የቀድሞ የጋምቤላ ፕሬዚዳንት ኦኬሎ ኦኳይ በሽብር ወንጀል ተከሰሱ

(ጥላሁን ካሳ)

የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ርእሰ መስተዳድር የነበሩት ኦኬሎ ኦኳይ በሽብር ወንጀል  ክስ ተመሰረተባቸው።

ተከሳሾቹ የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ርእሰ መስተዳድር የነበሩት ኢኬሎ ኦኳይ ፣ ዴቪድ ኡጁሉ፣ ኡቻን ኦፔይ ፣ ኡማን ኝክየው ፣ ኡጁሉ ቻም ፣ አታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡመድ ናቸው።

የፌደራል አቃቤ ህግ ሁሉንም  ግለሰቦች ራሱን የጋምቤላ ህዝቦች ነጻነት ንቅናቄ /ጋህነን/ እና እህት ድርጅት ነው በሚሉት የጋምቤላ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ /ጋህነን/  በተሰኙ የሽብር ቡድን ድርጅቶች ከአመራር ሰጪነት እስከ አባልነት ተሳትፎ አላቸው በሚል ነው በሽብር ወንጀል ክስ የመሰረተባቸው።

1ኛው ተከሳሽ ኦኬሎ ኦኳይ በ1996 ዓ.ም የጋምቤላ ርእሰ መስተዳድር ነበሩ።

ክሱ በወቅቱ  በክልሉ የሚገኙ የአኙዋክና የኑዌር ብሄረሰብ አባላት መካከል ግጭት ይቀሰቀሳል፣ በግጭቱም ከ 400 በላይ ሰዎች  ህይወታቸውን አጥተዋል ፤ እኚህው ርእሰ መስተዳደሩ ሃላፊነታቸውን ተጠቅመው ግጭቱ በቁጥጥር ስር ሊያውሉ ሲገባ እንዳባባሱት ይጠቅሳል።

በዚህ ብቻ አላበቁም ግጭቱን አስመልክቶ ለተለያዩ የውጭ ሃገር መገናኛ ብዙሃን የተዛባ መግለጫ መስጠታቸውና የሚሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እልቂቱን አባብሶት እንደነበርም ተጠቅሷል።

ኋላም ድርጊታቸው እንደሚያስጠይቃቸው በመረዳት  የግል አጃቢያቸውና ሾፌራቸውን እንደያዙ ጥር 1996 ሃገር ከድተው መውጣታቸውን ፣ ሃገር ቤት ሆነው እልቂቱን ያባባሰ  መግለጫቸውን መቀመጫቸውን ውጭ ሃገር ላደረጉ መገናኛ ብዙሃን መስጠት መቀጠላቸውን ክሱ አመልክቷል።

ወደ ኖርዌይም በማቅናት ጥገኝነት ካገኙና ሃገር ከድተው ከወጡ ከሶስት አመታት በኋላ ራሱን የጋምቤላ ህዝቦች ነጻነት ንቅናቄ/ጋህነን/ የተባለውን የሽብር ቡድን ለመቀላቀል በመወሰን  በወቅቱ የዚህ ሽብር ቡድን መስራችና ሊቀመንበር  ከሆነው ፒተር ካጋ ጋር በመገናኘት  የውጭ ግንኙነት ሃላፊ በመሆን ተሹመው የሽብር ቡድኑን ተልእኮ ማስፈጸም አንድ ብለው መጀመራቸውን ክሱ አትቷል።

በአውሮፓና በአሜሪካ እየተዘዋወሩ የሽብር ቡድኑን አባላት በመመልመል ፣  ከአባላቱ በወር እስከ 50 ዶላር ሰብስበዋል የሚለው በክሱ የተጠቀሰ ሌላ ጭብጥ ሲሆን ፥  ታህሳስ 2000 ዓ.ም ላይ ከድርጅቱ የሽብር አመራሮች ጋር ያደረጉት ቴሌ ኮንፈርንስም በክሱ ላይ ተጠቅሷል።

በዚሁ ዓመት ጥር ወር ላይ ጋህነን ለሁለት ሲከፈል ኦኬሎ ኦኳይ አንዱን ክንፍ መስራቹ ፒተር ካጋ ደግሞ ሁለተኛውን መያዛቸው በክሱ ተመልክቷል።

የሊቀመንበርነትን በትረ ስልጣን እንደጨበጡ ኤርትራ በመሄድ በሽብር እቅዳቸው ላይ ለ45 ቀናት ያህል ውይይት አደረጉ፤ጀርመን ሳውዲ አረቢያ እና ስዊድን በመሳሰሉ ሃገራትም በማቅናት  የሽብር ቡድኑን ለማጠናከር መከሩ ይላል ክሱ።

አሜርካም ተጉዘው በወቅቱ ከጋምቤላ  ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ /ጋዴን/  ሊቀመንበር ጆንሰን ኡጁሉ የሊቀመንበርነቱን ሃላፊነት ተረክበው ጋህነን እና ጋዴንን መርተዋል የሚለውም ተጠቅሷል።

በዚህ ሃላፊነታቸው ኡጋንዳ መጡ 860 አዳዲስ አባላትን  መልምለው ወታደራዊና ፖለቲካዊ ስልጠና እንዲያገኙ ካደረጉ በኋላ ፤ አባላቱ ከደቡብ ሱዳን አማጽያን ጋር እንዲቀላቀሉ ማስደረጋቸውም ተዘርዝሯል።

ሁለተኛው ተከሳሽ ዴቪድ ኡጁሉ የደቡብ ሱዳን ዜግነት ያለው የ36 አመት ጐልማሳ ሲሆን ፥ በሽብር ቡድኑ የደቡብ ሱዳን ሃላፊ ነው።

ከመስከረም  2005 ዓ.ም ጀምሮ ባሉት ጊዜያት አሜሪካ ሃገር  ሚኒሶታ ከተማ ለሽብር ስራው ማከናወኛ  በተለያዩ ባንኮች የሚላክለትን ገንዘብ ሲቀበል ቆይቷል ፣ የመለመላቸው አባላቱ የደቡብ ሱዳን አማጺያንን እንዲቀላቀሉ አስተባብሯል የሚለው በክሱ ላይ ተጠቅሷል።

ከእርሱ ሌላ ኦኬሎ ኢኳይን ጨምሮ ሰባቱም ተከሳሾች ከሌሎች ተመሳሳይ የሽብር  ድርጅቶች ያገኟቸውን ልዩ ልዩ የሽብር ስልጠና ተጠቅመው ፥ አንድ አስከፊ ድርጊት ሊፈጽሙ ዝጅግት በማድረግ ላይ እያሉ ነው በደቡብ ሱዳን የጸጥታ ሃይሎች የተያዙት።

በጋምቤላ ክልል ወርቅ በሚቆፈርባቸው የዲማ እና ጆር የተሰኙ ወረዳዎች ላይ በማቅናት ፤ በወርቅ ቁፋሮ ላይ የተሰማሩ በርካታ ወጣቶችን በማፈን የደቡብ ሱዳን አማጺ መሪ ዴቭድ ያውያው ስልጠና በሚሰጥበት ቦታ በማምጣት፣  ሰልጥነው የሽብር ቡድኑን እንዲቀላቀሉ የማድረግ  አላማ እንደነበራቸው  በክሱ ላይ ተመልክቷል።።

ይህንን ምክራቸውን ጠንስሰው ወደ ኢትዮዽያ መጥተው ተግባራዊ ለማድረግ ሲዘጋጁ ድንገት የኢትዮዽያ መንግስት ከደቡብ ሱIዳን ጋር ባለው የጋራ የጸጥታ ስራ ቅንጅት በቁጥጥር ስር ውለዋል ፤ ዛሬ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤተ 4ኛ የወንጀል ችሎት ቀርበውም  ክሱ ተነቦላቸዋል።

የአማርኛ ቋንቋ ለማይናገሩት በአስተርጓሚ እንዲረዱት የተደረገ ሲሆን ፥ መንግስት ጠበቃ ያቁምልን በማለታቸውም ችሎቱን አቤቱታቸውን ተቀብሏል።

የተጠቀሰባቸው የህግ አንቀጽ ዋስትና የሚከለክል በመሆኑ ፥ ከሚመደብላቸወ ጠበቀ ጋር ተመካክረው የክስ መቃወሚያ እንዲያቀርቡ ችሎቱ  ሰኔ 24 2006ን ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።

*******

ምንጭ፡- ፋና – ሰኔ 5፣ 2006 – ርዕስ “የቀድሞው የጋምቤላ ርእሰ መስተዳድር ኦኬሎ ኦኳይ በሽብር ወንጀል ተከሰሱ”.

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories