የዩኒቨርስቲዎች ሃይማኖታዊ ስነስርአትና አለባበስ ደንብን በመቃወም በሽብር የተሳተፉ ግለሰቦች ጥፋተኛ ተባሉ

(በጥላሁን ካሳ)

የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ሃይማኖታዊ ስነስርአትና አለባበስን በሚመለከት ያወጡትን የስነምግባር ደንብ በመቃወም የተለያዩ አደረጃጀቶችን በመፍጠር በሽብር ድርጊት ውስጥ የተሳተፉ 13 ግለሰቦች የጥፋተኝነት ፍርድ ተላለፈባቸው።

ተከሳሾቹ እስማኤል ኑር ሁሴን፣ ፈትያ መሃመድ፣ ኑርዬ ቃሲም፣ ያሲን ፈያሞ፣ መሃመድ አሚን፣ መሃመድ ሰይድ፣ የሱፍ ከድር፣ ጣሂር መሃመድ፣ መሃመድ ሰይድ፣ ሰይድ ኢብራሂም፣ አብደላ መሃመድ፣ አብዲ መሃመድ እና ኢብራሂም የሱፍ ኢብራሂም ናቸው።Ethiopia Federal High Court - Lideta

የወንጀል አድማ ስምምነት በማድረግ የመንግስት ዩንቨርስቲዎች ሃይማኖታዊ ስነስርአትና አለባበስን በሚመለከት ያወጡትን የስነምግባር ደንብ በመቃወም የተለያዩ ምስጢራዊ  አደረጃጀቶችን በመጠቀም ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ የሽብር ድርጊት ፈጽመዋል በሚል ነው የፌደራል አቃቤህግ የከሰሳቸው።

ተከሳሾቹ በ2005 ዓ.ም በባህርዳር ዩንቨርሲቲ ሃይማኖታዊ አለባበስን በሚመለከት የወጣውን ደንብ ተከትሎ በጥቂት ዩኒቨርሲቲ ሙስሊም ተማሪዎች የተጀመረው አመጽና አድማ በተናጠል ከሚሆን ሃገር አቀፍ መሆን አለበት በማለት በየዩኒቨርስቲዎች በስልክ፣ በማህበራዊ ድረ ገጾችና በአካል በመንቀሳቀስ ቀስቅሰዋል።

በሽብር ተከሰው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙ ራሳቸውን የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ እያሉ የሚጠሩ 17 ግለሰቦች ከህግ ውጭ ከእስር እንዲፈቱም ተንቀሳቅሰዋል።

ከእንግዲህ በኋላ ሰላማዊ ትግል አብቅቷል፤ መላው ሙስሊም ለመረጃ  ቅርብ መሆን አለበት፤ ለሚፈጠረው ነገር ሁሉ ራሱን ማዘጋጀት አለበት በማለት ግልጽ የአመጽ ጥሪ አድርገዋል ነው የሚለው ክሱ።

ክሱን ሲመረምር የቆየው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድቤት የአቃቤ ህግን ምስክር እና የተከሳሾችን የመከላከያ ማስረጃ ከመረመረ በኋላ ሁሉም ተከሳሾች ክሱን ማስተባበል ባለመቻላቸው ጥፋተኞች ናቸሁ ሲል ፈርዶባቸዋል።

ችሎቱ የቅጣት ውሳኔ ለማስተላለፍ ለጥቅምት 4 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
*******
ፋና፡- መስከረም 26፣ 2007

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories