ለጋማ ጋማማ አህያም ጋማ አላት – አያስጥልም እንጂ ጅብ ሲዘነጥላት

(አርአያ ጌታቸው)

በጅቦች መንድር ነው አሉ። ሶስት አህዮች በጠፍ ጨረቃ ሰፊ መስክ ላይ ተሰማርተው ሳር እየጋጡ ዓለማቸውን ይቀጫሉ። በዚህ መሀል ሶሰት ጅቦች የሚበላ ፍለጋ ሲዘዋወሩ አህዮቹን ይመለከቷቸዋል። በአህዮቹ ድፍረት የተገረሙት ጅቦቹም “እነዚህ አህዮች እንዴት ቢጠግቡ እንዴትስ ቢንቁን ነው በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት እንደዚህ ተዝናንተው ሳር የሚግጡት?” ሲሉ እርስ በእርስ ይጠያየቃሉ። አውጥተው አውርደውም ለምን ችሎት ተቀምጠን አንፈርድባቸውም በማለት ይወስናሉ። አህዮቹም በየተራ ወደ ጅቦቹ እየቀረቡ ጥያቄ ይቀርብላቸው ጀመር፤

የመጀመሪያዋ አህያ ቀረበች፤

“እመት አህያ እንደው ለመሆኑ ማንን ብተተማማኝ ነው በዚህ ሌሊት በእኛ ግዛት ያላንዳች ከልካይ ሳር የምትግጭው?” ተብላ ተጠየቀች። አህይትም ሳትፈራ ቅምም ሳይላት “ፈጣሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ግፍ የሚሠራ ካለ የፈጠረኝ ዝም አይለውም፤ መዓት ያወርድበታል” ስትል ለጅቦቹ መልሷን ሰጠች። ፍርዱን በኋላ ተብላ ተራውን ለሁለተኛው አህያ ለቅቃ ዞር ብላ ተቀመጠች።

ለሁለተኛዋ አህያም ተተመሳሰይ ጥያቄ ቀረበላት። እርሷም በተመሳሳይ ሳትደናገጥ “አሳዳሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ጥቃት የሚያደርስ ካለ አሳዳሪዬ ዝም አይለውም፤ ይበቀልልኛል” በማለት ምላሿን ሰጠች። እርሷም ፍርዱን እንድትጠብቅ ተነግሯት ለሶሰትኛዋ አህያ ስፍራውን ለቀቀች።

ጅቦቹ ሶስተኛዋን አህያ አስቀርበው “አንቺስ ማንን ብትተማማኝ ነው በዚህ ጠፍ ጨረቃ ይህን አይነት ድፍረት ይህንን አይነትም መዝናናት?” ሲሉ በግርምት እንደተሞሉ ጠየቋት። ይህችኛዋ አህያም ትንሽ አሰብ አድርጋ፤ «አንደኛ እናንተን የአካባቢውን ንጉሶች ሁለተኛም ጋማዬን ተማምኜ» ስትል ቃሏን ሰጠች። በመልሷ ፈገግ ያሉት ጅቦቹም ፍርዷን እንድትጠብቅ እስከዚያው ከመሰሎቿ ጋር እንድትቀመጥ አዝዘው ለብቻቸው መምክር ጀመሩ።

ጅቦቹ ማንን መብላት እንዳለባቸው አወጡ አወረዱ። “የመጀመሪያዋን ብንበላት ፈጣሪ አይለቀንም። ሁለተኛዋን ብንበላትም አሳዳሪዋ ይበቀለናል። እኛንና ጋማዋን የተማማነችውን አህያ ብንብላት ማንም አይነካንም፤ እስኪ ጋማዋም ያስጥላት እንደሆነ እንይ” ሲሉ ተስማሙ። ሮጠው በመሄድም ሶስተኛዋ አህያ ላይ ሰፈሩባት። ዘነጣጥለውም ረሃባቸውን ኣስታገሱባት አሉ።

እንዲህ እንደተረቱ ሁሉ በመካከላችንም ብዙ አህዮች ብዙም ጅቦች እንዳሉ ልብ ብለው አይተው ይሆን? የእርስዎን ምላሽ ለእርስዎ ልተወውና የእኔን ትዝብት ልንገርዎት። ሰሞኑን ከወደ ተባበሩት መንግስታት የተሰማ ዜና አለ። የኤርትራ መንግስት በኢትዮጵያ መንግስት አሸባሪ ተብለው ከተሰየሙ ድርጅቶች ጋር ቃል ኪዳን ማሰሩንና ለዚህም ስራ በዝቶበት ሽርጉድ ሲል መክረሙን ድርጅቱ ይፋ ካደረገው መረጃ አንብበናል። ምስራቅ አፍሪካ ጭር ሲል የማይወደው የኤርትራ መንግስት የአልቃይዳ ክንፍ ከሆነው አልሸባብ፣ ራሱን የኦጋዴን ነጻ አውጭ ግንባር /ኦብነግ/ ብሎ ከሚጠራው አሸባሪ ድርጅት ጋር የአህያዎቹንና የጅቦቹን አይነት ታሪክ ሊደግሙ ውል አስረዋል።

እነዚህ ሁለት አህዮች / አልሸባብና ኦብነግ/ በቀጠናው የሽብር ንጉስ በሆነው ጅቡ የኤርትራ መንግስት ግዛት ስር የወዳደቀ ትርፍራፊ ሊቃርሙ መጓዛቸው እርሱንም ተማምነው መኖራቸው ብዙም አይገርመንም። ምክንያቱም መጨረሻቸው እርስ በእርስ መዘነጣጠል እንደሚሆን እንኳንስ እኛ እነሱም አሳምረው ያውቁታል። የማይተማመኑ ባልጀሮች በየወንዙ ዳር መማማላቸውም ደንብ ነው። አሁንም የሆነው ይሄው ነው። በሶማሊያ የነበረውን ግዛት ሁሉ እየተነጠቀ መፈናፈኛ ያጣው አልሸባብና በኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት አከርካሪው ተሰብሮ የተባረረው ሽርፍራፊ የኦብነግ ኃይሎች የኤርትራን መንግስት ተማምነው ከእርሱ ጋር ውል ማሰራቸው የመጨረሻቸው መጀመሪያ ላይ መድረሳቸውን መረዳት አላቃተንም።

የድርጅቱ መግለጫ የኤርትራ መንግስት እአአ በ1907 የተፈረመውን አለም አቀፍ ስምምነት ወደ ጎን በመተው ለኦብነግ የትጥቅና የገንዘብ ድጋፍ እያደረ ይገኛል ሲል ይከሳል። በዚህ ድጋፍ የልብ ልብ ያገኘው አሸባሪው የኦጋዴን ነጻ አውጭ ግንባርም አቅጣጫውን በመቀየር ወደ ሞቃዲሾ በማቅናት ከአልሸባብ ጋር የሎጅስቲክ ስምምነት አድርጓል። ጌታውንና ጅቡን የኤርትራ መንግስት ተማምኖ።

እንደሚታወቀው በእአአ በ2012 አብዛኛው የኦጋዴን ነጻ አውጭ ግንባር ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የሰላም ድርድር በማድረግ ትጥቅ ፈትቶ በሰላም ወደ ክልሉ ተቀላቅሏል። ነገር ግን ይሄንን መንገድ ያልፈለጉ ጥቂት የቡድኑ አባላት እንደገና በመሰባሰብ ወደ እኩይ ተግባራቸው ተመልሰዋል። ይህ ቡድን ያለፈቃዳችን ያለ እኛም ስምምነት በቅኝ ግዛት ውስጥ ነን ብሎ የሚያምን ነው። ልብ ይበሉ ኦብነጎች እያሉ ያሉት የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በቅኝ ግዛት ስር ነው እንደ ማለት ነው። ይህች አስተሳሰብ ደግሞ የማን እንደሆነች በደንብ ትታወቃለች። የጌታቸው የጅቡ ይቅርታ የኤርትራ መንግስት ጸረ ኢትዮጵያ አቋም ናት። ይሄው የምስራቅ አፍሪካ ሰላም የሚያመው የኤርትራው ሰውዬ የሚመራው መንግስት እነዚህን ሲበሉ የላኳቸውን ጀሌዎቹን እያሰለጠነ እያሰየጠንም ጭምር የረጅም ጊዜ ህልሙን ያሳኩለት ዘንድ ላይ ታች ማለቱን ቀጥሏል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኤርትራው ፕሬዝዳንት አማካሪ በየማነ ገብረአብ እና በስለለ ክፍል ዋና ኃላፊው አብረሃ ካሳ አስተባበሪነት በተደረገ ኮንፈረንስ የኡጋዴን ነጻ አውጭ ግንባር መቀመጫውን ወደ ሶማሊያ ሞቃዲሾ እንዲያደርግ ተስማምተዋል። ለዚህ የስፍራ ቅያሬም የተሰጠው ምክንያት በሞቃዲሾ ያለውን ያልሰከነ የጸጥታ ሁኔታ በመጠቀም ድርጀቱን መሳሪያ ለማስታጠቅና መልሶ ወደ ኦጋዴን አካባቢ ለማሰማራት የሚል ነው። ይህ የኢሳያስ መንግስት ቁማር የት እንደሚያደርሳቸው ወደፊት የሚታይ ቢሆንም ከወዲሁ መነጋር የሚቻለው ግን የኦብነግ እጣ ፋንታ ጋማዋንና ጅቦችን እንደተማመነችው አህያ መሆኑ አይቀርም።

የኢትዮጵያ መንግስት እጅግ ጠንካራ የሆነ የደህንነት መረብ እንዳለው ወዳጅም ብቻ ሳይሆን ጠላት የሚያውቀው የአደባባይ ምስጢር ነው። ታዲያ ኦብነግ ይሄንን አጥቶት ይሆን የቀቢጸ ተስፋ ተግባር እየፈጸመ ያለው? አይደለም። ጅቦቹን እንደተማመነችዋ አህያ ሆኖ እንጂ። ይሄ አሸባሪ ድርጅት ከጌታው የኤርትራ መንግስትም በላይ የመከላከያ ሰራዊታችንን የፈረጠመ እጅ በተደጋጋሚ የቀመሰው ነውና ኦጋዴን ብሎም ኢትዮጵያ ሱሚ መሆናቸውን ጠንቅቆ ያውቃል።

ሪፖርቱ የኤርትራ መንግስት ለኦብነግ የገንዘብ ድጋፍ እየደረገ ስለመሆኑ በደፈናው ሳይሆን አብነት በመጥቀስ ነው የጥፋት አባትና ልጅ መሆናቸውን ያጋለጠው። የኢሳያስ መንግስት በተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ዱባይ የሚገኝን ባንክ በመጠቀም ለኦጋዴን ነጻ አወጭ ግንባር ገንዘብ አስተላልፏል። የአስመራ ሰዎች ዱባይ ወደ ሚገኝ የአሸባሪው ድርጅት አካውንት ታዋካል የሚባል የሃዋላ አገልግሎትን በመጠቀም ጠቀም ያለ ገንዘብ አስገብተዋል። ይህ የገንዘብ አካውንት ደግሞ ነዋሪነቱ አውስትራሊያ በሆነ የአሸባሪው ድርጅት ምክትል ሊቀመንበር ሞሀመድ ኢስማኤል ስም የሚንቀሳቀስ ነው። ይህ ገንዘብ በግለሰቡ ከወጣ በኋላ ባልታወቀ ሌላ ሃዋላ አመካኝነት ለአሸባሪዎቹ እንዲደርስ ተደርጓል። ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመደገፍ ድርጊት ደግሞ በኢትዮጵያም ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ህግ የሚያስጠይቅ እኩይ ተግባር ነው።

የኤርትራ መንግስት የዚህን አይነት የወንበዴ ስራ የሚሰራው ለኢትዮጵያ ካለው ጥልቅ ጥላቻ በመነሳት ነው። አሸባሪው ድርጅት ኦብነግም ሆነ አልሸባብ ከኤርትራ ህዝብ ጋር ምንም የሚያመሳስልም ብቻ ሳይሆን አንድ ሊያደርግ ቁመናና ዓላማ የላቸውም። ነገር ግን የጠላቴ ጠላት ለእኔ ወዳጄ ነው በሚለው ቀመር እነዚህ ጌታቸውንና ጋማቸውን የተማመኑ አሸባሪ ድርጅቶች ጣታቸውን በኢትዮጵያ ላይ ቀስረዋል። በዚህ ድርጊታቸውም ከተጠያቂነት እንደማያመልጡ እኛም ብቻ ሳንሆን የአለም መንግስታት አሳስበዋል።

በተለይ ደግሞ በሪፖርቱ ላይ የተጠቀሱት የኤርትራ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት ከዚህ ሁሉ ሴራ ጀርባ ያሉ መሆናቸው ታውቋል። የተባበሩት መንግስትት ሪፖርት ኮሎኔል ተወልደ ሀብቴ፣ ኮሎኔል ሙሳ እና ኮሎኔል ሀጎስ የተባሉ ከፍተኛ የኤርትራ መንግስት ወታደራዊ ባለስልጣኖች ለኦጋዴን ነጻ አውጭ ግንባር ባህር ተሻግሮ መሄድ ተጠያቂ ናቸው ይላል። እነዚህ ወታደራዊ ባለስልጣኖች በተጨማሪ ከኤርትራ መንግስት ድጋፍ ለሚያገኙ ታጣቂዎች ክትትል የሚያደርገውና የፕሬዝዳንቱ የቅርብ ሰው የሆነው ኮሎኔል ተስፋልደት ሀብተሥላሴም እጁ እንዳለበት ይገልጻል።

ይኸው ሪፖርት በቀቢጸ ተስፋ እየተንቀሳቀሰ ያለው የኦጋዴን ነጻ አውጭ ግንባር በአሁኑ ወቅት መቀመጫውን በሰሜናዊ ሞቃዲሾ ጋልካሲዮ በተባለ አካባቢ አድርጓል። ይህ ቦታም የተመረጠው ወደ ኢትዮጵያ እንደልባቸው ለመግባትና ለመውጣት ወታደሮችንም ለማሰልጠን መሳሪያም ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት ይመቸናል ብለው እንደሆነ ሪፖርቱ እማኞችን በመጥቀስ ያብራራል። በተጨማሪም መሳሪያ እንደልባቸው ለመሸመት አካባቢው ምቹ መሆኑ ተገልጿል።

የኢትዮጵያ መንግስት የደህንነት መረብና የመከላከያ ሰራዊቱም የመዘናጋት ባህሪ ቢኖራቸው ኖሮ ፍረሃት ይሰማን ይሆን ይሆናል። እንደመታደል ሆኖ ግን የኢትዮጵያ ደህንነት መዋቅርና የመከላከያ ሰራዊት ፍጹም ጠንካራና በጅቦችና ጅቦችን በተማመኑ አህዮች የሚሰበር አይደለም። ስለዚህም የእኛ መልዕክት ዛሬም እንደቀደመው ጊዜ ሁሉ ተመሳሳይ ነው፤ “አልሆነልሽም አንቺ ጋለሞታ ቂጣሽን በልተሽ ወደ መኝታ የሚል”።

አበቃሁ!

***********

ምንጭ፡- አዲስ ዘመን፣ ሕዳር 23-2007

Areaya Getachew (MA) is a public relations expert at a foreign embassy. He studied second degree at Addis Ababa University and was deputy editor in-chief of Addis Zemen newspaper.

more recommended stories