የመንግሥት ሠራተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት ሰኞ ይጀመራል

የፌዴራልና የአዲስ አበባ ሲቪል ሰርቪስ ሠራተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት የሙከራ ስምሪት የፊታችን ሰኞ እንደሚጀመር የፐብሊክ ሰርቪስ ሠራተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅት አስታወቀ፤ለጊዜው አገልግሎት መስጠት ከሚጀምሩት 55 አውቶቡሶች በተጨማሪ ዘግይተው የደረሱ መረጃዎችን መሠረት በማድረግ ሌሎች አዳዲስ አውቶቡሶች እንደሚሰማሩ ታውቋል። Civil Servants' bus

የድርጅቱ ዋና ሥ ራ አስኪያጅ አቶ ደረጀ ወልደ ዮሐንስ እንደተናገሩት፤ መስከረም 5 ቀን 2007 ዓ.ም የሚጀመረው አገልግሎት ለመነሻ 10 የሙከራ ስምሪት መስመሮች ይኖሩታል። ከመስመሮቹ መካከል ጨፌ-ሃያት፣ ጀሞ፣ አቃቂ ቃሊቲ፣ የሺ ደበሌና አስኮ ሳንሱሲ ይገኙበታል። የሙከራ ስምሪቱ የጉዞ አቅጣጫቸው በጎን በኩል በተጻፈባቸው 55 አውቶቡሶች የሚጀመር ይሆናል።

ሠራተኞችን ለማጓጓዝ በጊዜያዊነት የአንበሳ አውቶቡስ ፌርማታዎችን እንደሚጠቀሙ አቶ ደረጀ ተናግረዋል። ለጊዜው አገልግሎቱ የሚሰጠው አስፈላጊ የሠራተኞቻቸውን መረጃ ቀድመው ለላኩ መስሪያ ቤት ሠራተኞች ሲሆን፣ ቀስ በቀስ አውቶቡሶችን በመጨመር ሁሉም የፌዴራል ሠራተኞች አገልግሎቱን እንዲያገኙ ይደረጋል።

ዘግይተው የቀረቡ መረጃዎችን በማደራጀትና ጥቆማዎችን ተቀብሎ እርምት በመውሰድ የአውቶቡሶችን ቁጥር በመጨመር አገልግሎቱ እንደሚሻሻልም ተናግረዋል። የአገልግሎቱ መጀመር የመንግሥት ሠራተኞችን ገንዘብ፣ ጊዜና እንግልት ይቀንሳል ብለዋል አቶ ደረጀ።

መስሪያ ቤቶች ሠራተኞች አገልግሎቱን ማግኘት የሚችሉበትን መታወቂያ እየወሰዱ እንደሚገኙ የገለጹት ዋና ሥራ አስኪያጁ መታወቂያውን ያልወሰዱ መስሪያ ቤቶች ከዛሬ ጀምሮ መጥተው እንዲወስዱ አሳስበዋል። ለጊዜው የተሰሩት መታወቂያዎች የሠራተኞቹን መነሻና መድረሻ የጉዞ መስመር ጨምሮ የተለያዩ መረጃዎችን አካተተዋል። ሠራተኛው በተመደበለት አውቶቡስ ብቻ መጠቀም እንደሚገባውም ጠቁመዋል። ወደ ፊት ኤሌክትሮኒክስ መታወቂያዎችን አገልግሎት ላይ እንደሚያውሉም ተናግረዋል።

የትራንስፖርት አገልግሎቱ ሙሉ ለሙሉ ሲጀመር ከፍተኛ የነዋሪ ብዛት ካለባቸው 26 መስመሮች በመነሳት የመንግሥት መስሪያ ቤቶች በብዛት ወደሚገኙባቸው 11 መዳረሻዎች ሠራተኞችን ማጓጓዝ ያስችላል።

*******

ምንጭ፡ አዲስ ዘመን

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories