ብንዘባርቅ ፍፁም የማይለያይ ስለመሆኑ የሚያስረግጥ እውነት መሆኑ እቀበላለሁ::
በአጠቃላይ እነዚህንና የመሳሰሉት የክልሉና የድርጅቱ ውስጣዊ ጉዳይ በማተኮር የነበሩት ፀረ ህገ-መንግስትና የጎራ መደበላለቅ ችግሮች በመፍታትና እስከጥግ ድረስ በመሄድ መለየት ለአማራ ህዝብ የዘላቂ ልማትና እድገት ዋስትና መስጠት ነበረበት ባይ ነኝ:: በመሆኑም አቶ ብርሃነ ያስቀመጡት የመፍትሄ ሃሳብ የታያቸው የመፍትሄ ሃሳብ ማስቀመጣቸው እንደ አቶ ተኮላ ባያስፈራኝምና እንደ አቶ እውነቱ ባያናድደኝም ቅድሚያ የሚመጣ ብቸኛ መፍትሄ ነው ብየ ግን አላምንበትም:: ምክንያቴ ደግሞ ላይ ለመግለፅ የሞከርኩትን ጉዳይ ሳይፈታ የሰዎች መቀያየር ብቻ ስለሚሆን የአቶ ገዱ መውረድና አቶ እውነቱ ወደ ስልጣን መምጣት ያው ስለሆነ:: እነዛ የጠቀስኩዋቸው ጉዳዮች እስካልተጣሩና ባለቤታቸው በሚለይና መበደላለቁን ሳይቀረፍ አቶ ገዱ የተገለፀው ሃጥያት በትክክል እጃቸው አለበት የለበትም ብሎ መከራከር ውሃ የሚቋጥር አይደለም:: በሌላ በኩል ደግሞ እነዚህን ጉዳዮች ተጣርተው ባለቤታቸው እስካልታወቀ ደግሞ የክልሉ ፕረዚዳንት በመሆናቸው ብቻ ተጠያቂነታቸው ከሌላው ባለስልጣን እንደሚጎላ ሳይታለም የተፈታ (Guilty until proven innocent) ነው::
እስቲ አሁን ደግሞ የአቶ እውነቱ ሃሳቦች እውነት ካላቸው እንያቸው:: እዚህ ላይ የአቶ ተኮላ እምነትም ከአቶ እውነቱ የተለየ እንዳልሆነ መታወቅ አለበት:: አቶ ተኮላ የአቶ ብርሀነ ፀሁፍ እንጂ ጎንደር ሽንፋእና መተማ የሞተው ሰው አያስፈራቸውም ምክንያታቸው ባለውቅም::
አቶ እውነቱ ዘለቀ (ሌላ ካልሆኑ) ባለፈው አመት “የኢህአደግ አመራር መሰረታዊ ስህተቶች” በሚል አርእስት የፃፉት አይቼ ነበር በወቅቱ ሳነበው በተደጋጋሚ መልስ የተሰጠበት ደርጎችና ኢህአፓዎች ግን ምንም ያህል መልስ ቢሰጣቸው ነገርን መላልሰው በመቆስቆስ እውነት ለማስመስል አልመውና እምቢ ብለው ስለሚሰሩ ጊዜ ማጥፋት ነበር አሁንም ለዚሁ ፅሁፋቸው መልስ የመስጠት ሃሳብ የለኝም ሆኖም ፅሁፉ ከጅምሩ የተሳሳተ መሆኑ ለማሳየት የኢህአደግ ጥንካሬ ብለው ከገለፁት “ኢህአደግ በሽግግር መንግስት ምስረታ ወቅት ከኢሰፓና ኢህአፓ ውጪ ሌሎች ፓርቲዎች ጋብዘዋል” ይሉናል በወቅቱ የተጋበዙት ግን ከኢሰፓ ውጪ የነበሩት የታጠቁና ያልታጠቁ ፓርቲዎች (ኢህአፓም ጭምር) ነው ኢህአፓ በትእቢት ተወጥሮ ወያነ በጠራው ኮንፈረንስ አልሳተፍም ብሎ ቢቀርም:: ሃቁ ይሀ ሁኖ ሳለ የኢህአፓ ትእቢት ላለመቀበል ሲባል ኢህአፓ እንዳልተጠራ አድርጎ ማቅረብ የምን ታሪክ ማዛባት ነው:: የኢህአደግ ስህተቶች ተብለው የተጠቀሱትም ቢሆን ለኔ እንደሚገባኝ እነሱ ሳይሆን ከጅምሩ ጀምሮ በደርጎችና ኢህአፓዎች ሲነዛና ሲዘራ የነበረው በአንድ ብሄር ያነጣጠረ ዘረኛ የበሬ ወለደ ወሬና አሉባልታ በሚገባ እየተመከተ አዲሱን ትውልድ እንዳይበርዝ አለማድረጉና ችላ ብሎ ማለፉ ነው::
አቶ እውነቱ በአቶ ገዱ ላይ የተቀመጡት የግለ ሰቦች የግል አስተያየቶች በመቃወም የተሰማቸውና የሚያምኑበት መልስ መስጠታቸው መብታቸው ስለሆነ በምንም መለኪያ ስህተት አይሆንም:: በአቶ ገዱም ሆነ በራሳቸው ላይ እንዲደርስ የማይፈልጉት ያልተገባና ያልተጣራ የሚሉትን አይነት አስተያየት መስጠት ግን በዚሮ ማባዛት ነው:: አቶ ገዱ አቶ እውነቱ እንዳስቀምጧቸው መልአክ ኣይደሉም በሌላ በኩል አቶ ብርሃነ እንዳስቀመጧቸውም ሰይጣንም አይደሉም ሰው በመሆናቸው የፈፀምዋቸው ጉድለቶች ይኖራሉ ለወደፊቱም ከዚህ ነፃ አይሆኑም ዋና ነገር የተፈፀሙት ስህተቶች መታረማቸው ላይ ነው ትኩረት መደረግ የነበረበት::
የአቶ እውነቱ ሶስቱም ፅሁፎቻቸው ተመሳሳይ ናቸው በሳቸው እምነት በትግርኛ ተናጋሪ የሚባል ሁሉ ለኢትዮጵያ የማይጠቅምና የወረደ እንደሆነ አማርኛ ተናጋሪ እንኳ ቢሆን ትግራዋይ የሚለው እውነት የሚደግፍ ከሆነ ሰይጣን እንደሆነ ለማሳየት ሲባል ሰላምወርቅ የተባሉ ፀሃፊ ያስቀመጧቸው ሂሶች ከማስተባበል ይልቅ ፀሃፊው የትግራይ ተወላጅ ስለመሆናቸው ለማሳመን ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም ስለሆነም ይህ የቆየው የገዢ መደቦችና የኢህአፓዎች የትግራይን ስም የማጥፋት ዘመቻ አካል ስለሆነ በአቶ ብርሃነ ፅሁፍ መልስ ለመስጠት የተፃፈው ፅሁፋቸው ላይ ትኩረት በማድረግ አንዳንድ ነገር ልበል::
1/ አቶ እውነቱ በአማራ ክልል የተፈጠረው ምስቅልቅሉ የወጣ አስተዳደራዊና ፖለቲካዊ ሁኔታ የፈጠረው ህወሓትና አንዳንድ የትግራይ ተወላጅ ፀሃፊዎች እንደሆኑ ለዚህም ከጅምሩ ህወሓት በእጅጉ ዘረኛ የሆነ አስተሳሰብ ኮትኩቶ በማሳደግ ህይወት እንዲዘራበት ያደረገው ህወሓት ነው ይሉናል:: ይህ ፍፁም አዲስ ነገር የሌለበትና ኢህአፓዎች ሲፈጠሩ ጀምረው ስለ ብሄርህ ማሰብ ዘረኝነት ነው ብለው ሲከሱ የነበሩት አፋቸው የከፈቱበት ፖለቲካ ነው:: አማራ እንዲህ ሆነ፤ ትግሬ አገር የለውም ኦሮሞ እንደዚህ ነው እያለ ሲጮህ ጊዜውን የሚያሳልፈው ግን ህወሓት አለመሆኑንና ህወሓት ለአማራ ህዝብ ምኑ እንደሆነ ሰፊው የአማራ ህዝብ ስለሚያውቀው አውቆም በ36ኛ የብአዴን ልደት በዓል የደብረታቦር ህዝብ ያስቀመጠው እውነት ይመሰክራል:: ስለሆነም የእናቴ ቀሚስ ከመሆን አልፎ ውሃ አይቋጥርም::
2/ ባለፈው ጊዜ የተፈጠረው የስድስተኛ ክፍል መፅሃፍ ላይ የተከሰተው ስህትት ህወሓት ሆን ብሎ አደረገው ብለው ይከሳሉ (ኣቶ ተኮላም ደግመውታል) ይህ በማስረጃ ያልተረጋገጠ የስም ማጥፋት ዘመቻ መሆኑን ሳይታለም የተፈታና ወደ ትክክለኛ ማጣራት ተወስዶ መረጃው እንዳይገኝ የማሳሳት ጉዳይ ካልሆነ በወቅቱ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ሃላፊ ኣማራ የመስሪያ ቤቱ ሰራተኞች ከ60% በላይ አማራ በሆኑበትና በመስሪያ ቤቱ የሚሰራ የትግራይ ተወላጅ ከ5% በማይበልጥበት መስሪያ ቤት እንዴት ብሎ ህወሓት እንደሰራው ግልፅ አይደለም ወይስ መፅሃፉ የታተመው መቀለ ነው ሊሉን ነው:: ይህም ጅራፍ ራሱ ገርፎ እንዳይሆን እኔ እንደሚመስለኝ በየቦታው የተሰገሰጋችሁ ኢህአፓዎች ራሳችሁ ሰራችሁት ከደበቃችሁት ደግሞ ፈትሻችሁ አወጣችሁት:: አረ ለመሆኑ በአማራ ክልል ህወሓትና የትግራይ ተወላጆች ይህ ሁሉ ለብጥብጥና ሁከት የዳረገ ስራ ሲሰሩ ይሀ ሁሉ 26 ዓመት የት ነው ተኝታችሁ የነበረው ለክልሉ ህዝብ ምንም አልሰራችሁም ማለት እኮ ነው:: እንደዚህ ከሆነ መፍትሄው ምን ይሁን ይላሉ?
3/ ሌላው በጣም አስገራሚና በትግራይ ህዝብና ተወላጅ ላይ ያላቸው ቅጥ ያጣ ጥላቻ የሚያሳየው በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ሃላፊ የሆኑት ዶ/ር አዲሱ የሰዘነሩት ዘረኛ አባባላቸው ነው:: ዶ/ር አዲሱ የሰብአዊ መብት ኮሚሽኑ ሃላፊ ስለሆኑ ኮሚሽኑ የደረሰበትን ድምዳሜ ለሾማቸው አካል ሪፖርት የማቅረብ ሃላፊነት ስላለባቸው አቀረቡና በአቶ እውነቱ ተከሰሱ እዚህ ላይ ኮሚሽኑ ለሚሰራቸው ስህተትና ስህተቱም እንዳለ ተቀብለው ሪፖርት ካቀረቡ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ዶ/ር አዲሱ ያውቃሉ ግን ያቀረቡት ሪፖርት “የክልሉ ባለስልጣናት የቅማንትን ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ጥያቄ ህገ-መንግስቱ በሚፈቅደው መንገድ አላስተናገዱም አልፎም እንግልትና እስራት ታይቷል፤ የክልሉ የፀጥታ ሃይልም አድልዎ ፈፅመዋል” የሚል ነው ይህ ደግሞ እርስዎም በፅሕፉዎ ገልፀውታል ታድያ እዚህ ደርሶ ዶ/ር አዲሱ የሚያስወቅስ ምን ተገኘ:: ለመሆኑ ዶ/ር አዲሱ የኮሚሽኑ ሃላፊ በመሆናቸው የሚከሰሱ ከሆኑ በስድስተኛ ክፍል መፀሃፍ ላይ የተከሰተው ችግር በወቅቱ ሃላፊ የነበሩ አቶ ደመቀ፤ በአማራ ክልል የተከሰተው ችግር የክልሉ ፕረዚዳንት የሆኑ አቶ ገዱ ለምን አይከሰሱም ይላሉ አቶ እውነቱ? ነው ወይስ አማርኛ ተናጋሪ የፈለገው ቢያጠፋ አይከሰስም እያሉን ነው? ንጉስ አይከሰስም ሰማይ አይታረስም የሚለው የአባቶችዎ ብሂል ይዘው ከሆነ አይሰራም እንዳይመለስ ተቀብረዋል::
4/ አቶ እውነቱ የአቶ ብርሃነ ፅሁፍ ሲቃወሙ በመጨረሻ የወረደ እንደሆነ የብአዴን አባላትና የአማራ ህዝብ ቢሰማው ጥሩ ስላልሆነ የተወሰነ ብቻ እንደናገሩና ከወረደ ፅሁፍ ጋር መውረድ ትክክል እንዳልሆነ ይህም ለህወሓትና ለትግራይ ህዝብ እንደማይጠቅም ሊነግሩን ሞከሩ:: እስቲ መለስ ብለው ፅሁፍዎን ያንብቡት የትግራይ ተወላጆችና ህወሓት በአማራ ክልል የተፈጠረው ችግር እንዲፈጠር ምክንያት ሆነዋል፤ ህወሓት ጠባብ ፍላጎቱ ለማሟሟላት ሲል ዘረኛ አስተሳሰቡን ለማስረፅ ከቅማንት ህዝብ ጥያቄ ጀምሮ እስከ የስድስተኛ ክፍል መፅሃፍ የተፈጠረው ችግር ፈጣሪና ተጠያቂ ነው፤ በአጠቃላይ ከጎሳና ዘር ግጭት ውጪ ህወሓት/የትግራይ ህዝብ ለዚህች አገር ምንም አልፈየዱም እያሉን አይደለም ለዛውም ባልተጨበጠና አልፎም ራሳችሁ የሰራችሁትና ያጠፋችሁት በመለጠፍ::
5/ አቶ እውነቱና አቶ ተኮላ የአቶ ብርሃነ ፅሁፍ ስትቃወሙ ስለአማራ ክልል ምን አገባው ለአማራ ክልል ህዝብና መንግስት እንዲሁም መሪ ድርጅቱ ብአዴን መተው አለበት ብለችኋል፤ ከኛ በላይ ላሳር የሚለውን የእንስሳ አስተሳሰባችሁ ነው እንጂ ማንም ሰው የሚታየው ነገር መፃፉ ሃጢኣት ሆኖ አይደለም እንኳንና ኢትዮጵያዊ የውጭ አገር ዜጋም ቢሆን ሃሳብ ማቅረብ ይችላል ገምቢ ከሆነ ትቀበላለህ ካልሆነ ትተወዋለህ፤ በኔ እምነት በአቶ ብርሃነ ፅሁፍ የተጠቆሙት ትችቶች ሳይሆን ድምዳሜው ላይ ግን በድርጅቱና በፍርድቤት ጉዳይ በመግባት መዘበራረቅ አልነበረትም እላለሁ:: ለመሆኑ እናንተ እንደዚህ አላችሁ ስለወልቃይት ጎንደር ላይ ሁኖ መጮህ በአንድ ክልላዊ መንግስትና ህዝብ የውስጥ ጉዳይ እጅ ማስገባትስ ምን የሚሉት ወጥ መርገጥና ድፈረት ብላችሁ ነው የምታዩት ለዛውም በባለስልጣናት ደረጃ:: ስለወልቃይት ህዝብ የሚቆረቆረው ጎንደሬ ነው ብላችሁ ነው የምታምኑት?
6/ ሌላዋ ትንሽ የምትመስል ግን ደግሞ ሆን ተብላ የራስዋ መልእክት ለማስተላለፍ በአቶ እውነቱ የተቀመጠች ድግሞ ህወሓት ብለው ለመጥራት ሲፈልጉ ህወሓት/ኢህአደግ ብለው የሚያስቀምጡት ብአዴን ብለው ለመናገር/መፃፍ ሲፈልጉ ደግሞ ብአዴን/ኢህደን ብለው ነው የሚፅፉትና ብአዴን ኢህአዴግ አይደለም እያሉን ነው ወይስ ምን ማለታቸው መሆኑ ስላልገባኝ በቀጣይ ፅሁፍዎ ማብራርያ እንዲሰጡኝ አስቤ ነው:: ምክንያቱ ብአዴን ኢህአደግ ነው ብለን አስበን ስለሆነ የምንናገረው ከውስጥ አዋቂዎች እነ አቶ እውነቱ ማብራርያ ያስፈልጋል::
በመጨረሻ አቶ እውነቱ በትግራይ ኦንላይን፤ በአይጋ ፎረምና በውራይና የማይረባ ፅሁፎች እያወጡ እንዳለሽቸገሩና ሚዛናዊነት እንደሚጎድላቸው ነው የነገሩን እነዚህ ድህረ ገፆች ግን የእርስዎ አንድ ብሄር የሚያንቋሽሽ ፅሁፍ ይዘው የወጡት የግልዎ አስተያየት ስለሆነ ለእርሰዎም እያስተናገዱ ነው:: በኔ እምነት ግን የወጡት ፅሁፎች ሃላፊነት ያለበት ፀሃፊው ይመስለኛል ሚዛን የማስያዝ ደግሞ ሁላችን በእውነትና በማስረጃ አስደግፈን በመወያየትና መልስ በመስጠት እንጂ ሁላችንም የመሰለንና ያመንበት የመግለፅ ህገ-መንግስታዊ መብታችን ነው:: እርስዎ የአቶ ብርሀነ ሃሳብ መንቀፍ በመሰልዎት እንደገለፁት እኔ ደግሞ የሁላችሁም በመሰለኝና በማምንበት የመግለፅ መብት አለኝ በቃ ከዚህ በዘለለ ስለየትግራይ ህዝብ/ተወላጅና መሪ ድርጅቱ መጥፎ ስም ሲሰጥ ትክክል ስለ አማራ ህዝብ/ተወላጅና መሪ ድርጅቱ ብአዴን መጥፎ ሲወራ የሚያንገበግብ መሆን አይችልም ለሁሉም እኩል ነው ሁሉም የነሱ ያልሆነ የፈጠራ ወሬ የደካሞችና አቅመ ቢሶች ተግባር ነው:: ስለሆነም እኔ በበኩሌ በትግራይ ህዝብ/ተወላጅና መሪ ድርጅቱ ላይ እንዲሆን የማልፈልገው በአማራ ህዝብ/ተወላጅና መሪ ድርጅቱ ብአዴን እንዲፈፀም አልፈልግም::
************
ለሌተናል ጀረናል ፃድቃን ገ/ተንሣይ የተሰጠ መልስ
ለረጅም ዘመናት በትምክህተኛ ሥርዓትና የአፈና መዋቅር መዳፍ ስር በመውደቅ ሰብአዊ ክብሩንና መንነቱን፤ ሰብአዊ መብቱን ተነፍጎና ተነጥቆ፤ ተዋርዶ በአገሩ ውስጥ የመኖር ዋስትናውን አጥቶ እንደ ሁለተኛ ዜጋ ተቆጠሮ ጎስቋላና አሳዛኝ ሕይወት ውስጥ ኖሯል፡፡ ነገር ይህንን የህዝባቸውን አሣፋሪና አሣኝ ሶቆቋ የተሞላበት ሕይወት መሸከም ያቋታቸው ጥቂት የሕዝብ ልጆች የዩኒቨርስቲ ትምህርታቸውን በማቋረጠ ሞራልና ወኔ ሰንቀው ወደ በረሃ በመግባት ይህን አስከፊ የሆነውን የትምክህተኛው ፋሽሽታዊው የደርግ ስርዓት መላ የኢትዮጽያ ሕዝብ ከጎናቸው በማሰለፍ በተራዘመ የትጥቅ ትግል ለማሸነፍ ዓላማ በመያዝ ከፍተኛ የሆነ መስዋትነት በመክፈል ለማመን የሚከበደውን በአፍሪካ ተወዳዳሪ ያልተገኘለት ወታደራዊውን የደርግ ስርዓት ለመገርሰስ ተችሏል፡፡ የትግራይ ሕዝብም በመሪ ድርጅቱ ሕወሓት በመመራት ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች በጋራ በመሆን በመግንባር ቀደምትነት በመሰለፍ ከፍተኛ የሕይወትና የንበረት መስዋእትነት ከፍለዋል፡፡ በመሆኑም እንደሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች በአገሩ ውስጥ የሰላም አየር እየተነፈሰ ይገኛል፡፡ በአገር በኢኮኖሚ፤ ሰላም ዲሞክራሲ ግንባታ በኩል እንደ ክልልም እንደ ሃገር የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ይገኛል፡፡ ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ያለው ግንኙነት በተመለከተ በመከባበር በመደገጋፍና በመተሣሰብ በሰላምና ዲሞክራሲ ግንባታ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል፡፡ የሃገራችን ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ተወይይተውበት፤ መርጠው በላኳቸው ተወካዮች የፀደቀው ሕገመንግሥት የሀገሪቱን ሕዝቦች የቡድንና የግል መብቶች አረጋጧል፡፡ የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች፤ የፍትሐዊ ተጠቃሚነትና ተሣታፊነት ድርሻን በግልጽ ደንግጓል፡፡ ላለፉት 25 ዓመታትም በድልና በጠንካራ ህብረ ብሔራዊ አንድነት ተጉዘንበታል፡፡ በጎረቤቶቻችንም ይሁን በአለም አቀፍ ደረጃ ተአማኒታችን ተሰሚነታችን ወደ ላቀ ደረጃ እንዲሸጋር አስችሏል፡፡ በውጭ ፖሊሲያችን ግንኙነታን በሰራነው ሥራ መሠረት ከአሁን በፊት ወደ አገራችን መጥተው የማያውቁ የሀያላን መንግሥታት መሪዎች ወደ አገራች መጥተዋል ውይይትና ገለጻ አድርገዋል፡፡ ለአብነት ኘረዚዳንት ኦባማ ስንመለከት በአገራችን አጠቃላይ የሰላም ማስከበር ሂደት አገራችን ሲያስቀም|ጧት “Ethiopia is one of the Best in the World” ይህ ቅን ለሆነ ኢትዮጽያዊ ዜጋ በሙሉ ሊያስደስተውና ሊኮራበት የሚገባ ሐቅ ነው፡፡ ለሐገራቸው ደንታ የሌላቸውና የራሣቸው ምቾትና በትምክሕት ለተወጠሩ ሰዎች ሞት፤ ሽንፈት ውርደት ይመስላቸዋል፡፡ ምክንያቱም የትምክህት ሀይሉ የኖረና እየኖረ ያለው በእብሪት በትእቢት ስለሆነ ኢትዮጵያዊነት ማለት ለሱ አንድ ቋንቋ አንድ ሀይማኖት የግዛት አንድነትና ጨፍልቆ መግዛት መኮፈስ በባዶ በወሬ ሳይሰራ መስዋእትነት ሳይከፍል ታዋቂ የአገር ፈላጭ ቆራጭ አንባገነን መሪ መሆን፤ ለሕዝቡ ውሸት እየነገረ ታላቅ ሕዝብ ነህ እያለ በድህነት እንዲማቅቅ ያደረገና ወደ ኋላ እንዲመለስ ሌት ተቀን እየሰራ ይገኛል፡፡ በአሁኑ ወቅት ስንት መስዋእትነት በመክፈል በትግሉ ያረጋገጠውን መብት ለመንጠቅ የተለያዩ የውጭና የውስጥ ሀይሎች ግንባር በመፍጠርና ውል በመፈራረም(ሻእብያ፤ ግንቦት 7 እና ኦነግ) እንዲሁም አፈንግጠውና መድረክ ረግጠው የወጡ የሕወሓት አመራር፤ ከድተው የገቡ እነ ገብረመድህን እንዲሁም በትግለ ወቅት ከድርጅት በሰላማዊ ውይይት ተሸንፈው የተሸኑ እነግደይ ዘርኣጽዮን እና አረጋዊ በርሀ በመንግሥታችን በተለይ ደግሞ በትግራይ ሕዝብ ላይ ከፍተኛ ዘመቻ ከፍተዋል፡፡ ከሁሉም በላይ የሚገርመውን በዚህ በትጥቅ ትግል ወቅት ለረጅም ዓመታት የታገሉለትና መስዋእትነት የከፈሉለትና መሪ ድርጅት ሕወሓት ውስጥ ሲያታግሉና ሲታገሉ የነበሩ ከድል በኋላም በከፍተኛ የመንግስት እርከን በመቀመጥ ሲመሩ የነበሩ አመራሮች ነገር ግን በትምክህት፣ በጥበትና በኪራይ ሰብሳቢነት ዙሪያ ድርጅቱ ራሱን ለመፈተሽ ለማጽዳት ባደረገው ግምገም ኪራይ ሰብሳቢነትን ከሚያቀነቅነው “አንጃ” ጋር በመወገንና በመሰለፍ ህገ መንግስቱን ተፃርረው በፖለቲካ ጉዳዮች ውስጥ በመግባት ሕዝብ የጣለባቸውን አደራ ወደ ጎን በመተው የራሣቸው አጀንዳ ሲያራምዱ የነበሩት ግለስብ ነዎት፡፡ የትግራይ ሕዝብ አሁንም ነፃ እንዳልወጣና ሕዝቡን ነጻ ለማውጣት ደግሞ ትግል የሚያስፈልግ መሆኑን ለዚሁም በጽረ ገጽ በለቀቁት ጽሑፍ የገለፁ ሲሆን መግሥት ሊያጋጥመው ይችላል ብለው የተነበዮት 3 የተለያዩ ስጋቶች (Scenarios) አስቀምጧል፡፡ ለእነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ስጋቶች ወይም ችግሮች መንስኤውም ያስቀመጡ ሲሆን እነዚህም እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
1ኛ. ኢህአዴግ ኦነግ ጋር በቅንጅት ያስቀመጠውን የመንግስትን አሰራርና ባህርይ መለክያ ይሆናል ያለውን መተግበር እያቃተው ሃገሪቱ ወዳልተፈለገ መንገድ እየገባች መሆኑን፤
2ኛ. ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎች የሚሰነዘርበትን ተቃውሞ መቋቋም የቻለው በመቶዎች የሚቆጠር የሰው ሂወት በመግደል ነው።
3ኛ. የትግራይ ተወላጆች ሆነው አሁን ያለው ሕገ-መንግስት የሚቃወሙ ሃይሎች እንዳሉ አውቃለሁ። ከነዚህ በላይ ግን ሕገመንግስቱ ሲጸድቅ በነበረው አብዮታዊና ዴሞክራሲያዊ መንፈስ አለመተግበሩ የሚቃወሙ ይበዛሉ፡፡ ከዚህ የተነሳም ሙሉ በሙሉ ተግባር ላይ ከዋለ ህገ-መንግስቱን የሚጠብቀው፣ የሚያዳብረው ኋይል ይበዛል ያሸንፋል። ይህንን ሕገ-መንግስት መጠበቅ በሚል ሰበብ አሁን ያለውን ስርዓት የመጠበቅ ሸክም ለምን በትግራይ ህዝብ ጫንቃ ላይ ብቻ ይወድቃል?
4ኛ. አሁን ያለው የፌዴራል መንግስት አወቃቀር መሠረት ያደረገ ህገ-መንግስታዊ ሥርዓት ሕገ-መንግስቱ እራሱ በሚፈቅደው አሰራር ተቀባይነት ላያገኝ ይችላል። በሌላ አነጋገር አዲስ ህገ-መንግስት ያስፈልጋል የሚል ሐሳብ አሸናፊ ሊሆን ይችላል። ይህ የሕገ-መንግስቱ አሰራር ተከትሎ ህዝቡን አሳምኖ በሰላማዊ መንገድ እስከተፈጸመ ድረስ የህዝብ ፍላጎት ነውና ተቀባይነት ማግኘት አለበት። አሁን ያለው ህገ-መንግስት በህዝብ ዘንድ በፍቃደኛነት ተቀባይነት እንዲኖረው ይህንን ሕገ-መንግስት የሚደግፉት ፖለቲካዊ ሃይሎች ሥራቸው ሰርተው በሰላማዊ መንገድ ካላሸነፉ ተሸንፈዋል ማለት ነው።
5ኛ. በርከት ባሉ የትግራያ ተወላጆች የሚነሳ አንድ ጥያቄ አለ፡፡ ይኸውም አሁን ባለው መንግስት ላይ ያለንን “የበላይነት” ካጣን ጠቅላላ መብቶቻችን አንድናጣ መልሰን እንድንጨቆን አድልዎ እንዲፈፀምብን ቢደረግስ ምን ዋስትና አለን? ዋስትናችን በትግላችን ያገኘነው አሁንም ከሌሎች ህዝቦች ጋር ሆነን እየታገልን የምንጠብቀው ሕገ-መንግስታችን ያለምንም ማቅማማት ተግባራዊ ማድረግ ነው። ሌላው ዋስትናችን ህዝቡ ራሱ ነው፡፡ የተወሰኑ የክልሉ ተወላጆች በፖለቲካዊ ሥርዓቱ ወሳኝ በሚባሉ የሥልጣን ቦታዎች ላይ መቀመጥ አይደለም።
6ኛ.“የትግራይ ህዝብ ከሌሎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር ባለው ግንኙነት፤ በተለይ አሁን ጠንክሮ መገኘት አለበት፣ የደከመ መስሎ መታየት የለበትም” ጠንክሮ መገኘት ማለት የመከላከያና የድህንነት ሃይል በመቆጣጠርና በማሰማራት ኢህአዴግና ይህ ድርጅት የሚመራው መንግስት የሚወስነው ውሳኔ ህዝብ ወደደሞ ጠላም ተቀብሎ እንዲሄድ ለማድረግ መንቀሳቀስ ነው? ወይም በፌዴራል መንግስት በንፅፅር ሲታይ በአገሪቱ ፖለቲካዊ ስርዓት ላይ ወሳኝ የተባሉትን የስልጣን ቦታዎች በብዛት መቆጣጣጠር ማለት ነው? ከዚህ አልፎም በየሄዱበት በተገኘው አጋጣሚ ሃይል ያለን መሆናችንን ለማሳየት መሞከር ነው? በአጠቃላይ ከኢህአዴግ በፊት የነበሩ ገዢ መደቦች ሲያደርጉት የነበረውን ለመኮረጅ መሞከር ነው ጠንክሮ መገኘት ማለት? ምንድን ነው?
7ኛ. በረጅምና መራራ ትግል የደርግ ስርዓት መፈራረስ የጀመረው በመጨረሻም የደርግን ስርዓት ሲያገለግል የነበረውን የኢትዮጵያ ሰራዊት በአስር ሺዎች እጁን ሲሰጥ የነበረው እኛ የትግራይ ታጋዮች የተለየ ጀግንነት ስለነበረን እነሱ ደግሞ ፈሪዎች ስለነበሩ አይደለም፤ እነሱም ጀግኖች ነበሩ፣ ግን የቆሙለት ዓላማ ከዳቸው፣ የቆሙለትን ፖለቲካዊ ዓላማ አምነው መከላከል ተሳናቸው፡፡ ውስጣዊ ጥንካሬያቸው በየግላቸው መፍረስ ጀመረ፡፡ ሌሎችን ጨቁኖ በመግዛቱ ላይ በተመሠረተ ፖለቲካዊ ዓላማና በብልሹ አስተዳደር የሚመራ ሰራዊት ደግሞ ውስጣዊ ጥንካሬ ይኖረዋል ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡
8ኛ. በመከላክያ ሃይል ጣልቃ ገብነት የሚጠበቅ የትግራይ ህዝብ መብት ይሁን ጥቅም የለም። ቀደም ብሎ የነበሩ ገዢ መደቦች የፈጸሙትን ስህተት ለመፈፀም ከቃጣን ደግሞ አንችለውም። እነሱን እንኳን ከትግራይ ህዝብ የበዛ ህዝብ፣ የበለጠ ሀብት፣ የተሻለ ተሞክሮ፣ የተሻለ የተማረ የሰው ኋይል ይዘው አልቻሉትም፣ ምክንያቱም አስተሳሰቡ አድሀሪ ስለሆነና ህዝብ ለመጨቆን የሚቃጣ ስለሆነ አይቆምም።
9ኛ. ከላይ የሚታዩት የሰራዊት አዛዞች የትግራይ ተወላጆች በርከት ብለው ቢታዩም ሰራዊቱ የኢትዮጵያ ህዝቦች ስብጥር ነው። በዚህ አካል ውስጥ ወገንተኛ የሆነ ፖለቲካዊ አቋም ከተያዘ ራሱን ተቋሙን ከውስጥ ለማፍረስ እንደወሰነ መታወቅ አለበት። በተቋም ያሉት አባላት የሁሉም የኢትዮጵያ ህዝቦች ልጆች ስለሆኑ በየብሔር ብሔረሰቦቻቸው ተከፋፍለው ተቋሙ ይፈረካከሳል። ይህ ደግሞ ሰበቡ እጅግ ከፍተኛ ነው። የአገር መከላክያ ሰራዊት የአንድን አገር ሉአላዊነት ጠብቆ አንድ አገር እንዲሰራ ከሚያስችሉት ተቋማት ዋናው ምሰሶ ነው። እዚህ ተቋም ውስጥ የሚመጣ መፈረካከስ አገሪቱ በሙሉ ይዞ ነው የሚፈረካክሰው። ስለዚህ ከፍተኛ ጥንቃቄ ይጠይቃል። ዋነኛው የጥንቃቄ እርምጃ ደግሞ እንደ ተቋም ወደ ወገንተኛ ፖሊቲካ (የብሔር፣ የፓርቲ፣ የኋይማኖት ወዘተ) አለመግባት ነው። ሕገ-መንግስታዊ ተልእኮውን ብቻ መፈጸም ነው። ስለዚህ የመከላክያ ሃይል በማጠናከርና በፖለቲካዊ ጫዋታ ውስጥ እንዲገባ ማሰብ በእሳት እንደመጫወት መሆኑ መታወቅ አለበት።
ከላይ የተጠቀሱት ዋና ዋና ሃሣቦች የተወሰዱት ከሌቴናል ጻዳቃን ገብረተንሣይ የሃገራችን ፖለቲካ ሁኔታና የመፍትሔ ሀሳቦች በሚል በድህረ ገጽ የተለቀቁት ሲሆን እነዚህ ከላይ የተቀመጡት ስጋቶች፤ ምክሮች ማስጠንቀቂያዎች፤ ማስፈራሪያች ጠቅለል ብለው ሲታዮ የትምክህተኞች፤ የጠባቦች፤ በአጠቃላይ ስልጣን በአቋራጭ እናገኝ ይሆን እንዴ ምክንያቱም መንግሥት በተለያዩ አከባቢዎች በሚከሰቱ የተፈጥሮ አደጋ ድርቅ ይሁን ሰው ሰራሽ ችግሮች ለአብነት አክራሪነት፤ ከአገራችን የኢኮኖሚ እድገት በመነሣት እየተከሰተ ያለውን የኪራይ ስብሳቢነትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ከፍተኛ ደረጃ ላይ ስለደረሱ በዚሁ ምክንያት ሕዝቡ በከፍተኛ ደረጃ ስለተማማረረ ኢህአዴግ የምንጥልበት ወቅቱ አሁን ነው በሚል ትንተናና የተሳሳተ ትንበያ እናንተ በኦሮሚያ፤ በአርባ ምንጭ፤ በአማራ ክልል አመፁን አቀጣጥሉት እኔና ጓደኞቼ ደግሞ ፁሑፍ በማዘጋጀትና በቪዲዮ የህብረተሰቡን አስተሳሰቡን፤ በመንግሥት ላይ ያለውን እምነት በመቀየር ተስፋ እንዲቆርጥ በማድረግ መንግሥት የሕዝብ ድጋፍ እንዳያገኝ በማድረግ ኢህአዴግ/ወያኔ አሽቀንጥረን ሥርዓቱን ንደን አዲስ መንግሥት እንመሠርታለን በሚል የተሣሣተ ስሌት በአገር ውስጥና በውጭ አገር የኒዮሊበራሊዝም ርእዮት አራማጆች የሚሰጥዋቸውን ፍርፋሪና ባዶ ተሰፋ በመሰነቅ ከነዚህ ሀይሎች የሚሰጣቸውን መመሪያ በመቀበል ውስጡ ውስጡን ሲሰሩይ ቆይተው አሁን በይፋ ገሃድ አውጥቶውቷል፡፡ በጣም የሚገርመው ለረጅም አመታት ምንም ትንፍሽ ሣይሉ በኢህአዴግ መንግሥት ይሁን በድርጅቱ አስተያየት ሳይሰጡ የግል ኑራቸውን እየኖሩ እየተማሩ ሃብት ለማከማቸው ሲራወጡ የቆዩ ግለሰብ ናቸው፡፡
ለቀረበው ፁሑፍ የተሰጠ መልስ
1. ከጠቀሱት የኢህአዴግ ድክመት አንዱ ኢህአዴግ ኦነግ ጋር በቅንጅት ያስቀመጠውን የመንግስትን አሰራርና ባህርይ መለክያ ይሆናል ያለውን መተግበር እያቃተው ሃገሪቱ ወዳልተፈለገ መንገድ እየገባች መሆኑን ያትታሉ፤
ነገር ግን ኦነግ በሽግግም መንግሥት ምሥረታ ወቅት ከሌሎች ድርጅቶች አብላጫ የሆነው ቁጥር በመውሰድ በስራ አስፈጻሚ በተለያዩ ተቋማት በርካታ ቦታዎችን ይዞ ሲንቀሣቀስ የነበረ ድርጅት መሆኑ ሕዝቡ በተለይ የኦሮሞ ተወላጆች ያውቃሉ ነገር ግን ከስር መሠረቱ ኦነግ አመራሮቹ በውጭ አገር ተቀምጠው በኦሮ ሞ ሪስም እየነገዱ ገንዘብ በመሰብሰብ የራሣቸውን የተደላደለ ኑሮ እየኖሩ ጫካ ውስጥ በመግባት የሕዝቡን ችግር እየተካፈሉ በቅርብ ሆነው ሲታገሉና ሲያታግሉ ያልነበሩ ፋሽስታዊውን የደርግ ስርዓት ማፍረስ ሳይሆን የደርግ ወታደር በመያዝ ስልጣን ለመያዝ የሚንቀሣቀሱ የነበሩ፤ ፍፁም የሆነ ሕዝባዊነት መሠረት የሌላቸው ከጫካ ሳይሆን በቦሌ የገቡ የድል አጥቢያ አርበኛ የነበሩ ናቸው፡፡ በመሆኑም ፀረ ዲሞክራሲና የፀባብነት ባሕርይ አሸንፎት በርካታ በደሎችና የሽብር ተግባራት በንፁሓን ህዝብ ሲፈጽም የነበረ ፀረ ሕዝብ ድርጅት በመሆኑ ጫካ ውስጥ በመግባት ጦርነት በማወጅና በመክፈት በሎኮሰው በጦርነት የተሸነፈ ድርጅት መሆኑና ከዚያም በኋላ የሻእብያ ተላላኪ በመሆን ባካሄዳቸው በርካታ የሽብር ተግባራት በአገር አቀፍና በአለም አቀፍ ደረጃ ሽብርተኛ ድርጅት ሆኖ እንዲፈረጅ ተደርጓል፡፡ በኦነግ በተካሄደው ጦርነት መምራት በኩል ስንመለከት በከፍተኛ የመንግሥት እርከን ተቀምጠው በኦነግ ላይ ሲደረግ የነበረው ኦኘሬሽን እንደወታደራዊ መሪነትዎ በግንባር ቀደም በመሆን ከጓድዎ በዛን ወቅት የመከላከያ ሚኒስቴር የነበሩት አቶ ስየ አብርሃ ስትመሩት ነበር፤ እንደ አመራር በሰራችሁት ስራም ኦነግ ከዛም ከዛም ካሰባሰባቸው አባላቱና ባርካታ የደርግ ወታደር ጨምሮ 80ሺህ ሰራዊቱ እንዲደመሰሱና እንዲማረኩ በመደረጉ የኢትዮጽያ ሕዝብ በተለይ የኦሮሞ ተወላጆች እነሆ ለ25 ዓመታት የሰላም አየር በመተንፈስና በልማት ጎዳና እንዲመነደግ አስችሎታል፡፡ ነገር ግን ከ1993 ዓ.ም ከድርጅቱና ከሰራዊቱ ከፍተኛ አመራርነት ከወጣችሁ በኋላ ለረጅም ዓመታ ድምጻችሁ አጥፋታችሁ የቆያችህ ግለ ሰቦች አሁን እየሆናችህ ያለውን ስመለከት በጣም ይገርመኛል ያስደምመኛል ቅዠት አይሉት እብደት፤ በኦነግ ላይ የተወሰደው እርምጃ በራሳችሁ መሪነት፤ ፊርማና ትእዛዝ ሆኖ እያለ አሁን ደግሞ ትክክል አልነበርንም እያሉ ይገኛሉ ይህ ነገር በሕዝብ፤ በአገር፤ በድርጅት ታላቅ ክሕደት ነው፡፡ ከዚህ የምገነዘበው እኔ ወደ ድርጅቱ ከተቀላቀላችሁ አንስቶ እስከ 1993 ከድርጅቱና ከመንግሥት ሀላፊነት እስከተወገዳችሁ ጊዜ ውስጥ የኢህአዴግ ካባ በመልበስ በድርጅቱ፤ በሕዝብና በመንግስት ብዙ በግልጽ የሚታዮና የማይታዩ ክሕደቶች ስትፈጽሙ የነበራችሁ መሆናችሁን ያመላክታል፡፡ የዚህ የፖለቲካ ድራማ ተግባር ስመለከት ደግሞ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ ቅሬታ በመፍጠር ሕዝቡን በማነሣሣት ለአመጽ እንዲነሣ ለድረግ ሲሆን የኦሮሞ ሕዝብ ከማንኛው ጊዜ በላይ መብቱ ተከብሮለት ከሁሉም የኢትዮጽያ ብሔር ብሔረሰብ ተከባብሮ አገሩንና ክልሉን እያለማ ከልማቱም ተጠቃሚ ስለሆነ በናንተ በኩል የሚለቀቁ ማደናገሪያ የፖለቲካ ቁማር ፁሑፎች ጠንቅቆ ያውቃል አይደናገርም፡፡ በመሆኑም እንደ አቶ ገብሩ አስራት መስቀል አደባባይ ወጥታችሁ ይቅርታ ብትጠይቅ የተሻለ ይመስለኛል፡፡
2ኛ. ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎች የሚሰነዘርበትን ተቃውሞ መቋቋም የቻለው በመቶዎች የሚቆጠር የሰው ሂወት በመግደል ነው።
ኢህአዴግ በመጀሪያ ደረጃ ወደ በረሃ የገባው የአገራችን ብሔር ብሔረሰቦች ይደርስ የነበረውን ጭቆና፤ ግፍ በደል ከሚሸከመው በላይ ስለሆነበት ወደ በረሃ ሊገባ ችሏል፡፡ በረሃ ውስጥም ሕዝባዊነት በመላበስ ከህዝቡ ጋር ሆኖ ፍፁም ርሕራሔና ትሕትና ፍቅር በተሞላበት ዲሲፒሊን ሲታገልና ሲያታግል የቆየ ድርጅት፡፡በረጅሙ መራራውና እልህ አስጨራሹ የትግል ወቅት በድርጅቱ ውስጥ የሚያጋጥሙ ፈታኝ የሆኑ ችግሮች ድርጅቱ በዲሞክራሲያዊ መንገድ ይፈታው እንደ ነበር ከድርጅቱ የተሰነዱ ፁሑፎች ቪዲዮዎች ምስክር ናቸው፡፡ ለአብነት በ1977 ዓ.ም. በመሪ ድርጅቱ ሕወሓት የማእከላዊ ኮሚቴ አባላት ታጥሮ የቆየውን የሀሳብ ልዩነትና የድርጅቱ ወደ ኋላ የማሽቆልቀል አደጋ ከመላ አባላቱና የማእከላዊ ኮሚቴ አመራሮች በርካታ ተከታታይ ቀናት የወሰደ ዲሞክራሲያዊ ውይይት በማካሄድ ከተሣሣተ ርእዮትና አመለካከቱ አመራሩና አባላቱን በማጽዳት ድርጅቱን ከማሽቆልቆል አደጋ ታድጎት ድርጅቱ ሕወሓት/ኢሕአዴግ ወደ ላቀና ቀጣይ ወደ ወታደራዊ ድል የሚያበቃ አቅም የሚፈጥር ፋሽሽታዊው ደርግን በአጭር ዓመታ እድሜውን የሚያሣጥር ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረና የአገራችን ኢትዮጰያ መፃኢ ብሩሕ ተስፋ የቀየሰ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ በዚህ ወቅት የተለየ ሃሣብና ርእዮት የነበራቸው እነ ግደይ ዘርኣጽንና አረጋዊ በርሀ በሰላም ወደ ፈለጉት አገር እንዲሸኙ ተደርጎ እነሆ እስከ አሁን በውጭ አገር በሕይወት እየኖሩ ይገኛሉ፡፡ በተጨማሪ በ1993ዓ.ም. በተፈጠረው የሀሣብ ልዩነት አንጃ ሁኖ የወጣው የሕወሓት አመራር አሁን በሰላም እየኖሩ ግማሹ ትምህርቱ እስከ ፒኤችዲ በመማርና ሃብት አፍርቶም ባለሀብት ሆኖ በሰላም እየኖረ ያለና ነገር ግን ያለፈበት ታሪክ ረሰቶና የግልሉ ጥቅም በማስቀደም ሕዝቡ የሰጠውን አደራና ያለፈውን የሕዝቦች ግፍና ሰቆቃ በመርሣትና በመናቅ ወደ ሌላ ተግባር የገባ አለ ሌላው ደግሞ የግሉ ጥቅም ሳያስቀድም ወዲያና ወዲህ ሳይል በሰላም ኑሮውን የሚመራ አለ፡፡ ነገር ግን በሌሎች ድርጅቶች ስንመለከት እንደዚህ አይነት ክስተት ሲፈፀም መደምደሚያ የሚሆነው በመገዳደል ነው፡፡ ለአብነት በኢህአፖና በሰደድ፤ በመኢሶንና ኢሕአፖ፤ ተሓት፤ ተሓኤ ማየት ይቻላል፡፡ በመሆኑም እናንተ ከድርጅቱና ከከፍተኛ የመንግሥት አመራርነት ስለወጣችሁ ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎች የሚሰነዘርበትን ተቃውሞ መቋቋም የቻለው በመቶዎች የሚቆጠር የሰው ሂወት በመግደል ነው ሊያስብል የሚችል ተጨባጭ የሆነ ነገር የለም ቃሉም ከእርስዎ የሚጠበቅ አይደለም አይመጥንዎትም።
3ኛ.የትግራይ ተወላጆች ሆነው አሁን ያለው ሕገ-መንግስት የሚቃወሙ ሃይሎች እንዳሉ አውቃለሁ። ከነዚህ በላይ ግን ሕገመንግስቱ ሲጸድቅ በነበረው አብዮታዊና ዴሞክራሲያዊ መንፈስ አለመተግበሩ የሚቃወሙ ይበዛሉ፡፡ ከዚህ የተነሳም ሙሉ በሙሉ ተግባር ላይ ከዋለ ህገ-መንግስቱን የሚጠብቀው፣ የሚያዳብረው ኋይል ይበዛል ያሸንፋል። ይህንን ሕገ-መንግስት መጠበቅ በሚል ሰበብ አሁን ያለውን ስርዓት የመጠበቅ ሸክም ለምን በትግራይ ህዝብ ጫንቃ ላይ ብቻ ይወድቃል? ሕገ መንግስቱ ሁሉንም የብሔር ብሔረሰቦች ጥያቄ በሚመልስ መንገድ ተደርጎ ተዘጋጅቶ በብሔር ብሔረሰብ ተወካዮቻቸው በኩል በሙሉ ድምጽ ተቀባይነት አግኝቶ የፀደቀ ሕገ መንግሥት ነው፡፡ ከዚሁም ብሔር ብሔረሰቦች ባለፉት 25 ከዚሁ ሕገ መንግሥት በኢኮኖሚ፤ በሰላም፤ በባሕላቸውና በእመነታው ከማንኛው ሥርአቶችና ጊዜያቶች ተጠቃሚ አድርጓቿል፡፡ ስለዚህ ይህ ሕገ መንግሥት ሁሉም ዜጋ የሚጠብቀው ሕገ መንግሥት ነው እንጂ በትግራይ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ሊወድቅ የሚገባው ሕገ መንግሥ አይደለም ላድርግ ቢልም አይችል፡፡ ከመጀመሪያው የትግል ወቅት አንስቶ ሕወሓትና የትግራይ ሕዝብ ግንባር ቀደም ድርጅት በመሆን መስዋእትነት የከፈለና አሁንም በመክፈል ላይ ያለና ሌሎች ብሔራዊ ድርጅቶችና ሕዝቦች እንደዚሁ ግንባር ቀደም በመሆን መስዋእትነት በመክፈል የሚገኙ ናቸው፡፡ ነገር ግን ግንባር ቀደም በመሆን ለአገሩ መስራት መስዋትነት መክፈል አያስነውርም፡፡
4ኛ. በርከት ባሉ የትግራያ ተወላጆች የሚነሳ አንድ ጥያቄ አለ፡፡ ይኸውም አሁን ባለው መንግስት ላይ ያለንን “የበላይነት” ካጣን ጠቅላላ መብቶቻችን አንድናጣ መልሰን እንድንጨቆን አድልዎ እንዲፈፀምብን ቢደረግስ ምን ዋስትና አለን? ዋስትናችን በትግላችን ያገኘነው አሁንም ከሌሎች ህዝቦች ጋር ሆነን እየታገልን የምንጠብቀው ሕገ-መንግስታችን ያለምንም ማቅማማት ተግባራዊ ማድረግ ነው። ሌላው ዋስትናችን ህዝቡ ራሱ ነው፡፡ የተወሰኑ የክልሉ ተወላጆች በፖለቲካዊ ሥርዓቱ ወሳኝ በሚባሉ የሥልጣን ቦታዎች ላይ መቀመጥ አይደለም።
መልስ አቶ ፃድቃን ምን እያልክ ነው? የትግራይ ሕዝብ የበላይ ሆኖ ሊያመጣው የሚችል ሰላም፤ ዲሞክራሲ እንዲሁም ልማት የለም ሁሉም የብሔር ብሔረሰቦች በጋራ በመተሣሰብ በመደጋገፍ ነው፡፡ በትግል ወቅት የበረው ሁኔታና ኢህአዴግ በምርጫ ስልጣን ከያዘበት ጀምሮ ያለው ሁኔታ ፍፁም የተለየ ነው፡፡ ምክንያቱም የደርግ ሥርዓት በረጅም የትግል ጉዞ ለማሸነፍ ወደ ደደቢት በረሃ የገባ የመጀመሪያና አንጋፋ ድርጅት የነበረ በመሆኑ ትግሉን በበላይነት እየመራ የመጣ ድርጅት መሆኑንም ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን የፌዴራል አስተዳደር ሥርዓት በመላ አገሪቱ ከዋቀረ ጊዜ ጀምሮ ከፍተኛው ስልጣን ያለው በክልሎች ነው፡፡ በማእከል ያለው የተወካዮች ምክር ቤት እና የፌዴሬሽን ምክር ቤት ደግሞ የተዋቀረው በክልሎች ባላቸው የሕዝብ ቁጥር ውክልና ነው፡፡ በሥራ አስፈጻሚ ወይ በሚኒስቴርነት ወይም ሚኒስቴር ዴታ እንዲሁም ባለሥልጣን በተመሣሣይ ነው፡፡ አንድ ዋናው ቁም ነገርና ሊታሰብ የሚገባው ነገር ካለ ፍትሃዊ የሆነ ሥራ እየሠራ ሰላም ዲሞክራሲ ልማት ብልጽግና አመጣ ወይ የሚለው ጉዳይ ሊሰመርበት ይገባል፡፡ በመሆኑም የትግራይ ተወላጆች በፖለቲካዊ ሥርዓቱ ወሳኝ በሚባሉ የሥልጣን ቦታዎች ላይ በማስቀመጥ መብቶቻው ማስጠበቅ እንደማይቻል ለማንም ግልጽ። ምክንያቱም የሕብረተሰቡ መብት የሚጠበቀው ሕዝቡ አርቅቆ ባፀደቀውና ተግባራዊ ባደረገው ሕገ መንግሥት በመሆኑ፡፡ ነገር ግን አሁን አቶ ፃድቃን እያሉን ያሉት የትግራይ ሕዝብ በበላይነት እየመራ እንደሆነና እሱ ካስወገድነው በስንት መራራ መስዋእትነት በብሔር ብሔረሰቦች የፀደቀውን ሕገ መንግሥቱ በቀላሉ ማፍረስ ወይም መናድ እንደሚቻልና አቶ ፃድቃን ያረቀቁት አዲስ ሕገ መንግሥት ደግሞ ለአገሪቱ በጣም ጠቃሚ መሆኑና በተጻፈው የአቶ ፃድቃን የወረቀት ሕገ መንግሥት የትግራይ ሕዝብ የሚጠበቅ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ይህ አባባል ፍፁም ስሕተትና የሕዝብ ንቀት ነው፡፡
5ኛ. በመከላክያ ሃይል ጣልቃ ገብነት የሚጠበቅ የትግራይ ህዝብ መብት ይሁን ጥቅም የለም። ቀደም ብሎ የነበሩ ገዢ መደቦች የፈጸሙትን ስህተት ለመፈፀም ከቃጣን ደግሞ አንችለውም። እነሱን እንኳን ከትግራይ ህዝብ የበዛ ህዝብ፣ የበለጠ ሀብት፣ የተሻለ ተሞክሮ፣ የተሻለ የተማረ የሰው ኋይል ይዘው አልቻሉትም፣ ምክንያቱም አስተሳሰቡ አድሀሪ ስለሆነና ህዝብ ለመጨቆን የሚቃጣ ስለሆነ አይቆምም።
መልስ በመከላክያ ሃይል ጣልቃ ገብነት የሚጠበቅ የትግራይ ህዝብ መብት ይሁን ጥቅም የለም። አቶ ፃድቃን ይህ ፁሑፍ ሲፁፉ ምንም ዓይነት መልእክት ለማስተላለፍ እንደፈለጉ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ በቀድሞ አያቶቻችን ሲነገር የቆየ ተረት አለ ይኸውም ጅብ በቀደደው ውሻ ይገባል የሚል አባባል አለ፡፡ በመሆኑም በአገራችን በተፈጠረው የመልካም አስተዳደር ችግሮችና የተፈጥሮ አደጋዎች ህዝቡ የሚያሰማቸው ብሶትና ምሬቶች አሉ፡፡ እነዚህ ችግሮች ደግሞ ግዚያዊና ሊፈቱ የሚችሉ ችግሮች መሆናቸው እየታወቀ ከአሁን በፊት በኢትዮጽያ ሕዝብ ከዚህ የከፋ ችግር ያውም ወጣቱ ከያለበት እየታደነ በቀይ ሽብር በነፃ እርምጃ በተገኘበት ሲገደል የነበረ፤ በየእስር ቤቱ ሲማቅቅ የነበረ፤ እየተያዘ ወደ ጦር ግንባር በመላክ በ100 ሺዎች የሚቆጠር ወጣት ያለቀበትና የተሰደደበት ዘመን አሳልፈዋል ነገር ግን የትምክሕተኛው ሀይል እና የጥፋት ሀይሎች ቀደም ሲል በኢትዮጽያ ሕዝብ የፈፀሙትን በደል ባለመፀፀትና በመርሣት የሕዝብ ተቆርቋሪ በመምሰል የህዝቡን ጥያቄ የራሣቸው አጀንዳ በማስመሰል የኢትዮጽያ እድገት የማይመኙና በቅናት ዛር በተዘፈቁ ሀይሎች በሚበረከትላቸው እርዳታና ገፀበረከት በመታገዝ በአገራችን የጥላቻ ፖለቲካ በመንዛት በጎንደር እና አካባቢው በሚገኙ የትግራይ ተወላጆች የጥፋት እጃቸውን በመሰንዘር በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ከፍተኛ አደጋ አድርሷል፡፡ ይህ ሴራ ደግሞ የብዙ ሀይሎች እጅ እንዳለበት ለማንም ግልጽ ቢሆንም አንዱ ግን የእርስዎ አቶ ፃድቃን ገ/ብረተንሣይ አትነሣም ወይ ግዜው አሁን አይደለም ወይ ያዘለ መልእክት ያለው ፁሑፍ እና ቀረርቶ ነው፡፡ ለአብነት በረጅምና መራራ ትግል የደርግ ስርዓት መፈራረስ የጀመረው በመጨረሻም የደርግን ስርዓት ሲያገለግል የነበረውን የኢትዮጵያ ሰራዊት በአስር ሺዎች እጁን ሲሰጥ የነበረው እኛ የትግራይ ታጋዮች የተለየ ጀግንነት ስለነበረን እነሱ ደግሞ ፈሪዎች ስለነበሩ አይደለም፤ እነሱም ጀግኖች ነበሩ፣ ግን የቆሙለት ዓላማ ከዳቸው፣ የቆሙለትን ፖለቲካዊ ዓላማ አምነው መከላከል ተሳናቸው፡፡ ውስጣዊ ጥንካሬያቸው በየግላቸው መፍረስ ጀመረ፡፡ ሌሎችን ጨቁኖ በመግዛቱ ላይ በተመሠረተ ፖለቲካዊ ዓላማና በብልሹ አስተዳደር የሚመራ ሰራዊት ደግሞ ውስጣዊ ጥንካሬ ይኖረዋል ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡ ነገር ግን ይህ ፁሑፍ ፍፁም እውነትነት የሌለው ለረጅም ዘመናት ለሕዝብ ክብርና ልእናሉ ሲሉ 1 ታጋይ ለ25 የደርግ ሠራዊት እየተዋጉ መራራ መስዋእትነ የከፈሉ የሕዝብ ልጆች ክብር የሚያንኳስስና የሚያሣንስ በሕዝብ ልጆች ደም የተሰራውና የተፃፈው ደማቅ ታሪክ የሚደመስስ ርካሽ የሆነ የትምክሕተኞች፤ የጠባቦችና የአረና የፖለቲካ ኘሮፖጋንዳና ከኒዮሊበራሊስት አራማጆች ገንዘብ መሰብሰቢያ ከመሆን የዘለለ ፋይዳ የለውም፡፡
አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት … እንዳይሆን ነገሩ!
ታጋይ ካህሳይ ቃሉ የተባሉት ጽሀፊ የትግራይ ህዝብና መሪ ድርጅቱ ህወሓት ላይ ያነጣጠረ መሰረተ ቢስ ውንጀላ እስከ መቸ? በሚል ርዕስ እኔ በአይጋ ፎረምና በትግራይ ኦን ላይን ድረ-ገጾች ላይ ላወጣኋቸው ተከታታይ ጽሁፎች ምላሽ ለመስጠት የሞከሩ ሲሆን ይህንኑ ጽሁፍ በአይጋፎረም፣ በትግራይ ኦን ላይንና በቅርቡ ደግሞ በሆርን አፌይርስ ድረ-ገጽ ላይ ፖስት አድርገውት ተመለከትሁ፡፡
የሚገርመው ነገር እኒህ ሰው በዚሁ ጽሁፋቸው ላይ ምንም አይነት ለውጥ ሳያደርጉበትና የተለየ ሀሳብም ሳይጨምሩበት በተመሳሳይ ጽሁፍ እነዚህን ሶስት ማህበራዊ የመገናኛ አውታሮች ነገር ግን ለአንድ አላማ የቆሙ ለሚመስሉ ተቋማት ልከው ሀሳባቸው በበርካታ የድረ-ገጾቹ ተደራሲያን እንዲደርስ ለማድረግ የመቻላቸው ሚስጥር ምን እንደሆነ በቅጡ ባይገባኝም ተደራሲያቸው ግን በአብዛኛው ያው ተመሳሳይ የህብረተሰብ ክፍል መሆኑን የዘነጉት ይመስላል፡፡
ይህን ያልሁበት ዋነኛ ምክንያት እኔ ይህን ጽሁፍ ጨምሮ ቀደም ሲል አንድ ሁለት ጽሁፎችን ለአይጋ ፎረምና ለሆርን አፌርስ ድረ-ገጾች ብልክም የድረ-ገጾቹ አርታኢዎች ይኸ ምላሽ እኛን ስለማይመለከት ለትግራይ ኦን ላይን ድረ-ገጽ ቢላክ መልካም ነው በማለት መልሰውልኝ እንደ ነበር አስታውሳለሁ፡፡ ሆኖም ለታጋይ ካሳይና መሰሎቹ ሲሆን ግን የዚህ አይነቱ መመሪያ እንደማይሰራ አረጋግጫለሁ፣ ይሁን ምን ይደረጋል የተገኘውን ጠባብ መድረክም ቢሆን ተጠቅሞ መልክትን ለማስተላለፍ መሞከሩ በራሱ ጥሩ አማራጭ ይሆናልና ደጋግሞ በሮችን ማንኳኳቱ ተገቢ ነው ብየ ስለማምን በተባለው መልኩ ጽሁፌን ለማቅረብ ተገድጃለሁ፡፡
ይህም ሆኖ ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርሁት ለታጋይ ካህሳይ ቃሉና መሰሎቻቸው ግን የእነዚህ ድረ-ገጾች በር በሰፊው ብርግድ ብሎ የተከፈተላቸው እስኪመስል ድረስ በሶስቱም ድረ-ገጾች ላይ ያለ ምንም ማንገራገር ጽሁፋቸው ሲላክ አብይ ርዕሰ ጉዳይ ሆኖ እንዲታይ እስከ ማድረግ ይደረሳል፡፡
ይኸ የሚሆንበት ዋነኛው ምክንያት ደግሞ ግልጽና ግልጽ ነው፣ ህወሀትንና የትግይን ህዝብ የሚያሞግስና የሚከላከል ጽሁፍ ያውም ታጋይ ነኝ በሚል የትግራይ ተወላጅ የተዘጋጀ የመልስ ምት ስለሆነ ነው፡፡ የሆነ ሆኖ ታጋይ ካህሳይ በመንደርደሪያነት ያቀረቡትን ሀሳብ ሳነብ በተወሰነም ቢሆን ሚዛናዊ የሆነ አቀራረብን ሊከተሉ ይችሉ ይሆናል ብየ ተስፋ አድርጌ ነበርና ንባቤን ቀጠልሁ፣ ሆኖም ያሰብሁት ነገር ትንሽ ወረድ እያለ ሲሄድ መልኩን ቀይሮ “ነብር ዥንጉርጉርነቱን” መቼም ቢሆን ሊቀይር እንደማይችል ለማረጋገጥ ቻልሁ፡፡ የእኔ ጽሁፎች ምን ያህል እንዳበሳጩዋቸውና ከአንጀታቸው ድረስ ዘልቀው እንዳንገበገቧቸው የተገነዘብሁት ከሁለት አመት በፊት በአይጋ ፎረም ድረ-ገጽ ላይ ያወጣሁትን ጽሁፍ ጠቅሰው በመጀመራቸውም ብቻ ሳየሆን የአቶ ተኮላን ስም ከመጥቀስ የዘለለ ቦታ ሳይሰጡ የእኔ ጽሁፍ ላይ በማነጣጠራቸው ነው፡፡
ያም ሆነ ይህ ስለ ሽግግሩ ወቅት ፖለቲካዊ ሁኔታ ታጋይ ካህሳይ የሚያወቁትን ያህል ምናልባትም ከእሳቸው በተሻለ ሁኔታ እኔም በቦታው ስለነበርሁ ከእሳቸው ባልተናነሰ መልኩ አሊያም ጠለቅ ባለ ሁኔታ እውቀቱ እንዳለኝ ላረጋግጥላቸው እወዳለሁ፣ ይሁን እንጂ እውነታው ይኸ ሆኖ ሳለ ሀቁን በመሸፋፈን መጀመሩ በራሱ ተገቢ ካለመሆኑም በላይ ህወሀትንና የትግራይ ህዝብን ጨምሮ ለማንም አይጠቅምም የሚል እምነት አለኝ፡፡
እንዳውም ታጋይ ካህሳየ ዘንግተውት ካልሆነ በስተቀር እኔ እስከማውቀው ድረስ ደርግ ከመውደቁ በፊት እኮ ኢሰፓ ጭምር እንደ ፓርቲ በሚሳተፍበት የሽግግር መንግስት እንዲመሰረት ኢህአዴግ ጥሪ አቅርቦ ነበር፡፡ ከዚህ በላይ ስለሽግግሩ ወቅትም ሆነ ስለ ኢህአዴግ ጥንካሬና ድክመት ማውራት አልፈልግም፣ ይበልጥ ማወቅ የሚፈልግ ሰው ካለ ግን እንደ ታጋይ ካህሳይ ሁሉ ወደ አይጋ ፎረም ድረ-ገጽ ጎራ ብሎ ዝርዝሩን ይመልከት፡፡
ሌላው ታጋይ ካህሳይም ሆኑ መሰሎቻቸው ከተሳሳተ አረዳደድ የመነሳታቸው ሁኔታ ቀጥሎ ያለውን ሀሳብ በድፍረት እንዲጽፉ ያደረጋቸው መሆኑ ነው፡፡ የታጋይ ካህሳይ የተሳሳተ ድምዳሜ የሚከተለውን ይመስላል፣ “የአቶ እውነቱ ሶስቱም ፅሁፎቻቸው ተመሳሳይ ናቸው በሳቸው እምነት ትግርኛ ተናጋሪ የሚባል ሁሉ ለኢትዮጵያ የማይጠቅምና የወረደ እንደሆነ አማርኛ ተናጋሪ እንኳ ቢሆን ትግራዋይ የሚለውን እውነት የሚደግፍ ከሆነ ሰይጣን እንደሆነ ለማሳየት ሲባል ሰላምወርቅ የተባሉ ፀሃፊ ያስቀመጧቸው ሂሶች ከማስተባበል ይልቅ ፀሃፊው የትግራይ ተወላጅ ስለመሆናቸው ለማሳመን ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም”፡፡
ሲሉ ምኑን ከምን እንዳገናኙት በማይታወቅ አቀራረብ በውስጣቸው ተጠራቅሞ የነበረውን የጥላቻ ስሜት አጋጣሚውን በመጠቀም እንደወረደ ዝርግፍ አደረጉት፡፡ የሚገርመው ነገር እኔ በየትኛውም ጽሁፌ ላይ የትግራይን ህዝብና ህወሀትን ወይም አንዳንድ የትግራይ ተወላጅ ነን እያሉ የተሳሳተና የጥላቻ ስሜትን የሚዘራ ሀሳብ በጽሁፍ መልክ የሚያቀርቡ ግለሰቦችን በአንድ አይነት እይታ ፈርጃቸውም ሆነ ወቅሻቸው አላውቅም፡፡ ምክንያቱም በአንድ በኩል አብዛኛው የትግራይ ህዝብ እንደማንኛውም የኢትዮጵያ ብሔር-ብሔረሰብ ህዝብ አሁንም ድረስ በከፋ ድህነት ውስጥ የሚኖር፣ በመልካም አስተዳደር እጦት በእጅጉ የሚንገላታና ዴሞክራሲያዊ መብቱ የተገደበ እንሆነ ጠንቅቄ የማውቅ ሲሆን በሌላ በኩል እነዚህ ወገኖች በፍጹም የተለያዩ እንደሆኑ በጽናት አምናለሁና ነው፡፡
ይህም ሆኖ በስመ የትግራይ ተወላጅነትና የህወሀት አባልነት የትግራይን ህዝብም ሆነ የህወሀትን አስተዋጽኦ ከሚገባው በላይ አግዝፈው ሌላው የኢትዮጵያ ብሔር-ብሔረሰብ ህዝብ የደርግን ሰርአት በማስወገድም ሆነ አሁን በመመዝገብ ላይ የሚገኘውን ሰለaላመaማወwiዊ ሁኔታና ኢኮኖሚያዊ ዕድት በማምጣት ረገድ የነበረውን ፖለቲካዊና ወታደራዊ ሚና በእጅጉ አሳንሰው የሚጽፉትንና መሬት ላይ የሌለ ትርክት በመፍጠር በህዝቦች መካከል ያልተፈለገ የተቀናቃኝነትና የጥላቻ ስሜት እንዲፈጠር ለማድረግ የሚጥሩትን ከማጋለጥ ወደ ኋላ እንደማልል ሊገነዘቡ ይገባል፡፡
ታዲያ ታጋይ ካህሳይ ትግርኛ ተናጋሪ የሚባል ሁሉ ለኢትዮጵያ የማይጠቅምና የወረደ ነው ብሎ አቶ እውነቱ ጻፈ ለማለት ምን አነሳሳቸው? ይህንንም መሰረተ ቢስ የውንጀላ ሀሳባቸውን ሲያጠናክሩ አቶ እውነቱ አንድን ብሄር (ያውም የትግራይን ህዝብ ማለታቸው ነው) የሚያንቋሽሽ ፅሁፍ ይዘው ወጡ በማለትም በጭፍኑ ለመወንጀል ይሞክራሉ:: እረ በህግ አምላክ ጓድ ካህሳይ! አሁንም ደግሜ ለታጋይ ካህሳይም ሆነ ለመሰሎቻቸው ላረጋግጥ የምፈለገው ነገር ቢኖር ከእሳቸው ባልተናነሰ ለትግራይ ህዝብ ከልብ የመነጨ ክብርና ምስጋና ያለኝ መሆኑን ነው፡፡
ታጋይ ካህሳይ እንደ እርሰዎ መጠሪያየና እንደመነገጃም ጭምር አድርጌ ባልጠቀምበትም እኔም በትግሉ ሒደት ውስጥ ያለፍሁበት ህይወት ይልቁንም ከህወሀት ታጋዮች ጋር መልካም የሚባል ግንኙነት ፈጥሬ የቆየሁ አሁንም ጭምር ያለሁ ነኝና አንድን ህዝብ እንደ ህዝብ ያውም ለዚህ ሰላምና ልማት መምጣት ከፍተኛ የሆነ መስዋዕትነት የከፈለውን የትግራይ ህዝብ የምሰድብበት ወይም የማንቋሽሽበት ያን ያህል የወረደ የሞራል ደረጃ ላይ አልደረስሁም፡፡
ይህንን ሀቅ ለማረጋገጥ ከፈለጉ ጽሁፎቼን መለስ ብለው ቢያዩዋቸው አንድም ቦታ ላይ የትግራይን ህዝብ እንደ ህዝብ በጅምላ አልወቀስሁም አሊያም ሁሉንም የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ የህብረተሰብ ክፍል እርሰዎ ባሉት ደረጃ አላንቋሸሽሁም፡፡ ይልቁንም ለይቼ በትግራይ ህዝብ ስም ለመነገድ የሚሞክሩትን ግለሰቦች መጥፎ ሀሳብ ነው ለማጋለጥ የሞከርሁት፡፡ ችግሩ ያለው የሚመስለኝ በታጋይ ካህሳይም ሆኑ መሰሎቻቸው አካባቢ ህወሀትንና የትግራይን ህዝብ አንድና ያው አድርጎ የመመልከት ሁኔታ ላይ የሚያነጣጥር ይመስለኛል፣ በመሆኑም ህወሀት ሲወቀስ ወይም ሂስ ሲደረግ የትግራይ ህዝብ በጅምላ የተወቀሰ አሊያም አላግባበ ሂስ የተደረገ ይመስላቸዋል፡፡
ለማንኛውም ችግሩ የት ላይ እንዳለ ለማወቅ ከፈለጉ የእነዚህን ግለሰቦች ፌስ ቡክ ገጽ ትተን በአንዳንድ አክራሪ የትግራይ ተወላጆች አማካኝነት አይጋ ፎረምና ትግራይ ኦን ላይን ድረ-ገጾች ላይ የአማራ ክልልንና መሪ ድርጅቱን አስመልክቶ ባለፈው አመት ያወጧቸውን ጽሁፎች ብቻ ለማንበብ ጥረት ያድርጉ፡፡