“ዶክተር ኢንጂነር” ሳሙኤል ዘሚካኤል በማታለልና በሀሰት ሰነድ መገልገል ክስ ተመሰረተበት

አቃቤ ህግ ማታለልና በሀሰት ሰነድ መገልገል የሚሉ ሶስት ክሶች ናቸው የመሰረተበት።

በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ከቀረቡት ክሶች መካከል በ12/04/06 ቦሌ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው ገርጂ አምባሳደር ልብስ ስፌት ውስጥ ተጠርጣሪው ወንጀል መፈፀሙን ይጠቅሳል።
ዶክተር ኢንጂነር ነኝ በማለት አሳሳች ቃል በመናገር የድርጅቱን ባለቤት አቶ ሰኢድ መሀመድን አጭበርብሯል የሚለው በክሱ ተመልክቷል።

ድርጅትዎን በተለያዩ መድረኮች አስተዋውቃለው ስኬታማ የሆኑ ሰዎችንና ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ 20 ታዋቂ ሰዎች የሚካተቱበትን መፅሀፍ እያዘጋጀው በመሆኑ ድርጅትዎን በዚህ መፅሀፍ አስተዋውቃለሁ በማለት የተሳሳተ እምነታቸውን በመጠቀም ከ58 ሺህ ብር በላይ ወሰዶባቸዋል የሚልም በክሱ ተጠቅሷል።

ከእኝህ ግለሰብ ተማሪዎችን አሰልጥኜ አስመርቃለሁ በሚል ሰበብ 4 ሙሉ ልብሶችን ቼክ ሰጥቶ መውሰዱም በክሱ ተጠቅሷል።

ከቦሌ ቅርንጫፍ ወጋገን ባንክ በተዘጋ የሂሳብ ቁጥሩ በሌለው ስንቅ የአልባሳቱን ዋጋ 6 ሺህ ብር ቼክ ፈርሞ በመስጠትም ተከሷል።

በ11/07/06 በግምት ከጠዋቱ 3 ሰዓት ቦሌ ወረዳ 3 ልዩ ቦታው ፒኬ ህንፃ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቻይና አፍሪካ ቅርንጫፍ ተፈፀመ የተባለውን ወንጀል አቃቤ ህግ 3ኛ ክስ አድርጎታል።

ግለሰቡ የካ ክፍለ ከተማ ቤቴል ሜዲካል ኮሙኒኬሽን ኤንድ ኮንሰልቲንግ ሀላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር የሚል ስም የተሰጠውን የንግድ ፍቃድ አሳይቶ ብር ለመበደር ይሄዳል።

ይህ ንግድ ፍቃድ ከ2004 እና 2005 አ.ም ምንም እድሳት አልተደረገለትም የሚለው በክሱ ተጠቅሷል።

ተከሳሹ ግን የ2 ቱንም አመታት የንግድ ፍቃድ እንደታደሰ በማድረግ በራሱ እጅ ፅሁፍ በመፃፍና በመፈረም እንዲሁም ሀሰተኛ ማህተም በመምታት ለባንኩ አቅርቧል።

በመሆኑም አቃቤ ህግ በሀሰተኛ ሰነድ በመገልገል ወንጀል ክስ መስርቶበታል።

ተከሳሹ ሶስቱንም ክሶች ጠበቃ አቁሜ እከራከራለሁ በማለቱ የአራዳ ምድብ ችሎት ጠበቃ አቁሞ እንዲከራከር ለ15/01/07 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
**********
ምንጭ፡- ፋና፣ መስከረም 12፣ 2007

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories