የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት 56 በመቶ ተጠናቀቀ

የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት ግንባታ 56 በመቶ መጠናቀቁን የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ።

የ7ኛው አገር አቀፍ የከተማ ልማት፣ ቤቶችና ኮንስትራክሽን ዘርፍ ጉባኤ ተሳታፊዎች ፕሮጀክቱን ጎብኝተዋል።

በኮርፖሬሽኑ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር በሃይሉ ስንታየሁ እንደገለጹት የሰራው ዋና ዋና የሚባሉት ሰራዎች በመጠናቀቅ ላይ ሲሆኑ ግንባታውም በጥሩ እንቅስቃሴ ላይ ይገኛል።

ከባድ ከሚባሉት ስራዎች ባቡሩ በመሬት ውስጥ ለውስጥና በድልድይ ላይ የሚሄድበትን ግንባታ ማከናወን ሲሆን በመሬት ውስጥ ለውስጥ የሚሄድበት ተጠናቋል። አሁን የፌርማታ ስራ እየተከናወነ ሲሆን እሱም መጪው ክረምት ከመግባቱ በፊት የሚጠናቀቅ ይሆናል ብለዋል።

እንደ ኢንጂነር በሃይሉ ባቡሩ በድልድይ የሚሄድበት በተለይ  ከመስቀል አደባባይ እስከ ኮካ ኮላ ያለው ዋናው ክፍል ግንባታ ተጠናቋል።

ከአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ጋር በቅንጅት የሚሰሩ የሜክሲኮ፣ልደታና ቄራ ቦታዎች በተወሰነ መልኩ የመዘግየት አዝማሚያ የነበረ ቢሆንም በአሁን ወቅት ሙሉ በሙሉ ወደ ግንባታ ተገብቶ በመፋጠን ላይ ይገኛል።

እነዚህ ግንባታዎች ሲጠናቀቁም ድልድይ የመደርደሩ ሰራ እንደሚጀመር ጨምረው ገልፀዋል።

የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት 39 የመንገደኞች መሳፈሪያና መውረጃ ፌርማታዎች የሚኖሩት ሲሆን በፌርማታዎቹ መካከል የሚኖረው አማካይ ርቀትም እስከ 700 ሜትር ይደርሳል።

ፕሮጀክቱን ከጎበኙት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው አቶ ማሪያ ወልደ ሚካኤልና አቶ እንድሪስ ኤዶ የተባሉ  ተሳታፊዎች  እንዳሉት የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት የከተማይቱ ብሎም የሃገሪቱ ዕድገት አንዱ ማሳያ ነው፤ በግንባታው ሂደትና አጠቃላይ ባዩት ነገርም መደሰታቸውን ገልጸዋል።        

*******

ምንጭ፡- ኢዜአ፣ መጋቢት 4/2006፣ ‹‹የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት 56 በመቶ ተጠናቀቀ››

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories