በዋሽንግተን ዲሲ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሁከት የፈፀሙት ግለሰቦች በፖሊስ ተለይተዋል

ትናንት ጠዋት በዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ የነበረው ሁከት የኢትዮጵያን እድገት እና መልካም ስም የማይፈልጉ ጥቂት ግለሰቦች የፈፀሙት ድርጊት መሆኑን ኢምባሲው ገለፀ።

በዩናይትድ ስቴትስ የኢትዮጵያ አምባሳደር ግርማ ብሩ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደገለፁት፥ ትናንት በአሜሪካ ሰዓት አቆጣጠር እኩለ ቀን አከባቢ ቁጥራቸው ከ10 እስከ 15 የሚደርሱ ሰዎች ወደ ኢምባሲው በመግባት ሁከት ለመፍጠር ሞክረዋል።

አምባሳደር ግርማ እንዳሉት ሰዎቹ ወደ ኢምባሲው የቆንስላ አገልግሎት ስራ ክፍል ገብተው “አምባሳደሩን እንፈልገዋለን” በሚል አንዳንድ ፀያፍ ንግግሮችን ሲናገሩ የስራ ክፍሉ ሰራተኞች አምባሳደሩን ማግኘት የሚቻለው በፕሮግራም መሆኑን ሲገልፁላቸው ተሳድበው በመውጣት የኢትዮጵያን ባንዲራ ለማውረድ ሙከራ አድርገዋል።Ethiopia embassy washington disturbance

በዚህም ጊዜ የኢምባሲው የጥበቃ ሰራተኞች ከኢምባሲው ሰራተኞች ጋር በመሆን ይህንን ህገ ወጥ ተግባር እንዳይፈፅሙ የመከላከል ተግባር አከናውነዋል ነው ያሉት።

ሰዎቹ ህገ ወጥ ተግባራቸውን ማድረግ ከጀመሩ ከሶስት እስከ አምስት ደቂቃ ባለ ጊዜ ውስጥ የሀገሪቱ የጥበቃ ሀይል ተጠርቶ መምጣቱን ጠቁመዋል።
ከዚያም በኋላ ይህንን ተግባር የፈፀሙ ሰዎች ለአንድ ሰዓት በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ ማንነታቸውን በመለየትና አድራሻቸውን በመያዝ እንዲለቀቁ መደረጉን አምባሳደር ግርማ ተናግረዋል።

አመሻሽ ወደ 11 ሰዓት ገደማ አካባቢው ወደ ሰላማዊ ሁኔታ ተመልሶ ስራዎች በተለመደው መንገድ መቀጠላቸውን ነው አምባሳደሩ የገለፁት።

በእለቱ ምንም ዓይነት በህጋዊነት የተጠራ ሰልፍ እንዳልነበር ያነሱት አምባሳደር ግርማ፥ የድርጊቱ ፈፃሚዎች በየቦታው በሚዘጋጁ ሰልፎች ሁሌም በሁከት መልክ የሚሳተፉ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ለስራ ወደ አገሪቱ ሲመጡ እየተከታተሉ ተራና የወረደ ስድብ የሚሳደቡ በተወሰነ የፖለቲካ ድርጅቶችና በሻእቢያ ጀሌዎች የሚነዱ መሆናቸውን አመልክተዋል።

በህገወጥ ድርጊቶቻቸው በአገሪቱ ፖሊሶች ሳይቀር የሚታወቁት እነዚህ ህገወጥ ሰዎች በቅርብ ጊዜ በኢትዮጵያና አሜሪካ መሪዎች ደረጃ የተደረገው ውይይት በጣም ውጤታማ መሆኑና ይህም ከመሪዎቹ አንደበት የተነገረ መሆኑ ያናደዳቸው ናቸው ብለዋል።

የሁለቱ አገራት ግኑኝነት ፋይዳ ወዳለው ደረጃ መሸጋገሩን ሲያውቁ ተስፋ በመቁረጥ የፈፀሙት ድርጊት እንደሆነም አመልክተዋል።

ድርጊቱ ከተፈፀመ በኋላም በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ስልክ በመደወል “ባንዲራችንን የሚያዋርድና ለማዋረድ በሚሞክረው ድርጊት እጅግ አዝነናል” ሲሉ ገልፀውልናል ነው ያሉት።

እንደ አምባሳደር ግርማ የኢትዮጵያ ሀብትና ንብረት ወደ ሆነው ኢምባሲ ከህግ ውጪና ከተለምዶው የቪየና ኮንቬንሽን ውጪ በመሄድ እንዲህ ዓይነት ፀያፍ አድራጎት መፈፀማቸውንም ኢትዮጵያውያኑና ትውልደ ኢትዮጵያውያኑ ኮንነዋል።

*****
ምንጭ፡- ፋና፣ መስከረም 20፣ 2007

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories