(ፍቃዱ ፈንቴ)
አክራሪዎች በእምነት ስም የህዝብን ሰላም ለማደፍረስ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ በመቃወም እሁድ ነሃሴ 26/2005 ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርግ የአዲስ አበባ የሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ገለፀ፡፡
ሰልፉ ሁሉም የሀይማኖት ተከታዮች በሰላም አብሮ ለመኖር ያላቸውን ቁርጠኝነት ማሳያ ነው ተብሏል፡፡
ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ በእምነት ስም የሀገሪቱን ሰላም ለማደፍረስ ጥረት የሚያደርጉ አካላትን በመቃወም በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በተደጋጋሚ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ የሚታወስ ነው፡፡
በ10ሩም ክፍለ ከተሞች ውይይት ያደረጉት ነዋሪዎቹ በእምነት ስም የሚደረግ ማንኛውም የአክራሪነት እንቅስቃሴ በመቃዎም ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ እንደሚፈልጉ ለመንግስት ጥያቄ ማቅረባቸውን የአዲስ አበባ የሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጽ/ቤት ገልጿል፡፡
የሁሉም ሀይማኖት ተከታዩች በተገኙበት የሚካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ የሀይማኖት ተከታዮቹ አብሮ በሰላም ለመኖር ያላቸውን ቁርጠኝነት ማሳያ መሆኑን የአዲስ አበባ የሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጽ/ቤት ቦርድ ሰብሳቢ ርዕሰ ደብር በርሁን አርአያ ገልጸዋል፡፡
የሀይማኖት እኩልነት ባልተከበረበት ወቅት ጭምር ህዝቡ ጠብቆ ያቆየውን የመቻቻልና የአብሮነት እሴት ጥቂት አክራሪዎች ለማደፍረስ መሯሯጣቸውን ለመቃወም ሁሉም የሀይማኖት ተከታዮች በዕለቱ እንደሚሳተፉ ርዕሰ ደብር በርሁን አርአያ ጠቁመዋል፡፡
እሁድ 26/2005 በሚካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ የሁሉም ቤተ እምነት መሪዎች እና ተከታዮቻቸው የሰላም መልእክቶችን በመያዝ ከየአቅጣጫው ወደ መስቀል አደባባይ ያመራሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
**********
Source: Aug. 26, 2013 – titled “የአክራሪዎችን እንቅስቃሴ በመቃወም በአዲስ አበባ ሰላማዊ ሰልፍ ሊካሄድ ነው”