ETV | የግንቦት 7ቱ አንዳርጋቸው ፅጌ በየመን ተይዞ ለኢትዮጵያ ተላልፎ ተሰጥቷል

በሸብር ወንጀል ተከሶ በተደጋጋሚ የተፈረደበትና በኢትዮጵያ መንግስት በጥብቅ ሲፈለግ የነበረው የግንቦት 7 አሸባሪ ድርጅት አመራር የሆነው አንዳርጋቸው ፅጌ በቁጥጥር ስር መዋሉን የብሔራዊ የመረጃና የደሀንነት አገልግሎት እና የፌዴራል ፖሊስ የጋራ ፀረ ሽብር ግብረ ሀይል አስታወቀ፡፡

በየመን እና በኢትዮጵያ የመረጃና ደህንነት ተቋማት ማዕከል በፀረ ሽበር ትግሉ ተቀናጅተው ለመስራት በተደረሰው ስምምነት ሁለቱም ተቋማት አሽከባሪዎችን በመያዝና በመለዋወጥ በጋራ እንደሚሰሩ ይታወቃል፡፡Andargachew Tsige

በዚህም መሰረት የዚህ ተፈላጊ ወንጀለኛ የጉዞ መስመር እና የሚጓዝበትን እለት አስቀድሞ መረጃ የደረሰው የኢትዮጵያ ብሔራዊ የመረጃና እና ደህንነት አገልግሎት መረጃውን ለአጋር የየመን ብሔራዊ የደህንነት ቢሮ በማሳወቅ በሰንአ በኩል ወደ ኤርትራ ሊገባ ሲል ሰኔ 16/2006 በቁጥጥር ስር ውሎ በዚያው ዕለት ለኢትዮጵያ ተላልፎ ተሰጥቷል፡፡

ቱፋ፣ ጅንፓወል፣ ደርባባ፣ ጀምስፍራንኪ፣ሮቢ እና ሓሪና በሚባሉ የተለያዩ የሽብር የሚስጥር ስሞች ሲጠቀም የቆየው ይኸው የአሸባሪ ድርጅቱ አመራር ከ 5 ዓመት በላይ በቋሚነት ኤርትራ ወስጥ መሽጎ ከሻእቢያና ከሌላ ፀረ ኢትዮጵያ ከሆነ መንግስት ጋር በመቀናጀት አሸባሪዎችን በማደራጀት እና በማሰልጠን የአገራችንን ሰላም ለማደፍረስ እና ልማቷን ለማደናቀፍ የተለያዩ ጥረቶች ሲደረግ እንደነበር ይታወቃል፡፡

ከዚህ በፊትም እንደሚታወሰው በአንዳርጋቸው ፅጌና በኤርትራ መንግስት ለወራት ያህል የፈንጂ ስልጠና ወስዶ ወደ ሀገር ውስጥ የገባው አበበ ወንድምአገኝ የተባለ የእንግሊዝ ዜግነት ያለው ትውልደ ኢትዮጵያዊ በድንበር በኩል ከኤርትራ የተላከለትን ፈንጂ በመጠቀም ቦሌ መድሐኒአለም አከባቢ የሽብር ጥቃት በመፈፀም በበርካታ ሰላማዊ ህዝብ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ ዝግጅት ሲያደርግ ጥር 15/2005 ከነግብረአበሮቹ እና የፈንጂ ቁሳቁሱ ጋር እጅ ከፍንጅ ከተያዘ በኋላ ፍርድ ቤት ቀርቦ ጥፋቱ ተረጋግጦ የእስር ቅጣት እንደተበየነበት ይታወቃል፡፡

አሸባሪው አበበ ወንድማገኝን ከእንግሊዝ በመመልመል ለፈንጂ ስልጠና ወደ ኤርትራ የላከው በአንዳርጋቸው ፅጌ ስር የኦፕሬሽን ሃላፊ ተብሎ የተመደበው ሻለቃ ማሙ ለማ የተባለው ሌላ የእንግሊዝ ዜግነት ያለው ትውልደ ኢትዮጵያዊ እንደነበር የሚታወቅ ነው፡፡

በሀገር ውስጥም የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገ መንግስት ባጎናፀፋቸው የመደራጀት መብት መሰረት ህጋዊ መብታቸው ተረጋግጦላቸው በሰላማዊ መንገድ ተደራጅተው በሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች ውስጥ ተሰግስገው በአሸባሪነት ከተፈረጀው ከግንቦት 7 እና የድርጅቱ ልሳን ከሆነው የኢሳት ቴሌቪዥን ጋር ግንኙነት በማድረግ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ተጠርጣሪዎችም በፍርድ ቤት ትእዛዝ ዛሬ ሐምሌ 1/2006 በቁጠጥር ስር ውለዋል፡፡

በዚህ አጋጣሚ የሌላ ሀገር ዜግነትን፣ የህጋዊ የፖለቲካ ፓርቲ አባልነትን፣ጋዜጠኝነትን እና የመሳሰሉትን በሽፋንነት በመጠቀም በሽብር ተግባር ላይ በመሳተፍ፣ ከህግ ተጠያቂነት ሊያስጥል እንደማይችል ሊታወቅ ይገባል ሲል የብሔራዊ መረጃና የደህንነት አገልግሎት እና የፌዴራል ፖሊስ የፀረ ሽብር ግብረ ሀይል አስታውቋል፡፡

********

ምንጭ፡- ኢቴቪ፣ ሐምሌ 1፣ 2006

Daniel Berhane

more recommended stories