በአሶሳ ምንነቱ ያልታወቀ በሽታ ተከሰተ – ክልሉ ኢቦላ አይደለም ይላል

(አለማየሁ አንበሴ)

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የምግብ መበከል ሊሆን ይችላል ተብሎ የተጠረጠረ ምንነቱ ያልታወቀ በሽታ በሁለት ሰዎች ላይ መከሰቱንና አንደኛው መሞቱን የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ሃብታሙ ታዬ ለአዲስ አድማስ የገለፁ ሲሆን የኢቦላ በሽታ በክልሉ በየትኛውም አካባቢ አልተከሰተም ብለዋል፡፡Assosa, Benshangul Gumuz region, Ethiopia

የተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች በክልሉ በሚገኘው ባምባሲ የስደተኞች ጣቢያ በሽታው ተከስቷል ሲሉ ያሰራጩት መረጃ የተሳሳተ መሆኑን የጠቆሙት የቢሮ ኃላፊው፤ ለጊዜው በትክክል ምንነቱ ያልታወቀው በሽታ የተከሰተው ከስደተኞች ጋር ምንም አይነት ንክኪ በሌለው የአሶሳ ከተማ መንደር 47 በሚባል አካባቢ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በህክምና ባለሙያዎች የምግብ መበከል ሊሆን ይችላል በተባለው በዚህ በሽታ የተያዙት ሁለት ግለሰቦች ላይ የታየው ምልክት ደም ማስመለስና ማስቀመጥ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ሃብታሙ፤ በሽተኞቹ ለብቻ ተገልለው በጥንቃቄ እንዲታከሙ ተደርጓል፣ የአንደኛውን ህይወት ማትረፍ ባይቻልም ሌላኛው ቤተሰቦቻቸው ጋር ሆነው ህክምናቸውን እየተከታተሉ ነው ብለዋል፡፡

የኢቦላ በሽታ ምልክቶች ከሌሎች በሽታዎች ጋርም ሊመሳሰል ይችላል ያሉት የቢሮ ኃላፊው፤ ነገር ግን በህክምና ባለሙያዎች በሽታው ኢቦላ አለመሆኑ ተረጋግጧል፤ በሽታው የምግብ መበከል ሳይሆን እንዳልቀረ ተጠርጥሯል ብሏል፡፡

በድንበር አካባቢ በሽታው ሊገባ ይችላል የሚል ስጋት እንዳለ የጠየቅናቸው ኃላፊው፤ ሱዳን ውስጥ በሽታው ስለሌለ ስጋት የለብንም ብለዋል፡፡

ህብረተሰቡ በሽታው ኢቦላ ነው በሚል እንዳይደናገጥ በክልሉ ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ትናንት ጠዋት ቀርበው በሽታው ኢቦላ አለመሆኑን ማስረዳታቸውን አቶ ሃብታሙ ገልፀዋል፡፡

በተጨማሪም ግብረ ሃይል በማቋቋም ምንነቱ በትክክል ያልታወቀውን በሽታ ለማጣራት ባለሙያዎች የተከሰተበት ቦታ ድረስ በመሄድ የማጣራት ስራ መስራታቸውንና ኢቦላ በክልሉ የትኛውም አካባቢ እንዳልተከሰተ ማረጋገጣቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡

የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አህመድ አማኖ፤ በሃገሪቱ በየትኛውም አካባቢ ኢቦላ አለመከሰቱን ከየክልሎች በሚሰበሰቡ መረጃዎች መረዳት መቻሉን ለአዲስ አድማስ ገልፀው፤ ምናልባትም ከሙቀት መጨመር ጋር ተያይዞ ትኩሳት፣ የአፍንጫ መንሰር ሊያጋጥም ይችላል ብለዋል፡፡

አሶሳ ኢቦላ ተከሰተ ተብሎ በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲዎች የተሰራጨውም ትክክለኛ መረጃ አይደለም ብለዋል ኃላፊው፡፡

********

ምንጭ፡- አዲስ አድማስ፣ ነሐሴ 17፣ 2006

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories