የህዳሴ ግድብ ውሀ ለሚተኛበት ስፍራ ደን የማንሳት ሥራ ተጀመረ

ውሃው የሚተኛበትን ሥፍራ የማዘጋጀቱ ሂደት ከአጠቃላይ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ መርሃግብር ውስጥ ወሳኝ ምዕራፍ ተደርጐ የሚቆጠር ነው፤

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሲጠናቀቅ የግድቡ ውሃው በሚተኛበት ስፍራ የሚገኘውን የተፈጥሮ ደን የማንሳት ሥራ መጀመሩን የግድቡ ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ገለጹ፡፡

የተፈጥሮ ደኑ ውሃው ከሚተኛበት ቦታ መነሳቱ የግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ለአገልግሎት ሲበቃ ሊከሰት የሚችለውን የውሃ ትነት ያስቀራል፡፡

ኢንጂነር ስመኘው እንዳሉት፤ በአሁኑ ወቅት በስፍራ የሚገኘው የተፈጥሮ ደን በሰው ሃይልና በማሽን በመታገዝ የማንሳቱ ስራ በመካሄድ ላይ ነው፡፡

ከስፍራው የሚነሳው የተፈጥሮ ደን እንጨት በእንፋሎት መልክ ወደ ኤሌክትሪክ በመቀየር ለግድቡ አካባቢ ተጨማሪ የኤሌክትሪክ ግብዓት እንደሚውል አስረድተዋል፡፡

ይኸው ስራ እየተከናወነ የሚገኘው ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር በመቀናጀት እንደሆነም ገልጸዋል ፡፡

የግድቡ ውሃ የሚተኛበት ቦታ 1ሺ 680 ካሬ ኪሎ ሜትር ሲሆን፤ ከዋናው ሃይል ማመንጫው ክፍል ወደኋላ 248 ኪሎ ሜትር ርዝመት እንደሚኖረው የግድቡ ዲዛይን ያሳያል ፡፡

የግድቡ ውሃ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኙ የጉባ፣ ሸርቆሌ፣ ማንዱራና ወምበራ ወረዳዎች የተወሰኑ አካባቢዎችን እንደሚሸፍን ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ይገልጻሉ ፡፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታው ሲጠናቀቅ ኤሌክትሪክ ከማመንጨት ባሻገር የዓሣ ምርትን ጨምሮ ለተለያየ ኢንቨስትመንት ፣ለምርምር ፣ለትራንስፖርትና የቱሪስት ማእከል እንደሚሆን ይጠበቃል ብለዋል፡፡

ከተጀመረ ሶስት ዓመታት ያህል ያስቆጠረው የህዳሴው ግድብ ጠቅላላ የአርማታ ሙሌት መጠን 10 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሜትር ኩዩብ ነው ፡፡

የግድቡ ግንባታ ሲጠናቀቅ 145 ሜትር ከፍታና 1ሺ780 ሜትር ርዝመት ይኖረዋል ፡፡

እንዲሁም 63 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ ወይም የጣናን ሃይቅ ሁለት እጥፍ ያህል መጠን እንደሚኖረው ይጠበቃል፡፡

6ሺ ሜጋ ዋት ኤሌክትሪክ የሚያመነጨው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በታላቅነቱ ከአፍሪካ አንደኛ ከዓለም ሰባተኛ ደረጃ ይይዛል ፡፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የመሰረት ድንጋይ የተጣለበት ሶስተኛው አመት መጋቢት 24/2006 ዓ.ም ይከበራል፡፡

*******

ምንጭ፡- አዲስ ዘመን፣ መጋቢት 3/2006 ‹‹ለህዳሴው ግድብ ውሃ በሚተኛበት ስፍራ ላይ ደን የማንሳት ሥራ ተጀመረ››

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories