የህዳሴው ግድብ ድርድር ማርሽ መቀየሪያ ሰዓቱ አሁን ነው!

የግብፆቹ የክርክር ድርቅና ትንሽ ወረደብኝ። መልስ ባገኘና ሃገር ባወቀው ሃቅ ለመነታረክ ጊዜ መስጠት ልክ በአንድ ማርሽ የተለያየ ተዳፋትን በአንድ ፍጥነት ለማለፍ እንደመታገል አይነት ሹፍርና ይመሰልብኛል። ሞተር ማበላሸት ነው። ሃገራችንን ያስንቃል፤ የእነርሱንም የዲፕሎማሲ ድንቁርና እንደመውረስ ይቆጠራል።

ግድቡ ትልቅ ስለሆነ ጸንቶ አይቆምም፤ የመሬት መናወጥ ክልል ውስጥ ስለሆነ መሰራት የለበትም፤ … ሲሉ ላምናቸው ተቃርቤ የአለማቀፍ ባለሙያዎችን ቡድን ምስክርነትና ሌሎችንም መረጃዎች ስቃርም ከረምኩ። የመሰረቱን አለትነት ሲቆፈር ባለሙያዎቹም እኛም አየን። እንኳን የእኛ አለት የእነርሱም የበረሃ አሸዋ አስዋንን ለዘመናት ተሸክሞ ኖርዋል። እንኳን የእኛ ዘመን በፈጠረው ልዩ ቴክኖሎጂ የሚገነባ ኮንክሪት ሙሌት ቀርቶ የነርሱም ድንጋይና አሸዋ በዛ ዘመን ባለፈበት ተክኖሎጂ ተጠቅጥቆ ይሄው ጥቁር አባይና ነጭ አባይን ገድቦ ኖርዋል። የባለሙያዎች ቡድኑም ይህንን ከግምት አስገብቶና አወዳድሮ ግድቡ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ መሆኑን መሰከረ። በቃ የዚህ ስጋት በዚህ አበቃ። የምን ‘የደንቆሮ ለቅሶ መልሶ መልሶ’ ነው።

የሚቀጥለው ነገር ሶስቱንም ሃገሮች ያሳተፈ የማህበራዊና ተፈጥሮአዊ አዋጭነት ይሰራ ነው። ይህንን እኛም በሚገባ ሰርተን የራሳቸውን ስራ ደግሞ እራሳቸው እንዲወጡ መስጠት ነው። ይህ ጥናት ግን የማህበራዊና ተፈጥሮአዊ ተፅእኖ ብቻ አይደለም መያዝ ያለበት፤ የማህበራዊና ተፈጥሮአዊ አዋጭነትም ጭምር እንጂ። ተፅእኖ እና አዋጭነት ልዩነት አለቸው። አዋጭነት ውጪያዊ ጠቀሜታን (Externalities in economists term) ከሂሳብ ውስጥ ያስገባልና ግንፅና ሱዳን ለሚያገኙት ተጨማሪ ጠቀሜታ መክፈል እንዳለባቸው ከነክፍያው ጭምር ይዘረዝራልና።

እንኳን ግድባችንን በቦንብ ሊነኩዋት ቀርቶ  በነርሱ ተንኮል የተነሳ እነርሱ ያገኙትን አለማቀፍ ድጋፍ አጥተን ከልጆቻችን አፍ ዳቦ ነጥቀን በምንገድበው ግድብ ለሚያገኙት ተጨማሪ ጥቅም የማናስከፍል ቂሎች እንዳይደለን መንግስታችን ከሚያሳየው እልህ አስጨራሽ ትእግስቱ ጎን በማክበር በሚመለከታቸው በኩል ሊነግርልን የሚገባበት ጊዜ አሁን ነው። ይህንን ህዝባዊና የመከባበር አቤቱታ ህዝቡ በሃገር ውስጥም ሆነ በውጪ ድምፁን ለአለማቀፍ ህብረተሰብ የሚገልፅበት መድረክ መዘጋጀትም ግድ የሚልበት ወቅት አሁን ነው። ከግብፅ ተወካዮች (መንግስት ባይሆኑም) ለዘረጋንላቸው የፍቅር እጅ ከሚገባው በላይ የንቀት መልስ አግኝተናልና። ጊዜው አሁን ነው ያልኩት የህዝባዊ ዲፕሎማሲ የማርሽ ለውጣችን የግብፅ ህዝብ ለሚመሰርተው መንግስትም ሆነ ለአለማቀፍ አማካሪዎቹ ልብ የሚደርስ መልእክት ስለሚያስተላልፍልን ነው። በተረፈ የመከላከያ ኢንተለጀንስ መዋቅራችን ደረታቸውን ነፍተው ከቆሙልን ተራሮችም ሆነ ለመከላከል በተፈጥሮ ከተቆፈሩልን ሸንተረሮች የልምምድ አድማሱን ማሳደግ አለበት። እኛም ግብፆች ባንሆንም ኢትዮጵያውያኖች ነና። አልበዛም እንዴ!

ከላይ ስለግድባችን ዘመናዊነትና ጥንካሬ ከነርሱው አስዋን ጋር በማወዳደር ባጭሩ የምታውቁትን ሃቅ ለመናገር ሞክሬያለሁ። አሁን ደግሞ ከማስታወሻዬ ባጭሩ የራበው ሆዳችንን አስረን፣ የልጆቻችንን የልጅነት ፍላጎት ሆድ የሚያባባ ጥያቄ ታግሰን የምንገነባው ግድብ ለነዚህ ለሚያሾፉብን ጎረቤቶች የሚሰጠውን እልቆ መሳፍርት ጥቅም እኔ የማውቀውን ብቻ ትንሽ ልንገራችሁ። ተፈጥሮ እነርሱን በእኛ ቦታ አስቀምጣቸው ቢሆን እንዴት እንደሚያሽቆጠቁጡን ልብ በሉኝ። ‘በእጅ የያዙት ወርቅ’ እንደሚባል የሚከተሉትን እውነታዎች ይዘን ነው በድርድሩ እያዘገምንና የግንባታ ሞተራችንን ጥርስ እየበላን ያለነው። ለዚህም ነው ድርድሩ ማርሹን ይቀይር፤ የግንባታ ሞተራችንን በወረድ ፍጥነት አናበላሸው ለማለት የተነሳሁት።

**********

Sisay Demeku

more recommended stories