ነጋድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ ስለኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታዎች አሁንስ ምን ይሉ ነበር ይሆን?

(ሕሉፍ ሓጎስ [email protected])

መግቢያ

‹‹ታሪክን መማር ለሁሉ ሰው ይበጃል፤ ለቤተ መንግስት መኰንን ግን የግድ ያስፈለጋል››– ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ

በመጀመርያ የነጋድራስ ገብረ ሕወይት ባይከዳኝን ሥራዎች ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ጥረት ላደረጉ ለልጅ ልጃቸው ለወ/ሮ ዓይናለም አሸብር ገብረሕይወትና የሀገራችን ምሁራን በተለይም የታሪክ ምሁር ኤሜሪተስ ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ እና የስነ-ምጣኔ ምሁር ለኢኮኖሚስቱ ዶ/ር ዓለማየሁ ገዳ ታላቅ ምስጋናዮንና አክብሮቴን ለመግለፅ እወዳለሁ፡፡

በመቀጠልም የነጋድራስ ገበረ ሕይወት የግል ታሪክና ስራዎቻቸው ለመግለፅ የሚያስችል ብቁ ዕዉቀትና አንደበት ባይኖረኝም ከጥቂት ማጣቀሻዎች እንደተረዳሁት ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ የሃገራችን ዘመናዊ ትምህርት ከተቋደሱት የመጀመሪያዎቹ ወጣቶች አንዱ እንደሆኑና በራሳቸው ጥረት አውስትርያ በመሄድ የሕክምና ትምህርት ተከታትለው፣ የምዕራባውያንን የፖለቲካል ኢኮኖሚ ፅንሰ-ሀሳብም ቀምሰው ወደ ሃገራቸው የተመለሱ ብርቅየ፣ እጅግ በጣም ብልህ፣ ስለሃገርና ስለ ህዝብ በጥልቀት የሚያስቡና የሚቆረቆሩ አርቆ አሳቢ ወጣት የሀገራችን ምሁር እንደነበሩ ሳልጠቅስ ማለፍ አልፈልግም፡፡

የዚህ አጭር ፅሁፍ ዋና ዓላማ ደግሞ ሊቁ በወቅቱ የተገነዘቡት የሃገራችን ኋላ ቀርነትና ድህነትን እያብከነከናቸው ለውጥ ለማምጣት በ20ኛው ክፍለ ዘመን የመጀመርያ ሩብ ዓመት ከፃፍዋቸው ዘመን ተሻጋሪ ፅሁፎች ማለትም ከ‹‹አጤ ምኒልክና ኢትዮጵያ›› እና ‹‹መንግስትና የህዝብ አሰተዳደር›› የተረደኋቸው ዋና ዋና ነጥቦች ከሃገራችን ወቅታዊ ሁኔታዎች ለማስተጋባት ነው፡፡

ይህ አጭር ፅሁፍ ለመፃፍ ያነሳሳኝ ደግሞ ሊቁ እንዳሉት ‹‹ታሪክን መማር ለሁሉ ሰው ይበጃል፤ ለቤተ መንግስት መኰንን ግን የግድ ያስፈለጋል›› በዮ ስለማምን ነው፡፡

ነጋድራስ ገብረ ሕይወት እንዳሉት ጠቃሚ የሚሆኖው እውነተኛ ታሪክ መማር ሲሆን እውነተኛ ታሪክን መፃፍ ግን ቀላል አይደለም፤ ሶስት የእግዚአብሔር ስጦታዎች ያሰፈልጉናልና፡፡ እነዚህም፡- ተመልካች ልቦና የተደረገውን ለማስተዋል ፣ የማያዳላ አእምሮ በተደረገው ለመፍረድ እና የጠራ የቋንቋ አገባብ የተመለከቱትንና የፈረዱትን ለማስታወቅ ናቸው፡፡ እኔም ከላይ የተጠቀሱት ስጦታዎች ያካፍለኝ በማለት ፅሁፌን እንደሚከተለው አጠር ባለ መልኩ ለማስታወቅ እሞክራለሁ፡፡

Photo - Negadras Gebrehiwot Baykedagn
Photo – Negadras Gebrehiwot Baykedagn

ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ስለ የኢትዮጵያ ዕድገትና ወቅታዊ ሁኔታዎች አሁንስ ምን ይሉ ነበር ይሆን?

በነጋድራስ ገብረ ሕይወት አስተሳሰብ የአንድን ሃገር አጠቃላይ ዕድገት የሚያቀጭጬ ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉ፡፡ እነሱም ግጭት ወይም ጦርነት እና ያልተመጣጠነ የውጪ ንግድ ናቸው፡፡

ያልተመጣጠነ የውጪ ንግድ የሚለው ፅንሰ-ሃሳብ የሚወክለው የስነ-ምጣኔ ሀብት ምሁሩ ዶ/ር ዓለማየሁ ገዳ በደራሲው መፅሃፍ መግብያ ላይ እንዳስቀመጡት በአሁኑ የኢኮኖሚ ማጣቀሻዎች ‹‹የፕሬብሽ-ሲንገር መላምት ወይም አስተሳሰብ›› ተብሎ የሚታወቅ ሲሆን ፅንሰ-ሃሳቡ በዕድገታቸው ተመጣጣኝ ባልሆኑ ሁለት አገሮች የንግድ ልውውጥ ሲያደርጉ ያላደገው አገር እንደሚጎዳና ለዚህም ዋና ምክንያት ያላደገው አገር የሚነግደው ምርት ብዙ ዕውቀት የሌለበት ጥሬ ዕቃ በመሆኑና የሰለጠነ የመሰረተ ልማት አገልግሎት ባለመኖሩ የምርቱ ወጪ ከፍተኛ ስለሆነና የያደገው አገር ዕቃ ይዘት ደግሞ በተቃራኒው በመሆኑ ነው፡፡

ነጋድራስ ገብረ ሕይወት የመጀመሪያውና ዋነኛው የዕድገት ማነቆ ያሉት ማለትም ‹‹ግጭት ወይም ጦርነት›› ደግሞ እንደሚከተለው ይገልፁታል፡፡

ለነጋድራስ ገብረ ሕይወት የ ‹‹ግጭት ወይም ጦርነት›› ዋነኛ መነሻ ያአንዳንድ ግለሰቦች ሳይደክሙ (በዘመናችን ቋንቋ ኪራይ ሰብሳቢዎች ለማለት ይመስለኛል) የሰውን ላብ የመሻት ፍላጎት ነው፡፡ ከሃገራችን ተጨባጭ ሁኔታ በማያያዝ ሲተነትኑት ደግሞ በዘመናቸው ቋንቋ የአንዳንድ‹‹ነገዶች›› ወይም በአሁኑ ቋንቋ ብሄረሰቦች ጠበቃዎች ነን ባዮች አንዱ ብሄረሰብ ባንዱ ላይ እንዲነሳ በተለያየ መንገድ እንደሚቀሰቅሱ፣ ጦርነት ሲነሳ ብሄሮቹ እንደሚተላለቁና መሪዎች ነን ባዮች ግን ወደጦርነት ቦታ ድርሽ እንደማይሉ እንዲሁም የግጭቱ ወይም የጦርነቱ ተጠቃሚዎች ደግሞ ዘራፊዎቹ መሆናቸው በሠላ ብዕራቸው አስፍረውታል፡፡

ግጭቱ ወይም ጦርነቱ ቶሎ ብሎ እንዳይሰክን ዋነኛ ምክንያት የሚሆኑት ደግሞ ገበሬው ተበታትኖ ስለሚኖርና እርስ በእርሱ የሚገናኝበት የመሰረተ ልማት አውታሮች እና የተማረ የሰው ሀይል እጥረት ሲኖር (አሁን ግን በኢትዮጵያ የተማረ የሰው ሀይል እጥረት ሳይሆን የሚያመዛዝኑ ምሁራን እጥረት ነው የሚሉ ይመስለኛል) ነው ይሉናል ፡፡ ሰለሆነም የጦርነቱ ዋናው ተጠቂ የሚሆነው የኢኮኖሚ ዘርፍ ደግሞ እርሻ ሲሆን ጦርነቱ ከቀጠለ የእርሻ ልማት ከሥሩ ጠፍቶ የልጅ ልጆቻችን ወደ ዉጭ አገር እንደሚሰደዱ ይተነብያሉ፡፡

ይህ በእንዲህ እያለ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት የኢትዮጵያን የሰላም ሁኔታዋና ዕጣ ፋንታዋ እያብከነከናቸው እንደሚከተለው ሲሉ አትተውልናል (አሁንም መድረክ ላይ ወጥተው እስኪ ተናገሩ ቢባሉ ‹‹የድሮ ፅሁፌን ነው ደግሜ የማሳውቃቹ›› የሚሉን እየመሰለኝ)፡-

የኛ የኢትዮጵያዊያን ያለፈው ታሪክ እጅግ ያሳዝናል፡፡ ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት ጀምሮ እስካሁን ድረስ ፍጹም የሆነ ሰላም አግኝተን አናውቅምና፡፡ የተወደደች አገራችን፣ ዘወትር በጠላቶች ተከባ ስትኖር ነበረች፤ ትኖራለችም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ቸርነት የውጭ ጠላት ከዚህ በፊት አላዋረደንም፡፡ አንድነትም ስንሆን ምንም የሚደፍረን እንደሌለ ታሪክ ይመሰክራል፡፡ ዘወትርም በስምምና በፍቅር አድረን ብንሆን እስከ ዛሬ ድረስ ብዙውን ትልልቅ ነገር መፈጸም እንችል እንደነበር ጥርጥር የለውም፡፡ እግዚአብሔር ብዙ በረከት ሰጥቶናልና፡፡ ትምሕርትን በቶሎ መቀበል የሚችል ልቦናና የጦረኛን ባሕሪ፣ ማለፍያና ሀብታም አገርንም፡፡ ካለመስማማታችን የተነሳ ግን ሌሎች ሕዝቦች በአእምሮና በጥበብ እየበረቱ ሲሄዱ እኛ ወደ ኋላ ቀረን፡፡ እንደ አረመኖች እስኪቆጥሩን ድረስ፡፡ የዱሮውም ያሁንም ኑሮዋችን እጅግ ያሳዝናል፡፡ በመላው ዓለም ላይ ሰላም ሲሰፋ አእምሮም ስትበራ እኛ በጨለማ እንኖራለን፡፡ እርስ በርሳችን መጠራጠርንም አልተውነም፡፡ ሕዝቦቹም ሁሉ እርስ በርሳቸው በፍቅር ተቃቅፈው ስለ ልማታቸው ባንድነት ሁነው ሲደክሙ እኛ አንድ ዘርና ወንድማማች መሆናችንን ገና አልተገለጸልንም፡፡ እርስ በርሳችን መፋጀትም እስከ ዛሬ ድረስ ጀግንነት ይመስለናል፡፡ ስለዚህም እግዚአብሄር ለብርታት የሚሆነውን ስጥወታ ሁሉ ሰጥቶን ሳለ ባለቤቶቹ ሰነፍን፡፡ ሌሎቹም ነገሥታት እንደ ሰነፎች ይቆጥሩናል፡ ይንቁናልም (ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ሥራዎች፣ 2002 ዓ.ም፣ ገፅ19-20)፡፡

ይህን ካሉ በኋላ ‹‹እኛ ኢትዮጵያዊያን የሰውም ክብረቱ ስራና አእምሮ መሆኑን ገና አላወቅንም›› ይሉናል፡፡ በዙሪያችን ያሉት አገሮች ብዙዎቹ ብንመለከት አእምሮ ያላቸው ሕዝቦች በብዙ ትጋት ሲያለምዋቸው እናያለን እንዲሁም ‹‹አእምሮ በአእምሮ ካልሆነ በቀር በሌላ አትታገድም›› ይሉናል ወጣት ምሁሩ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀብቱና ዕውቀቱ ማደግ ሲጀምር ግን ዘውትር በሃገሩ አዲስ ሁከትና ጦርነት ይነሳል፡፡ በዚህም ምክንያት ሕዝቡ አቅንቶት የነበረውን የኢትዮጵያ ደንና መሬት እየተወ ሁከትንና ጦርነትን በተነሳ ቁጥር ለመመከት እንዲመቸው ሲል ድሮ ወደ ነበረበት ወደ መጥፎው መሬት ይመልሰዋል፡፡ ስለዚህ ‹‹በድንቁርናው ለሚቀመጥ ሕዝብ ወዮለት ዉሉ አድሮ ይደመሰሳልና›› ይሉናል፡፡

በተጨማሪም እኛ ኢትዮጵያውያን ከፈረንጆች ብንተዋወቅም ብዙም እንደማንጠቀምላቸው በመግለፅ መንግስታችን እንዳትጠፋ ስጋታቸውም በበሳል ብዕራቸው አስፍረውልናል፡፡ ለኢትዮጵያዊ ሰው እንዲህ ብለው ቢነግሩት ግን እንዲህ ሲል ይመልሳል ‹‹እግዚአብሔር አገራችንን አሳልፎ ለባእድ አይሰጣትም›› ይሉናል፡፡ እግዚአብሔርን የመንግስታችን አርነት እንዳትጠፋ ብዙ ጊዜ እንደከለከለልን በመጥቀስ ‹‹እኛ ግን ለቸርነቱ የተገባን ሕዝብ መሆናችንን አላሳየንምና በዚህ ምክንያትም ውሎ አድሮ እንዳይፈርድብን እንጠንቀቅ ፤ እንትጋም›› ይሉናል፡፡

ልብ ብለን ካሰተዋልን ደግሞ ከላይ የተባለውን አሁንም እንዳልቀረ ለሁላችን ግልፅ ይመስለኛል፡፡ ዲ/ን ዳንኤል ክብረትም በቅርብ ግዜ ‹‹ሕዝብን የሚያዳምጥ መንግሥት፤መንግሥትን የሚያዳምጥ ሕዝብ!›› በምትለው አጭር ፅሁፋ ያስነበበን ወጣት ምሁሩ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ያስነበቡን ጋር ተመሳሳይ ይመስለኛል፡፡ የዲ/ን ዳንኤል ክብረት ዋና ሃሳቡ እንደማመጥ ሲሆን እንዲህ ሲል ይገልፀዋል ፡-

…ለሕዝብ የመናገር ነጻነት ብቻውን ምንም አያደርግለትም፡፡ የመደመጥ መብት ከሌለው በቀር፡፡ ሰሚ ከሌለው እንኳን ሕዝብ ፈጣሪ አይናገርም፡፡ ቢናገር ጥቅም የለውም፡፡ ለዚህም ነው ሊቃዉንቱ እንደሚነግሩን፤ መላእክት እስኪፈጠሩ ድረስ ፈጣሪ ፍጥረታትን በአርምሞ ብቻ የፈጠረው፡፡ ለምን? ቢሉ ሰሚ ባይኖር መናገር ምን ያደርጋል ብሎ፡፡ መላእክት ከተፈጠሩ በኋላ ግን ‹ብርሃን ይሁን› ብሎ ሲናገር እንሰማዋለን፡፡ አሁን ሰሚ ተገኝቷልና መናገር ዋጋ አለው፡፡ … ወንዝ በድንጋይ ላይ ሲያልፍ ይጮኻል ግን ድንጋዩ አይሰማውም፡፡ ድንጋዩም ውኃው በላዩ ላይ ሲያርፍ ይጮኻል ፤ ግን ወንዙ አይሰማውም፡፡ ሕዝቡን የማያዳምጥ መንግሥትና እርሱ የፈጠረው መንግስት የማያዳምጥ ሕዝብ እንዲህ ናቸው፡፡

በአጠቃላይ ስናየው ደግሞ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ አንድን ሀገር ለማልማት ቆርጦ የተነሳ መንግስትና ሕዝብ ራሱን እንዲችል፤ ድምፁን እንዲያሰማና ህዝቡንና ሀገሩን እንዲለማ ትምህርትን ቅድሚያ መስጠት እንዳለበት እንዲሁም ዓለም አቀፋዊ ተሞክሮ በመቀመር የራስ የልማት ጎዳና መቀየስ እንዳለበት በአፅእኖት ይመክሩናል፡፡ በዚህም መሰረት ወጣት ምሁሩ በወቅቱ ለነበሩት የሃገራችን መሪ ያጤ ምኒልክ አልጋ ወራሽ እያሱን ‹‹ ከቡር ወልዑል ያጤ ምኒልክ አልጋ ወራሽ የጃፓን መንግሥት እንዴት እንዳደረገ አስመርምረው መንገዱን እንዲከተሉ ተስፋ እናድርግ››ሲሉ ምክረ ሃሳባቸው አቅርበዋል፡፡

በአግባቡ መርምረን ለአገራችን የሚበጀን የልማት ጎዳና ከነደፍን የሚደፍረን እንደሌለ ፤ያላደረግን እንደሆነ ግን ሃገራችን እንደምትፈራርስና ወደ ባርነትም እንደምትገባ ደግሞ አበክረው ይገልፃሉ፡፡ በወቅታችንም በደንብ አስተውለን ካነበብን ታሪክ የሚነግረንም ይሁን በዘመናችንም አሉ የተባሉ የስነ-ምጣኔ ሀብት (የኢኮኖሚክስ) ማጣቀሻዎች በተለይም በሀብትና የሀብት ክፍፍል ላይ ያተኮሩ ፅሁፎች ስናነብ የጃፓን የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች የኢኮኖሚ ዕድገትዋን ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ያስኬዱና የተረጋጋች አገር እንድትሆን እንደረዱዋት እንረዳለን፡፡

ይህ ካልኩ በኋላ ‹‹ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ስለ የኢትዮጵያ ዕድገትና ወቅታዊ ሁኔታዎች አሁንስ ምን ይሉ ነበር ይሆን?›› የሚለውን ጥያቄዬን ትክክለኛው መልስ እሳቸው ብቻ የሚመልሱት ቢሆንም በመግብያዬ የገለፅኳቸው ደራሲው የጠቀሱልንን ሶስት የእግዚአብሔር ስጦታዎች በጣም አስፈላጊ መሆናቸው በማስተዋል የመልሳቸው ግምት ለአንባቢው ትቼዋለው፡፡ ‹‹አንተስ ምን የሚሉ ይመስለሃል?›› ያለችሁኝ እንደሆነ ግን እንደሚከተለው አጠር አድርጌ ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡

በኔ ግምት ነጋድራስ ገብረ ሕይወትም በመጀመርያ የሀገራችን መንግስትና አብዛኞቹ የአለም አቀፍ ተቋማት እንደሚሉት ‹‹ሀገራችን ላለፉት 25 ዓመታት አመርቂ ዕድገት እንዳሳየች፣ በአለም አቀፍ ተሰሚነትዋን ከፍ እንዳደረገችና ህዝቦችዋም በጥሩ የልማት ጎዳና እየተጓዙ እንደነበሩ›› በማተት ለነኚህ ስኬቶች ዋነኛ ምንጫቸው ደግሞ ‹‹መንግስት የቀረፃቸው የልማት ፖሊሲዎች፣ ስትራተጂዎችና ዕቅዶች በአብዛኛው ድሮ እንደነ ጀርመንና ጃፓን ( አሁን ድምፄን በጥሩ ሁኔታ ተሰምቷል የሚሉ እየመሰለኝ) እና በቅርቡ እንደነ ቻይናና ሌሎች ስኬታማ የኤስያ ሃገራት የተከተሉትን የልማት ጎዳና በመመርመር ለራስዋን የሚጠቅማት የልማት ጎዳና ስላበጀች ነው›› የሚሉ ይመስለኛል፡፡

ታድያ ለምንድነው ብጥብጥና ሁከት በአገራችን አሁንም አልፎ አልፎ የሚታየው? ለምንስ ይህን ለመንግስት ሆነ ለህዝብ ትልቅ ስጋት የሆነው? ምንስ ቢደረግ ነው የሃገራችን ሰላምን አሰጠብቀን የስጋቶቻችንን ምንጭ የመፍትሄ ሃሳብ አበጅተን ወደፊት የምንራመደው? ብለን የጠየቅናቸው እንደሆነ ደግሞ የሚከተሉትን ነጥቦች የሚሉን ይመስለኛል፡-

አብዛኞቻችን ከላይ የተጠቀሱትንና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ስንመልስ በተለያዩ የሚድያ አውታሮች እንደሚስተዋለው ነጋድራስ ገብረ ሕይወትም ‹‹መነሻው በጣም እርግጠኛ አይደለሁም ፤ ነገር ግን በኔ ግምት ዋነኛ መንስኤ ሊሆን ይችላል ብዬ እምገምተው የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዕድገት ፍትሃዊነቱን በመሀል መንገድ ላይ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ተደናቅፎ እንደሚፈለገው ያህል ስላልሄደ ነው›› በማለት ይህም በስነ-ምጣኔ ሀብት ቋንቋ በቅጡ ያልተመጣጠነ የሀብት ክፍፍል ማለት ሲሆን[1] ‹‹የዚህ ችግር ሰለባ የሆኑት ሚስክን የህብረተሰቡ ክፍሎች በመጠቀም ደግሞ የሃገርን ጉዳይ ወደ ጎን በመተውና ወደ ፖለቲካ በመጠምዘዝ ሃገሪቱን እንደድሮው ያአንዳንድ ብሄረሰብ ጠበቃ ነን ባዮች አንዱ ብሄረሰብ ባንዱ ላይ እንዲነሳ በተለያዩ መንገዶች በመቀስቀስ በአቋራጭ የፖለቲካ ሥልጣን የሚመኙ ሃገር ወዳጆች ነን ባዮችና አገሪቱን ማተራመስ የሚፈልጉ የውጭ ሃይሎች በሚደረግ ኃላፊነት የጎደለው አጓጉል ድርጊቶች የሃገሪትዋ ሰላም አደጋ ላይ እየወደቀ ነው›› ብለው እንደሚያሰረዱን እገምታለው፡፡

‹‹ምንስ ቢደረግ ነው የሃገራችን ሰላምን አሰጠብቀን ስጋቶቻችን ፈትተን ወደፊት የምንራመደው?›› የሚለውን ጥያቂ ሲመልሱ ደግሞ እንደሚከተለው ብለው የሚያስረዱን ይመስለኛል፡፡

‹‹በመጀመርያ የመንግስት የልማት ፖሊሲዎችና ዕቅዶች፣ የአፈፃፀም ሪፖርቶች፣ጋዜጣዊ መግለጫዎች እና የመሳሰሉ ማጣቀሻዎች በአቅሜ መርመሬ እንደተረዳሁት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት ፈጣን ፣ ፍትሓዊ እና ሁሉን አቀፍ ነው የሚል መሆኑን ማስመር እፈልጋለሁ፡፡ በመቀጠል እኔም እንደተረዳሁትም በርግጥ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዕድገት ፈጣን ነው ፤ ፍትሓዊነቱ ደግሞ የመንግስት ስታስቲካል መረጃዎች እንደሚያሳዩትም ሆነ ዓለም አቀፍ ተቋማት እንደሚዘግቡት ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ አሉ የተባሉ የተመጣጠነ የሀብት ክፍፍል ካላቸው ሃገራት ውስጥ አንዷ ናት የሚል ሲሆን ከተለያዮ የፖለቲካ ፓርቲዎች (ገዢው ፓርቲ ሳይጨምር) ፣የመንግስት ሰራተኞች ፣ የዮኒቨርሲቲ ምሁራን እና ከአብዛኛው የከተማ ነዋሪዎች የተረዳሁት ደግሞ የሚያመዝነው በርግጥ ዕድገቱ ፈጣን ነው፤ ነገር ግን ፍትሓዊና ሁሉን አቀፍ ነው የሚያስብል ግን አይደለም›› የሚሉን ይመስለኛል፡፡

የትኛው ትክክል ይመስለዎታል ብለን ብንጠይቃቸው ደግሞ ‹‹የትኛው ነው ትክክል? የትኛው ነው ሀሰት? የሚሉት ጥያቄዎች ብዙም ጠቃሚ አይደሉምና ምን ብናደርግ ነው የመፍትሄ ሃሳብ የምናበጀው ብለን ብንነጋገር እጅግ በጣም ጠቃሚ ነው›› በማለት ጥያቄዎቻችን በሁለት ከፍለው የሚያዩት ይመስለኛል፡- በአጭር እና በመካከለኛ ግዜ፡፡

በአጭር ግዜ፡- በአጠቃላይ ‹‹የዱሮውም ያሁንም ኑሮዋችን እጅግ ያሳዝናል፡፡ በመላው ዓለም ላይ ሰላም ሲሰፋ አእምሮም ስትበራ እኛ በጨለማ እንኖራለን፡፡ እርስ በርሳችን መጠራጠርንም አልተውንም፡፡ ሕዝቦቹም ሁሉ እርስ በርሳቸው በፍቅር ተቃቅፈው ስለ ልማታቸው ባንድነት ሁነው ሲደክሙ እኛ አንድ ዘርና ወንድማማች መሆናችንን ገና አልተገለጸልንም፡፡ እርስ በርሳችን መፋጀትም እስከ ዛሬ ድረስ ጀግንነት ይመስለናል›› ብለው ድሮ የፃፉት ሃሳብ ትዝ እያላቸው፤ ‹‹የኢትዮጵያ ህዝብ ሁላችን ሰከን ብለን እናስብ፡፡ ሀብት ባይፈጠር ኑሮ ስለ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍልና የበለጠ የአኗኗር ዘይቤ አይወራም ነበር፤ እንዲሁም በየደረጃው የአስተዳደር እርከን የመልካም አስተዳደር ችግር ባይኖር ኑሮ ደግሞ አገር አቀፍ የመልካም አስተዳደር ችግር አይወራም ነበርና መንግስትም ህዝብም በጋራ ቆም፣ ሰከን ብለን እንደማመጥ››፡፡

ይህ ካሉን በኋላ ‹‹ለኔ አንዳንዶች የሚያነሱትን ስለክልሎች አወቃቀር… ብዙም አያሳስበኝም›› የሚሉ እየመሰለኝ ‹‹አሁንም በአሳሳቢ ችግር ላይ ያሉ የኢትዮጵያ ህዝቦች ቀላል አይደሉምና ወደባሰ ችግርና ደም መፋሰስ እንዳንሄድ በድጋሜ ሰከን ብለን እንደማመጥ፤ የተማርን ሰዎችም በሙያችን ያለን እውቀት በማመዛዘን እንጠቀምበት፡፡ አብዛኛው የመንግስት ሠራተኛ የአንድ ወር ደሞዙ ቢቋረጥበት፣ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው የከተማ ነዋሪዎች ለአንድ ቀን ዳቦና ደረቅ እንጀራ የሚሸጥባቸው ስቆች ቢዘጉባቸው፣ በተለያዮ መንገዶች በእርዳታ የሚተዳደሩ ወገኖች እርዳታው ቢቋረጥባቸው ምን አይነት ችግር እንደሚደርሰባቸው መገመት አያዳግትምና የየበኩላችን የሂወት ፍልስፍና መንገድ ከምንናገራቸውና ከምንሰራቸው ስራዎች ይሄዳሉ? ወይስ አይሄዱም? ብለን እንመርምር፡፡ ከመረመርን በኋላም የሚሰራጩ ፅሁፎችና ወሬዎች መርጠን እንጠቀም፤ በአሁኑ ግዜ የሚሰራጩ ፅሁፎች እጅግ በጣም ብዙ ናቸው፡፡ መረጃን መፍጠርና ማሰራጨት ቀላል ቢሆንም ለመቆጣጠር ግን በጣም ከባድ ነውና›› የሚሉን ይመስለኛል፡፡

በመቀጠል ከላይ የተጠቀሱት አካሄዶች ውጤታማ እንዲሆኑ ደግሞ መንግስት ሆነ ህዝብ ‹‹ ጥሩ የሆኑ ውጤቶች በራሳችን ጥረት ያስመዘገብናቸው ፤ ጥሩ ያልሆነ ደግሞ ሌላ አካል እንዳደረገው (ለምሳሌ፡- ግድግዳው ገጨሁት ላለማለት ግድግዳው ገጨኝ፣ እንቁላሉ ሰበርኩት ላለማለት እንቁላሉ ተሰበረብኝ፣ በአጠቃላይ ለራስ ሲጎርሱ አያሳንሱ እንደሚባለው አይነት) አድርገን የማሰብ ባህላችን በማቆም ወደ ውስጣችን እንይ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀብቱና ዕውቀቱ ማደግ ሲጀምር ዘውትር በሃገሩ አዳዲስ ሁከትና ጦርነት በመፈጠሩ አገሪትዋ ወደኋላ እንደተመለስች ታሪካችን ያትታልና ለሃገራችን ሰላምና ለህግ የበላይነት ቅድሚያ በመስጠት አሁን አገራችን እናድናት›› የሚሉን ይመስለኛል፡፡

በመካከለኛ ግዜ፡- ‹‹በርግጥ ላለፉታ 25 ዓመታት ኢኮኖሚያችን ፈጣን ለውጥ እንዳሳየ ተመስክሮለታል፡፡ ከዚህ ለውጥ ጋር ተያይዞም (ሀብት ባይፈጠር ኑሮ ስለ ሃብት ክፍፍልና የበለጠ የአኗኗር ዘይቤ አይወራምና ብለው እያሰቡ እየመሰለኝ) ህብረተሰቡ ተጨማሪ ለውጦችና ፍትሓዊ ተጠቃሚነት እየፈለገ ነው፡፡ ይህ አስተሳስብ ደግሞ የሚጠበቅና ተፈጥሯዊ ስለሆነ ሳይነሳዊ በሆነ መንገድ መንግስትና የሃገራችን ምሁራን አገራችን ፈጣን እድገት ለማምጣት የረዱዋትን የልማት ፖሊስዎችና እቅዶች (በተለይም ከ1998 ዓ.ም. በኋላ የተነደፉ) ለያንዳንዳቸው የተፅኖ ግምገማ (impact evaluation) ብናደርግላቸው፤ በዚህም መሰረት በፍጥነት የፖሊሲና የአተገባበር ማሻሻያ ብናበጀላቸው›› የሚሉን ሲሆን ‹‹መንግስትም ሆነ ገዢው ፓርቲ ደግሞ መዋቅሩ ከላይ ወደ ታች ፣ ከታች ወደ ላይ (እዚህ በደንብ ይሰራ የሚሉ እየመሰለኝ) በመገምገም መዋቅራቸው ብያጠሩ፤ መንግስት የዲሞክራሲ ምህዳሩ ብያሰፉው›› በማለት በአጭሩ ለመግለፅ የሚወዱ ይመስለኛል፡፡

ሰላምና ፍቅር ለኢትዮጵያ ሀገራችን፡፡

——–

[1] አብዛኞቻችን እንደምንለው እሳቸውም በፖሊሲው አተገባበር ላይ እንደ ጃፓን ስላልተከታተልነው ነው ይህ የተከሰተው የሚሉም ይመስለኛል፡፡

ማጣቀሻዎች፡-

* ወ/ሮ ዓይናለም አሸብር ገብረ ሕወት፡፡ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ሥራዎች፡፡ 2002 ዓ.ም፡፡ ነባር ምርጥ መጻሕፍት ሕትመት -003፡፡ አአዩ ፕሬስ

* ዲ/ን ዳንኤል ክብረት፡፡ ነሃሴ 2008 ዓ.ም፡፡ ሕዝብን የሚያዳምጥ መንግሥት፤መንግሥትን የሚያዳምጥ ሕዝብ!! 

*************

Guest Author

more recommended stories