አባይ ፀሐዬ፡- “የኦሮሞ ሕዝብ ማን እንደዘረፈው፣ ማን እንደበደለው ያውቃል” [ጽሑፍና ቪዲዮ]

በሚኒስተር ማዕረግ የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ማዕከል ዋና ዳይሬክተር አባይ ፀሐዬ ባለፉት ሳምንታት በማስተር ሰበብ በኦሮሚያ ከተከሰተው ተቃውሞ በተያያዘ አንዳንድ አካላት በትግራይና በህወሓት ላይ ያነጣጠረ ዘመቻ የሚያደርጉት አጀንዳ ለማስቀየስ ነው አሉ፡፡

የህወሓት መስራች እና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ የሆነት አባይ ፀሐዬ ይሄን የገለጹት በተለይ ለሆርን አፌይርስ በሰጡት አስተያየት ነው፡፡

ከሰሞኑ የዲያስፖራው ሚዲያ ኦ.ኤም.ኤን የእሳቸውን ድምጽ የተቆራረጠ ቅጂ በማቅረብ፣ ታህሳስ 20 በጎንደር ከተማ ታህሳስ አባይ ፀሐዬ እና የመከላከያ ሚኒስተር ሲራጅ ፈርጌሳ የመሩት ስብሰባ መካሄዱን፣ በዚያ ስብሰባ አቶ ሙክታር እና አባዱላ ገመዳ እንደተገኙበት እና አባይ ፀሐዬ በኦሮሚያ ከተከሰተው ተቃውሞ በተያያዘ ተግሳጽ ሰጡ በማለት የተሰራጨው ነበር ለአስተያየታቸው መነሻ የሆነው፡፡

አባይ ፀሐዬ የዘገባውን መሠረተ-ቢስነት የገለጹ ሲሆን፤ በማከልም የዚህ ዓይነት ወሬ የሚነዛበትን መነሻ ዘርዘር አድረገው ገልጸዋል፡፡

ደካማ ኢንተርኔት ላላቸው አንባቢያን ይረዳ ዘንድ የአባይ ፀሐዬን አስተያየት በከፊል በጽሑፍ አቅርበነዋል፡፡

[ቪዲዮውን ከታች ማየት ይችላሉ፡፡]
———

Photo - Abay Tsehaye and Daniel Berhane
Photo – Abay Tsehaye and Daniel Berhane

መጀመሪያ፡- ዘንድሮ ሆነ አምና ካች አምና ጎንደር ሄጄ አንድም ስብሰባ አላደረግሁም፤ አንድም ስብሰባ፡፡ ብቻዬንም ሆነ ከተጠቀሱት ሀላፊዎች ጋርም ሆነ አንድም ስብሰባ አላደረግሁም አልካፈልኩም፡፡ ስለዚህ የሌለ ነገር ነው ከየት እንዳመጡት አላውቅም፡፡ ቪዲዮውን በሙሉ ቢያመጡት ከነንግግሬ ከነምስሌ ጥሩ ነበር፡፡ ለምን እንደዚያ አያደርጉም? ፈጠራ ነው፡፡ ሆን ተብሎ የሚደረግ ያለ ነገር ነው፡፡ ባልሄድኩበት ቦታ ባተሳተፍኩበት ስብሰባ፡፡ እንደዚያ ዓይነት ስብሰባ መኖሩንም እኔ አላውቅም፡፡ እነአባዱላም ሄደው ከሆነ እነሲራጅም ሄደው ከሆነ አላውቅም፡፡

ከዚህ በፊትም ‹‹ወደዱም ጠሉም ልክ እናስገባቸዋለን ማስተር ፕላኑ የግድ ተግባራዊ ይሆናል ብሏል አባይ›› ተብሎ አምና በሰፊው በድረ-ገጽ በተደጋጋሚ ያቀርቡት እንደነበር ሰምቼ፤ ‹‹ምንድነው ይሄ ነገር እስኪ አንድ ነገር በል›› ብለውኝ [መልስ ሰጥቼ ነበር]፡፡ ይሄ ነገር የለም፡፡

የከተሞች አስተዳደሮች እናሰለጥን ነበረ በሀገር አቀፍ ደረጃ፡፡ እኔ ስለከተማ ፖሊሲ አስተምር ነበር ፡፡ ባጋጣሚ እዚያ ላይ ‹‹የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን እንዴት ነው እያከራከረ ነው›› የሚል ተነሳ፡፡

አንደኛ [ማስተር ፕላኑ] ጠቀሜታ አለው የትም ሀገር የሚሠራበት ነው፡፡ እነኚህ ትላልቅ ሜትሮፖሊታን የሚባሉ ከተሞች – ዋና ከተሞች እና ትላልቅ የኢንዱስትሪና የንግድ ማዕከሎች – ከአካባቢያቸው ከተሞች እና ገጠሮች ጋር ተሳስረው ነው የሚያድጉት፡፡ ትልቅ ዕድል ነው ትልቅ ከተማ አጠገብ መሆን፡፡ በአካባቢው ያሉ አነስተኛ ከተሞች፣ መካከለኛ ከተሞች እና ገጠሮችን ይዞ ነው የሚወጣው ትልቁ ከተማ፡፡ ይሄ የትም ዓለም የሚደረግ ነው፣ የትም ዓለም የሚሠራበት ነው፡፡ ስለዚህ ምንም ጉዳት የለውም፡፡

ሁለተኛ የአዲስ አበባ መስተዳድር እና የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር አቶ ኩማ የአዲስ አበባ ከንቲባ በነበረበት ግዜ አቶ ሙክታር የኦሮሚያ ፕሬዚዳንት እያለ በጋራ ያቋቋሙት ኮሚቴ ይሄ ማስተር ፕላን ሲሠራ ሲረቀቅ በባለሙያዎች የሚመራ የጋራ ኮሚቴ ከአዲስ አበባ መስተዳድር እና ከኦሮሚያ ክልል መስተዳድር በእኩል ቁጥር የተውጣጣ ኮሚቴ ነበር፡፡ ስለዚህ ከመጀመሪያው ፈቅደው ፈልገው የገቡበት ነው የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር፡፡ ማንም አላስገደዳቸው ወይም እነሱ ሳይካፈሉበት የተሠራ ማስተር ፕላን አይደለም፡፡ ይጠቅማል ብለው በጋራ ሲሠሩት የነበረ ነው፡፡ ለመስተዳድር አካላቱም ለባለሙያዎቹም በየጊዜው እየቀረበ ምክክር ይደረግበት የነበረ ነው፡፡

ሦስተኛ ማስተር ፕላኑ ሌላ ትርጉም ተሰጠው – የተሰጠው ትርጉም በኋላ እመጣበታለሁ – ግን በሆነ ምክንያት የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር ኃላፊዎች ሳይሆን በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ አንዳንድ አስተዳደሮች እና የተወሰኑ ምሁራን አካባቢ ይመስለኛል ማስተር ፕላኑን በትክክል አልተረዱትም ነበር፡፡ ስለዚህ እንዲረዱት ብለው ደግሞ በጋራ ስብሰባ አድርገው አስረድተዋቸው ነበር፡፡ በኋላ የሆነ ግርግር ተነሳ ዩኒቨርሲቲ አካባቢ፡፡ ይሄ ማስተር ፕላን የኦሮሚያን ክልል መሬት ወደ አዲስ አበባ ለማካለል ነው፣ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያለውን የኦሮሚያ ልዩ ዞን አስተዳደሩን ለማፍረስ ነው፣ አርሶ አደሩን ለማፈናቀል ነው፣ ምናምን የሚል ነገር ተወራ፡፡ የማስተር ፕላኑ ውይይት በባለሙያዎችና በሀላፊዎች ደረጃ ስለነበር፣ ቶሎ ወደህዝቡ ስላልወረደ ስለዘገየ ወርደን ቶሎ እናስረዳ ተብሎ የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር በየአካባቢው ማብራሪያ ሰጡ፡፡

ስለዚህ እኔ ያኔ ስልጠና ላይ ያልኩት ምንድን ነው፤ አብረው የሠሩት ነው -የአዲስ አበባ መስተዳድር እና የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር – ተመካክረው በጋራ እየመሩት የተሠራ ነው፡፡ አሁንም አንዳንድ ብዥታዎች ሲፈጠሩ ማብራሪያ እየሰጡ ነው፤ ስለዚህ አስረድተን እንቀጥልበታለን እያሉ ስለሆነ እስከተስማሙ ድረስ ተግባራዊ ይሆናል፤ ካልተስማሙ ነው ተግባራዊ የማይሆነው እንጂ ነው ያልኩት፡፡ ይቺ ናት፡፡ በግድም በውድም ወደዱም ጠሉም ተግባራዊ ይሆናል የሚል ቃል የለም፡፡ ቪዲዮው አለ፡፡ ምንም የለም፡፡ ስለዚህ አሁን ብለሀል አላልክም አይደለም፡፡

የጎንደሩም ጠቅላላው ያልነበርኩበት ስብሰባ ነው፡፡ እዚህም ጠቅላላ ያላልኩት ነው፡፡ ደግሞ ፓራግራፍ ወይም ሙሉ ዓረፍተ-ነገሩን እንኳን አያመጡትም ከነድምጼ፡፡ ይሄ አለ ብለው ነው ሐረግ የሚያመጡት – የኔ ድምጽ የለም፡፡ እንዴ ይሄ ያስጠይቃል ያስከስሳል፡፡ የኔ ድምጽ የሌለበት፣ ሙሉ ሙሉ ዓረፍተ-ነገሩ ወይም ሙሉ ፓራግራፉ የሌለበት፣ አንዳንዱ ደግሞ ባልነበርኩበት ቦታ ባልነበርኩበት ስብሰባም ነበረ እሱ እዛ ነው የተናገረው እየተባለ ነው ፈጠራ የሚደረግ ያለው፡፡ ይሄ አላልኩም ሀሰት ነው – የመጀመሪያ መልስ ነው፡፡

ዋናው መልሴ ግን ለምን እንደዚህ እንደሚያደርጉ ነው፡፡ እነኚህ በዚህ በሁከትና በግርግር ሊጠቀሙ የሚፈልጉ ያሉ ኃይሎች፤ እኔን እና ሌሎችን እንደዚህ መርጠው ስማቸውን ሊያጠፉ፣ ሊያጥላሉ፣ ከሕዝቡ ጋር ሊያጋጩ፣ አጀንዳውን ወደሌላ አቅጣጫ ሊወስዱት የሚፈልጉ ያሉ ምክንያታቸውን በግልጽ ሕዝብ ቢያውቀው ጥሩ ነው፡፡

አንደኛ ምክንያታቸው በዚህ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያለ የኦሮሚያ ልዩ ዞን የሚባል አካባቢ እዚያ ያሉ አንዳንድ አስተዳደሮች እና አዲስ አበባ ያሉ አንዳንድ ባለሀብቶች – የኦሮሚያ ባለሀብቶችም የሌላ ብሔር ባለሀብቶችም – በተለያየ ህገወጥ መንገድ የያዙት የወሰዱት የቸበቸቡት መሬት አለ በስፋት በብዛት፡፡ ሁለቴ ተገላብጦ የተሸጠ የተለወጠ መሬት አለ፡፡ የቸበቸበው እዚያ ያለ አስተዳደር ነው፡፡ የአዲስ አበባ አስተዳደር አይደለም፡፡ የገዙት በርካታዎቹ አየር ባየር ነጋዴዎች ናቸው – ጤናማ ነጋዴዎችም የገቡ ይኖራሉ፡፡

ማስተር ፕላኑ እነኚህን ከተሞችና ገጠሮች ከአዲስ አበባ ጋር ሊያቀናጅ በመሠረተ-ልማት በውሀ በመንገድ በባቡር በትራንስፖርት ገበያ ሊያቀናጅ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያለ የኦሮሞ ህዝብ አትክልትና ፍራፍሬ ጥራጥሬ ለስጋና ወተት የሚሆን የእንስሳት ተዋጽዖ ሊያቀርብ እንደዚህ ዓይነት ፕላን ነው ያለው፡፡ የአግሮ ኢንዱስትሪ እንዲስፋፋ፡፡ ስለዚህ በንግድ በግብይት በመሠረተ-ልማት እንዲተሳሰሩ ነው እንጂ የኦሮሚያን ቅንጣት ያህል መሬት ወደ አዲስ አበባ ለማካተት ያሰበ ማስተር ፕላን የለም፡፡

ለምን ወደዚህ ተረጎሙት፤ ይሄ ነገር ተግባራዊ ይሁን ሲባል፤ መሬቱ እንዴት ይልማ መሠረተ-ልማቱ እንዴት ይዘርጋ ኢንቨስትመንት እንዴት ይሁን ሊባል ነው፡፡ የተዘረፈ መሬት እና የዘረፈ ያስዘረፈ ያኔ ሊታወቅ ነው፡፡ ያኔ ሊገኝ ነው፡፡ ስለዚህ ከአስተዳደሩ አንዳንድ አካላት አሉ፡፡ ከነጋዴውም በዚህ መንገድ የዘረፉ አሉ፡፡ ይሄ እንዳይታወቅ ነው ማስተር ፕላኑ ሊያፈናቅላችሁ ነው፤ የኦሮሚያን ክልል መሬት ሊወስድ ነው ወደ አዲስ አበባ በሚል ተርጉመው አጣመው ወደ ግርግር እና ወደ ብዥታ የወሰዱት፡፡ አንዱ ትልቁ ምክንያታቸው ይሄ ነው፡፡ ስለዚህ ጥቂት የአስተዳደር አካላት አሉ፡፡ ይሄን መሬት መቸብቸብና መዝረፍ ላይ የተሳተፉ የተወሰኑ ነጋዴዎች አሉ፡፡ ይሄ ጉዳቸው ይሄ ገበናቸው እንዳይጋለጥ በዚህ ሂደት ነው ቀድመው የተከላከሉት፡፡ ያኔ ይሄ ነው ምክንያቱ፡፡

አሁን ደግሞ ሁለተኛ ምክንያት አለ፡፡ መንግስት በሀገር አቀፍ ደረጃ የመልካም አስተዳደር ችግር አለ፡፡ ይሄን ችግር የኔ ችግር ነው ብሎ መፍትሔ አስቀምጦ ቶሎ ይሄን ችግር እፈታለሁ ከሕዝብ ጋር ሆኜ ብሎ አወጀ፡፡ በኢሕአዴግ ጉባዔ ታወጀ፣ በየድርጅቱ ጉባዔ ታወጀ፣ በመንግስት ታወጀ፡፡ አሃ! የመልካም አስተዳደር ችግር ሊፈታ ከሆነ ሌባው መሬት የቸበቸበው ጉቦ የሰጠው ጉቦ የተቀበለው ሌላ ግፍና በደል ህዝብ ላይ ያደረሰው ህዝቡ ሊያጋልጠው ነው ሊጠየቅ ነው፡፡ ይሄ ከመምጣቱ በፊት ማስተር ፕላን ብለን ምን ብለን ግር ግር እንፍጠር የሚል ደግሞ አሁን የጨመሩት ተጨማሪ ምክንያት ነው፡፡

መሠረታዊ ምክንያቶቹ እነዚያ ሆነው፤ ከዚያ አልፎ ደግሞ የተወሰንን ግለሰቦች የተወሰንን ግለሰቦች ላይ – እኔም ሌሎችም ላይ – የሚያነጣጥሩበት ምክንያት ምንድነው፤ ይሄ ሁላ ያበላሹት የዘረፉት ያስዘረፉት ጥቂት ነጋዴዎችና ጥቂት የኦሮሚያ ልዩ ዞን አስተዳደር አካላት ናቸው ያፈናቀሉት ህዝቡን ካሣ ስጡት ተበለው ካሣውን የበሉት እነሱ ናቸው፡፡ እነሱ እንዳይጠየቁ ባንድ በኩል ማስተር ፕላን ነው ይባላል፡፡ በሌላ በኩል ህወሓት ነው ፌዴራል መንግስት ነው፡፡ የማይመለከተው እጁ የሌለበት አካል እዚህ ጉዳይ ላይ ተጠያቂ ሊያደርጉ፡፡ ተጠያቂዎቹ ሌላ ሰው ተጠያቂ እያደረጉ ነው ያሉት፡፡

ህወሓት እዚህ ውስጥ ምን አገባው? ህወሓት ፌዴራል መንግስቱን አያስተዳድረው፣ ህወሓት አዲስ አበባን አያስተዳድረው፣ ህወሓት ትግራይን ነው የሚያስተዳድር ያለው፡፡ በፌዴራል መንግስት ደግሞ እንደሁሉም ሌሎች የኢሕአዴግ አካላት ተሳታፊ ነው፡፡ ለምንድነው ህወሓት ላይ የሚነጣጠር ያለ ለምንድነው? እንዳንድ የሕወሓት አመራሮች ላይ የሚያነጣጥሩብን ያለው ለምንድነው? የትግራይ ህዝብና ሕወሓት ላይ የሚያነጣጥሩ ያለው የዘር ጥላቻ ለመቀስቀሰ ነው፡፡

የኦሮሞ ህዝብ መሬቴን የዘረፋችሁ ያስዘረፋችሁ እናንተ በጉቦ የመዘበራችሁኝ እናንተ ፍትሕ የከለከላችሁኝ የማዳምጡኝ እናንተ እያላቸው እያለ፤ እነኚህ አንዳንድ እዚህ [ልዩ] ዞን አካባቢ ያሉ ወረዳ አካባቢ ያሉ ከተማ አካባቢ ያሉ፤ አይ እኛ አይደለንም ህወሓት ነው፣ አይ እኛ አይደለንም ማስተር ፕላኑ ነው፣ አይ እኛ አይደለንም ኢህአዴግ ነው ብለው ወደ ሌላ አቅጣጫ ሊያስቱ፤ ህዝቡ ደግሞ ገብቶታል፤ እናንተ ናችሁ! ዞር በሉ ሂዱ ወይ አስተካክሉ ነው ያላቸው ወረዳ አስተዳደሮቹን ከተማ አስተዳደሮቹን ሌሎች ሀላፊዎችን፡፡ ስለዚህ ህዝቡ የሚጠይቀው ያለ የመልካም አስተዳደር ችግር ፍቱ ነው፣ የቸበቸባችሁት መሬት የዘረፋችሁት መሬት መልሱ፣ ለምንድነው እንደዚህ ያደረጋችሁት ነው፡፡: የበላችሁት ጉቦ፣ የበላችሁት ለኛ የተፈቀደ ካሣ፣ አፈናቅላችሁን በትናችሁን የቀራችሁ እናንተ ናችሁ ነው የሚል ያለው፡፡

በነሱ ላይ ያነጣጠረውን የህዝብ ጥያቄ ወደፌዴራል መንግስት፣ ወደ ህወሓት፣ ወደ አባይ ፀሐዬ፣ ወደ እገሌ ወደ እገሌ አቅጣጫ ማሳት ማወናበድ ነው የተያያዙት፡፡ እውነቱ ይሄ ነው፡፡

የኦሮሞ ሕዝብ ግን ያውቃል፡፡ ማን እንደዘረፈው፣ ማን እንደበደለው፣ ማን እንዳጉላላው፣ ማን እንደዘረፈው፣ ማን እንዳፈናቀለው ያውቃል፡፡ ይዟቸዋል አጥብቆ፡፡ አምጡ መልስ፣ ፍቱ ይሄን፣ እናንተ ናችሁ ብሏቸዋል፡፡ ወደዚያ ወደዚህ ቢያደርጉት አሁን የለም፡፡ በደንብ አስተውሏል የኦሮሚያ ህዝብ፡፡ ጥቅሙን ያውቃል መብቱን ያውቃል፡፡ የሚጎዳውንና የሚጠቅመውን ያውቃል፡፡ የኦሮሚያ ሕዝብ ነው ምሥክራችን፡፡ የኦሮሚያ ሕዝብ እየጠየቀ ያለው ጥያቄውን ይመልሱ አስተዳደሮቹ ነው እያለ ያለው፣ ፀረ-ሰላም ሀይሎቹን ደግሞ እዚህ ውስጥ አይግቡብን ነው እያለ ያለው፡፡ ምንም አያደርጉልንም፣ የሠራልንም ኢህአዴግ ነው ኦህዴድ ነው፣ ጉድለትም ያለው ደግሞ እንደወገን እንደልጆቻችን እስኪ ይቺንም አስተካክሉ እቺንም አርሙ ነው የምንላቸው ያለን ነው የሚል ያለው፡፡ እንደልጆቹ ነው ምክር የሚሰጥ ያለው፤ እርምት የሚሰጥ ያለው፡፡ ስለዚህ በዚህ መንገድ ነው መታየት ያለበት እና አጀንዳቸው የዘር ጥላቻ መቀስቀስ ነው፡፡ አጀንዳቸው እነሱ እያሉ በዳዮቹ ሌላውን በዳይ ለማስመሰል ነው፡፡
———-
ቪዲዮውን ይመልከቱ 

***************

Daniel Berhane

more recommended stories