የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ማቋረጥ ስህተትን እንደ መሳሳት ነው

ከሁለት ሳምንት በፊት “ማስተር ፕላን፦ የችግሩ መነሻ እና መድረሻ” በሚል ርዕስ አንድ ፅሁፍ አቅርቤ ነበር፡፡ የፅሁፉ ዋና መልዕክት ጠቅለል ተደርጎ ሲቀመጥ፤ “የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ፤ በኦሮሚያ ክልል እየታየ ላለው የሕዝብ ተቃውሞ እንደ ዋና መነሻ ምክንያት፣ እንዲሁም፣ የማስተር ፕላኑ መተግበር ከተማዋ ከተመሰረተችበት ግዜ ጀምሮ በዙሪያዋ ባለው የኦሮሞ አርሶ-አደር ገበሬ ላይ ያደረሰችውን ኢኮኖሚያዊ፣ አስተዳደራዊና ማህበራዊ ችግሮች እንደ ማስቀጥል ይቆጠራል” የሚል ነበር፡፡ እንሆ፣ በቀላሉ በውይይት ሊፈታ የሚችል ነገር ብዙዎችን ለሞት፣ እስርና ስቃይ ከዳረገ በኃላ የክልሉ መስተዳደር መቋረጡን በይፋ አሳውቋል፡፡

ማስተር ፕላኑ እንዲቋረጥ በመደረጉ ለህዝቡ ጥያቄ ምላሽ ተሰጥቷል። ነገር ግን ውሳኔውን ተከትሎ “እሺ… ከዚያ በኋላስ?” በሚል ስለ ሀገሪቱ ዋና ከተማ ቀጣይ እጣ-ፈንታ ብዙ ጥያቄዎች መነሳታቸው አይቀርም። ከዚህ በኋላስ፤ በ2006 ዓ.ም እንደተደረገው፣ በግዜ ርዝመት እና በኑሮ ዉጥረት ምክንያት በህዝቡ ዘንድ ያለው የተቃውሞ ድባብ እየበረደ ሲሄድ ይሄው ማስተር ፕላን ተመልሶ ሊመጣ ነው?፣ ሌላ ማስተር ፕላን ሊዘጋጅ ነው?፣ ወይስ የአዲስ አበባ ከተማ እስከ መጨረሻ ማስተር ፕላን ላይኖራት ነው?…ወዘተ የመሳሰሉት ጥያቄዎች መነሳታቸው አይቀርም።

የአዲስ አበባ መስተዳደር፣ የፌደራል መንግስት እና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በተናጠልም ሆነ በጋራ አቋማቸው የከተማዋን ልማትና እድገት በማስቀጠል መሆን አለበት። በመሰረቱ፣ ማስተር ፕላን አንድ ከተማ ወደፊት ከሚኖራት እድገትና መስፋፋት ጋር ተያይዞ የሚያስፈልጓት የመሰረተ-ልማት ግንባታዎች ተለይተው የሚቀመጡበት መሪ እቅድ ነው። እንኳን የሀገሪቱ ዋና ከተማ ቀርቶ፣ በዞንና በወረዳ ደረጃ ያሉ ትናንሽ ከተሞችን ልማት ያለ ማስተር ፕላን መምራት የማይታሰብ ነው። በተመሳሳይ፣ የአዲስ አበባ ከተማን እድገትና መስፋፋት ያለ ማስተር ፕላን ማስቀጠል አይቻልም። ስለዚህ፣ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ትግበራ ላልተወሰነ ግዜ እንዲቋረጥ ማድረግ የከተማዋ የወደፊት እድገቷ የሚያስፈልጓት የመሰረተ-ልማት አውታሮች እንዳይዘረጉ ያደርጋል። በዚህ መሰረት፣ የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ማቋረጥ የከተማዋን የወደፊት እድገት ከማቋረጥ ተለይቶ አይታይም።

እንደ የዘርፉ ባለሞያዎች ግምት፣ በቀጣይ 25 አመታት በአዲስ አበባ እና በአምስቱ የፊንፊኔ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች ነዋሪ ብዛት በድምሩ ወደ 8.1 ሚሊዮን ይደርሳል። በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ውሳኔ መሰረት እንዲቋረጥ የተደረገው ማሰተር ፕላን ደግሞ የተጠቀሰውን የህዝብ ቁጥር መጠን ለማስተናገድ የሚያስችል፣ አሁን የአዲስ አበባ ከተማ ካላት የቆዳ ሽፋን 21 እጥፍ (2,100%) የሚሆን ተጨማሪ ቦታ ያስፈልጋታል። በኦሮሚያ ክልል መሀል የምትገኝ እንደመሆኗ፣ “የአዲስ አበባ እድገት” ሲባል፣ በሌላ አነጋገር “ወደ ኦሮሚያ ክልል መስፋፋት” እንደማለት ነው።

ማንኛውም ኢትዮጲያዊ ልማትና እድገት የሌላት፣ ለውጥና መሻሻል የማይታይባት ርዕሰ ከተማ እንድትኖር የሚሻ አይመስለኝም። አዲስ አበባ እድገት እንዲቀጥል ከተማዋ ወደ ኦሮሚያ ክልል መስፋፋቷን መቀጠል አለባት። የከተማዋን እድገትና መስፋፋት ለማስቀጠል በቅድሚያ የመሰረተ-ልማት አውታሮች መገንባት አለባቸው። ተግባራዊ የሆነ የከተማ ማስተር ፕላን ከሌለ ደግሞ የመሰረተ-ልማት አውታሮች ግንባታን ማከናዎን አይቻልም። ስለዚህ፣ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ፣ አዲስ አበባ ማስተር ፕላን ሊኖራት የግድ ነው። በመሆኑም፣ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን እንዲቋረጥ ያደረገው የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ውሳኔ ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ሊሆን አይችልም።

ባለፈው ሳምንት ከሁለት የውጪ ሀገር ዜጎች ጋር ስለጉዳዩ እየተወያየን ሳል፤ “Why don’t you move the capital to Sodo?” በማለት የሰጠው የመፍትሄ ሃሳብ ለእኔ በጣም አስቂኝ ነበር። አንዳንድ ሰዎች ናይጄሪያ ዋና ከተማዋን ከሌጎስ (Lagos) ወደ አቡጃ (Abuja) ማዛወሯን እንደ ምሳሌ በመጥቀስ፣ ኢትዮጲያም ዋና ከተማዋን ወደ ወላይታ-ሶዶ፣ ደብረ-ማርቆስ፣ ወይም ሌሎች ከተሞች ብታዘዋዉር ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ይሰጣል ብለው ያስባሉ። እርግጥ ነው፣ የአዲስ አበባ ከተማ እድገት በቀጥታ ወደ ኦሮሚያ ክልል ከመስፋፋት ጋር የተያያዘ ስለሆነና እድገትና መስፋፋቱ ደግሞ ያለ ማስተር ፕላን ተግባራዊ ሊሆን ስለማይችል፣ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ለረጅም ግዜ እንዲቋረጥ ከተደረገ የሀገሪቱን ዋና ከተማ ወደ ሌላ ቦታ ማዛወር ግድ ይሆናል።

ነገር ግን፣ የኢትዮጲያ መንግስት ርዕሰ-ከተማውን ከአዲስ አበባ ወደ ሌላ ከተማ አዛወረ ማለት መንግስታዊ ተቋማቱ “የአድራሻ ለውጥ” ያደርጋሉ እንጂ የአዲስ አበባ ከተማ ከቦታዋ ተነቅላ ትሄዳለች ማለት አይደለም። የሀገሪቱ ዋና ከተማነቷ ይቅርና፣ የኦሮሚያ ክልል ከኢትዮጲያ ቢገነጠል እንኳን፣ የአዲስ አበባን እድገትና መስፋፋት ማቋረጥ አይቻልም። አንድን የዛፍ ችግኝ በመሬት ላይ ስሯን ሰድዳ ከበቀለች በኋላ በሃይል ቆርጦ በመጣል ካልሆነ በስተቀር እድገቷን ማዘግየትም ሆነ ማስቆም አይቻልም። ልክ እንደ ተክሎች፣ እድገት የከተሞች ተፈጥሯዊ ባህሪ ነው። ይህን ተፈጥሯዊ ሂደት የከተማዋን ህልውና በሃይል በማጥፋት ካልሆነ በስተቀር የአዲስ አበባን እድገትና መስፋፋት መግታት አይቻልም። አዲስ አበባ የኢትዮጲያ ማዕከል ሆና ብትቀጥል-ባትቀጥል፣ በኦሮሚያ ክልል እምብርት ላይ የበቀለች ተክል መሆኗን መቀየር አይቻልም። በመሆኑም፣ አዲስ አበባ እንዳታድግ የሚያግድ ማንኛውም ዓይነት ውሳኔ ራስን-በራስ እንደማጥፋት ይቆጠራል።

ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው፣ የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ማቋረጥ፤ በከተማዋ ለውጥና መሻሻል እንዳይኖር የሚያደርግ፣ ይህም የከተማዋ ህልውና አንዲያከትም የሚያደርግ ውሳኔ ነው። ስለዚህ፣ ለችግሩ ዘላቂ የሆነ መፍትሄ ሊሰጠው ይገባል። ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር ተያይዞ ለተነሳው የህዝብ ተቃውሞ እና ይህን ተከትሎ በክልሉ መንግስት ለተወሰደው እርምጃ ዘላቂ የሆነ መፍትሄ ለመስጠት እንዲቻል በቅድሚያ መገንዘብ ያለብን ሁለት ቁልፍ ነገሮች አሉ፣ እነሱም፡- ባለቤትነት እና ምክንያት ናቸው።

1ኛ) ባለቤትነት፡- የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ትግበራ እንዲቋረጥ የወሰነው አስተዳደራዊ አካል የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት መሆኑ ጉዳዩን በባለቤትነት መምራት የነበረበት የክልሉ መንግስት እንደሆነ ይጠቁማል። አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ፣ የአዲስ አበባ ከተማ እድገት በቀጥታ ወደ ኦሮሚያ ክልል መስፋፋት ማለት ስለሆነ፣ የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ከዝግጅት ጀምሮ እስከ ትግበራው ድረስ ያለውን የሥራ ሂደት በባለቤትነት መምራት ያለበት የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ነው። ነገር ግን፣ በሕገ-መንግስቱ አንቀፅ 49.5 መሰረት ለኦሮሚያ ክልል የሚገባውን ልዩ ጥቅም ለማስከበር የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ ባለመዘጋጀቱ፣ እንዲሁም በአዲስ አበባና በክልሉ መካከል ያሉ አስተዳደራዊ ጉዳዮች የሚመሩበት ዝርዝር የአፈፃፀም መመሪያ ባለመኖሩ ምክንያት፣ ክልሉ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ዝግጅትና ትግበራን በባለቤትነት ለመምራት ይቅርና በሕገ-መንግስቱ የተፈቀደለትን ልዩ ጥቅም እንኳን ማስከበር አልቻለም። ስለዚህ፣ ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት በቅድሚያ አስፈላጊው የሕግ-ማዕቀፎች (Legal Frameworks) እና የአፈፃፀም መመሪያዎች መዘጋጀት አለባቸው።

2ኛ) ምክንያት፡- እንደ እኔ ግምት፣ ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር ተያይዞ ከተደረጉት የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በጣም ሰፊና ከተለመደው ለየት ያለው በወሊሶ ከተማ የታየው የተቃውሞ እንቅስቃሴ ይመስለኛል። በወሊሶ ከተማ ስለነበረው የተቃውሞ እንቅስቃሴ “ወሊሶ…ከሰላም-ወደ-ሱናሚ” በሚለው ፅሁፌ በተወሰነ ደረጃ ለመዳሰስ ሞክሬያለሁ። ሐሙስ፣ ታህሳስ 02/ 2008 ዓ.ም በወሊሶ ከተማ በተካሄደው የተቃውሞ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ድርሻ የነበረው በአከባቢው ካሉ የገጠር ከተሞች የመጣው ህዝብ ነበር። እንቅስቃሴው በአምቦ ዩኒቨርሲቲ የወሊሶ ከምፓስ ተማሪዎች ከተጀመረ በኋላ፣ ከከተማው ማህብረሰብ ቀድመው እንቅስቃሴውን የተቀላቀሉት ኢጀርሳ እና ኦቢ በሚባሉት ትናንሽ የገጠር ቀበሌዎች ነዋሪዎች ናቸው። ጉዳዩን ከመጀመሪያው ጀምሮ ለተከታተለ ሰው ለነዋሪዎቹ ይበልጥ አሳሳቢ የሆነው ጉዳይ “የአዲስ አበባ ከተማ ማስተር ፕላን” ሳይሆን “የወሊሶ ከተማ ማስተር ፕላን” እንደሆነ መረዳት ቀላል ነው። ለምሳሌ፣ ከሁለት አመት በፊት “ኢጀርሳ” በሚባለው ቀበሌ በፖሊስና በአከባቢው ማህብረሰብ መካከል በተከሰተ ግጭት የአንድ ፖሊስ ህይወት ጠፍቷል። እንዲሁም፣ “አርሶ-አደርን ከመሬቱ ከማስነሳት ይልቅ ማጠጋጋት” በሚለው ፅሁፌ ለማሳየት እንደሞከርኩት፣ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን መቋረጥና ያለመቋረጥ፣ በሞጆ-ሃዋሳ የፈጣን መንገድ ግንባታ ፕሮጀክት ምክንያት 20.00 ብር በካሬ ሜትር እየተከፈለው ከእርሻ መሬቱ የሚፈናቀለውን ገበሬ አይታደገውም። በወሊሶ፣ በጅማ፣ በነቀምት፣ በመቀሌ፣ በባህርዳር፣ በሃዋሳ፣ በድሬዳዋ…ወዘተ፣ ብቻ በሁሉም ከተሞች እየሆነ ያለው ነገር አንድና ተመሣሣይ ነው፦ ለገበሬ ሕይወት አስፈላጊውን ትኩረት ሳይሰጡ፣ ያለ በቂ ትኩረትና ቅድመ-ዝግጅት ለዘመናት ከኖረበት ኑሮና አኗኗር ማፈናቃል ነው። ስለዚህ፣ ችግሩ የመልካም አስተዳደርና ዴሞክራሲ ጉዳይ ስለመሆኑ ጥርጥር የለውም።

በመጨረሻም፣ ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት እንዲቻል በቅድሚያ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት እንደማንኛውም ልዓላዊ አስተዳደር በክልሉ ውስጥ ለሚከናዎን ማንኛውም ዓይነት ተግባር ሙሉ የሆነ የባለቤትነት ሚናውን እንዲጫወት የሚያስችል አሰራር በሕገ-መንግስቱ ድንጋጌ መሰረት መዘርጋት ያለባቸው፣ ለዚህም አስፈላጊ የሆኑ አሰራሮች እና መመሪያዎች መዘጋጀት አለባቸው። በመቀጠል፣ የአዲስ አበባ መስተዳደር፣ የፌደራሉና የክልሉ መስተዳደሮች በኦሮሚያ ክልል የተከሰተው ሰፊ ህዝባዊ ተቃውሞ መሰረታዊ ምክንያት ምን እንደሆነ ግልፅ የሆነ ግንዛቤ ሊኖራቸው ይገባል። ለዚህ ደግሞ ዋና ምክንያቱ ምን እንደሆነ መረዳት ይጠይቃል። በአጠቃላይ፣ ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር ተያይዞ ለተከሰተው ችግር ዘላቂ መፍትሄ መስጠት የሚቻለው የጉዳዩ ባለቤት ሙሉ የባለቤትነት ሚናውን እንዲጫዎት ሲደረግ እና የችግሩ ዋና መንስዔን መረዳት ሲቻል ነው። ነገር ግን፣ የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን በማቋረጥ ለችግሩ መፍትሄ ለመስጠት መሞከር ስህተትን እንደመሳሳት ይቆጠራል::

************

Seyoum Teshome is a Lecturer at Ambo University Woliso Campus and head of Management Department. He was born in Arsi, Assela, in 1979 and studied Management at Harameya University and MBA at Mekelle University. He also blogs at http://ethiothinkthank.com

more recommended stories