ግምገማ:- የግርማ ሰይፉ መጽሐፍ “የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?”

(በየማነ ናግሽ)

ፍርኃታችን ልክ አይደለም፡፡ ኢሕአዴግ ሁለትና ሦስት በመቶ እያስፈራራን እኛ ግን 95 እና 96 በመቶ እየፈራን ነው፤›› ሲሉ በደጋፊዎቻቸው ጭብጨባ ታጅበው ነበር፡፡ ‹‹አዎ ፈሪዎች ነን›› የሚለውን አባባላቸውን ማረጋገጥ እስኪመስል ድረስ ጭብጨባው ቀጥሎ ነበር፡፡

በአሁኑ ወቅት ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ (መድረክ – አንድነት) የፓርላማ አባል አቶ ግርማ ሰይፉ ‹‹የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?›› የሚለውን መጽሐፋቸውን ባስመረቁበት ጊዜ ነበር ይህንን ያሉት፡፡

ምርቃቱ ባለፈው ሐሙስ ሐምሌ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አዳራሽ በርከት ያሉ ታዳሚዎች፣ የአንድነት ፓርቲ አመራሮችንና ጋዜጠኞችን በአንድ ላይ አሰባስቧል፡፡ ‹‹የሚሊዮን ድምፅ ለነፃነት›› በሚል መፈክር ለሦስት ወራት የታቀደው የተቃውሞ ሰላማዊ ሠልፍ ሒደት በጎንደርና በደሴ ተጀምሮ እየተካሄደ ባለበት ወቅት ነው ይኼው ሥራ ለሕዝብ የቀረበው፡፡ የመጽሐፉንና የሠልፉን ስያሜ ጥሪ ያመሳሰላቸው ሁለቱም በነፃነት ዙሪያ የሚያጠነጥኑ መሆናቸው ብቻ አይደለም፡፡ በተመሳሳይ ወቅት መከናወናቸው ብቻም አይደለም፡፡ የተቃውሞ ዕቅዱ ይፋ የሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ፍትሕ ፓርቲ ሲሆን፣ ‹‹የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?›› መጽሐፍ ደራሲም የፓርቲው ከፍተኛ አመራርና የፓርላማ አባል መሆናቸው ጭምር ነው፡፡

‹‹ፍርኃትን እንፍራ››

‹‹የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?›› የሚለውን ርዕስ አግባባነት በብዙዎች ሲነሳ ተስተውሏል፡፡ ‹‹ምን ማለት ነው? ነፃነት በዋጋ ይተመናል እንዴ?››፣ ‹‹ነፃ ወጪና ነፃ አውጪ ማን ነው? ከማንስ ነው ነፃ የሚወጣው?›› በሚል በርከት ያሉ አንባቢዎች እየጠየቁ ነው፡፡ ጸሐፊው ለሥራቸው ርዕሱ ስለተመረጠበት አኳኋንና ስለጉዳዩ ይዘት ለመዘርዘር ሞክረዋል፡፡ ‹‹ፍርኃትን እንፍራ›› የሚሉትን በመጽሐፉ ሽፋን ላይ ተደጋግመው በተሰካኩ ቃላት ለማሳየት እንደሞከሩት፣ እዚህ አገር ዜጎች በተጋነነ ፍርኃት ውስጥ እየኖሩ መሆናቸውን በመልዕክታቸው ማስተላለፍ የፈለጉ ይመስላል፡፡

በመጽሐፋቸው ምርቃት ወቅት ባደረጉት ንግግር እንደ መግቢያ የተጠቀሙበት፣ ‹‹እዚህ የተሰባሰባችሁ በሙሉ ጀግኖች ናችሁ›› በማለት የመጽሐፋቸውን ርዕስ የመረጡት በምርጫ 2002 ብቸኛ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ሆነው ፓርላማ የተቀላቀሉ ጊዜ እንደሆነ ተናግረው፣ ‹‹የመረጥኩት ርዕስ ትክክለኛ መሆኑ የገባኝ ግን አሁን መጽሐፉን ለማስመረቅ እንቅስቃሴ በጀመርኩበት ጊዜ ነው፤›› ብለዋል፡፡Ethiopian opposition MP - Girma Seifu Maru

በመጽሐፋቸው በተለያዩ አገላለጾች የኢትዮጵያ ሕዝብ ምን ያህል የፖለቲካ ፍርኃት ውስጥ እየኖረ እንደሆነ ለማሳየት የሞከሩ ቢሆንም፣ ‹‹የተጠቀምኩት ርዕስ ትክክለኛ መሆኑ የገባኝ አሁን ነው፤›› ያሉበት ምክንያት ግን መጽሐፋቸውን ለማስመረቅ ሲንቀሳቀሱ በገጠማቸው ውጣ ውረድ ምክንያት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

አንዳንድ ድርጅቶችና ግለሰቦች መጽሐፉን ለማስመረቅ ከተስማሙ በኋላ ይዘቱንና ጸሐፊው ራሳቸው ግርማ ሰይፉ መሆናቸውን ሲያውቁ መሸሻቸውን ይናገራሉ፡፡ በመጨረሻ ‹‹በአንድ ስልክ ጥሪ ተፈቀደልኝ›› ያሉት የመንግሥት አዳራሽ መነሻ፣ የፍርኃት ምንጮች ታች ያሉት የኢሕአዴግ ካድሬዎች መሆናቸውን፣ ዜጎች ራሳቸው በአዕምሮአቸው በሚፈጥሩት ከመጠን ባለፈ ፍርኃት እንደሚወራቸው ማሳያ አድርገው አቅርበውታል፡፡ ‹‹እዚህ የተሰባሰባችሁ በሙሉ ጀግኖች ናችሁ›› ያሉበት ምክንያትም በየቤታቸው ሆነው ተደብቀው መጽሐፉን ለማንበብ የተዘጋጁ መኖራቸውን፣ በምርቃቱ ዕለት እርሳቸው የሚሉትን ለመስማት በፍርኃት ምክንያት መምጣት አለመቻላቸውን በመናገር ነው፡፡ ‹‹የፈሪዎችን ትብብር እንጂ የአስፈራሪዎችን ትብብር የሚጠይቅ አይመስለኝም፡፡ ከዚህ ዘግናኝ ፍርኃት መውጣት አለብን፤›› ሲሉ ንግግራቸውን ቀጥለዋል፡፡

ይዞታቸው ምንም ይሁን ምን በአሁኑ ወቅት ሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥትና ባለሥልጣናት የሚያወድሱ የተለያዩ ‹‹ውድ ሰዎች›› ሊሰኙ የሚችሉ መጻሕፍት በመንግሥት መሥሪያ ቤቶችና በገዥው ፓርቲ ኩባንያዎች ዳጐስ ያለ ስፖንሰርነት ለገበያ እየቀረቡ ነው፡፡ ከጸሐፊው ጀምሮ በዚሁ መድረክ የተንፀባረቁ አስተያየቶችም እንዲሁ ነበሩ፡፡ ዜጎች ‹‹ከዘግናኝ ፍርኃት›› ውስጥ ራሳቸውን ነፃ እንዲያወጡ የጠየቁት ግን እንዲህ መንግሥት በመቃወም የመንግሥትን ሥርዓት በመተቸትና ገዥውን ፓርቲ በመውቀስ የሚቀርቡ ሥራዎች ወደ ሕዝብ ለማቅረብ ምን ያህል እጅ አዙር የሆነ ‹‹ሳንሱር›› ሊሰኝ የሚችል ሁኔታ መኖሩን በመጥቀስ ነው፡፡ ጸሐፊው የተጋነነና ከመጠን በላይ ያለፈ ምክንያት አልባ ፍርኃት ያለ ቢመስልም፣ ‹‹ከየት የመነጨ ይሆን?›› ብሎ ለሚጠይቅ በአጠቃላይ የአገሪቱ ሥርዓት አሁንም ‹‹ከፖለቲካና ከኮረንቲ›› የተላቀቀ እንዳልሆነ አመላካች ነው ብለዋል፡፡

አቶ ግርማ ስለዚህ ጉዳይ በገጽ 62 ላይ እንዲህ ሲሉ አስፍረውታል፡፡ ‹‹በገበያ ሕግ መሸጥ ሲባል ዕቃውን ወይም አገልግሎት የሚሰጥ ሰው ገንዘብ ወይም ሌላ ተመጣጣኝ ዋጋ ያለው ነገር ተከፍሎት ነው፡፡ አሁን አሁን ይህን መደበኛ የገበያ ሕግ በሚፃረር መልኩ ውድ የሆነውን (ለገበያ መቅረብ የሌለበትን) ነፃነት ተከፍሎት ሳይሆን ከፍለን እየሸጥን እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ይህን ቅጥ ያጣ፣ የግብይት ሕግን የጣሰ የነፃነት መቸብቸብ ገበያ ሳስበው ነፃነት ዋጋው ስንት ነው? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፤›› ብለው፣ ‹‹ነፃነትታችንን አሳልፈን ሰጥተናል›› የሚለውን እምነታቸውን ጸሐፊው ከቤተሰባቸው ጀምሮ እስከ መሥሪያ ቤት አካባቢ እጅግ ነግሦ የሚገኘው ፍርኃትን በማስረጃነት ለማሳየት ይሞክራሉ፡፡

ምርጫ 2002 እንደ መነሻ

በአራት ክፍሎች የተደራጀው ‹‹የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?›› መጽሐፍ የጸሐፊው የፖለቲካ አጀማመርና ተሳትፎ ከ1997 ዓ.ም. ምርጫ ጀምሮ የሚያስቃኝ ሲሆን፣ በአራት ዋና ዋና ክፍሎችና በ19 ምዕራፎች የተደራጀ ነው፡፡ አቶ ግርማ ከራሳቸው የፖለቲካ እንቅስቃሴና ተሳትፎ ባሻገር ቅንጅት ውስጥ የነበሩ የአንዳንድ መሪዎች ሴራዎች፣ የመንግሥት አፈናዎች፣ የምርጫ 2002 ድባብና ከዚያ በኋላ እየባሰበት መጣ ያሉት ‹‹ዘግናኝ ፍርኃትን›› በተመለከተ ሸፍነዋል፡፡ በመጨረሻ የራሳቸውን ግላዊ የፖለቲካ ርዕዮት ያከሉበት ይኼው መጽሐፍ በተለይ በምርጫ 97 ማግስት የቅንጅት የፓርላማ ‹‹መግባት አለመግባት›› እና ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳን በተመለከተ የራሳቸውን አቋም ለማሳየት ሞክረዋል፡፡

‹‹የኢሕአዴግ መካሪ›› ያሉት ሪፖርተር ጋዜጣን ጨምሮ የተለያዩ ወገኖች ቅንጅት ያገኘውን የፓርላማ ወንበርና የአዲስ አበባን አስተዳደር መረከብ ነበረበት የሚለው አስተሳሰብ የተሳሳተ መሆኑን እንደሚያምኑበት አንፀባርቀዋል፡፡ በወቅቱ (97) ዕጩ ተወዳዳሪ ሆነው እንዳይቀርቡ በአንዳንድ የቅንጅት አመራሮች ‹‹ተፈጸመብን›› ባሉት ሴራ ምክንያት የድርጅቱ የላዕላይ ምክር ቤት አባል ያልነበሩ አቶ ግርማ ‹‹ቅንጅት ምራኝ ብሎ የመረጠውን ሕዝብ ተመልሶ እንዴት ልምራችሁ? ብሎ ሊጠይቅ ወደ ሕዝብ ወረደ?›› የሚለውን ወቀሳ ይከላከላሉ፡፡

ይህ አቶ ልደቱ አያሌውን ጨምሮ የተለያዩ የቀድሞ ቅንጅት አንጋፋ አመራሮች እንደ ትልቅ ስህተት የተቀበሉትን ነበር አቶ ግርማ ‹‹ስህተት አልነበረም›› በሚል ክርክር ውስጥ የገቡት፡፡ ‹‹ፓርላማ እንግባ ወይ?›› ብሎ ሕዝብን መልሶ ማወያየትን ብቻም አይደለም የደገፉት፡፡ ቅንጅት ‹‹ፓርላማ አልገባም›› ያለበት ወቅት እንዳልነበረ አቋም ይዘዋል፡፡ ይህ በአቶ ልደቱ አያሌው ‹‹መድሎት›› በዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ‹‹የነፃነት ጎሕ ሲቀድ›› እና ሌሎች በቅንጅት ዙሪያ በተጻፉት ብዙ የተባለበት ቢሆንም፣ አቶ ግርማ በወቅቱ ከፍተኛ አመራሮች የነበሩትን በማነጋገርና ሁኔታውን በውል ለመገንዘብና ለመተንተን ጥረት ያደረጉ አይመስልም፡፡ ‹‹የአዲስ አበባ ምክር ቤትም ሆነ የፌዴራል ፓርላማ አልገባም፤›› አላለም ያሉት መንግሥት በሚቆጣጠረው ሚዲያ በተሳሳተ ዘገባ መሆኑን ከመግለጽ ውጪ፣ ድርጅቱ የመረጠኝ ሕዝብ አትግባ ብሎኛል በሚል ለመግባት የወሰነውን ውሳኔ በግልጽ ማሳየት አልቻሉም፡፡ ይህ የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ ወደኋላ እንዳይጎተት ተደርጎ በስፋት የሚታመንበት ዕርምጃ እንዳይደገም ከመስበክ ይልቅ በመከላከል ላይ መቆማቸውን አንዳንድ አንባቢዎች እንዲታረም ይጠይቃሉ፡፡ ‹‹አሁን የውሸት ቃላት በመደርደር ወይም እንደ አዲስ እንዲህ አልነበረም በሚል ስህተት አይስተካከልም፤››ም ይላሉ፡፡

የመጽሐፉ ጥንካሬና ድክመት

የመጽሐፉ አቀራረብ በርካታ መልካም ጎኖች ይዟል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ከዚህ በላይ መተንተን የሚያስፈልገው ቢሆንም፣ የመጽሐፉ ዋና ይዘት የሆነውን ‹‹ከፍርኃት ነፃ የመውጣት ጥሪ›› መንግሥት ከሚወስደው አፈና በላይ ኅብረተሰቡ ራሱ ከፈጠረው ብዥታና አመለካከት የመነጨ መሆኑን ለማሳየት ተሞክሯል፡፡ ትረካው ግን በአንዳንድ መሪዎች ላይ ያነጣጠረም ይመስላል፡፡ በተለይ በአቶ ልደቱ አያሌውና በዶ/ር ዓለማየሁ አረዳ ላይ ምክንያት እየፈለገ መውቀስ ይታይበታል፡፡ ከርዕሱ አንፃር ቀጥተኛ የፖለቲካ ጠቀሜታ የሌላቸው ቤተሰባዊ ትረካዎችና የሃይማኖት ጥቅሶችም ይበዙበታል፡፡ ‹‹አደናገሪ የኢሕአዴግ ቃላቶች›› ያሉዋቸውን ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነትና›› ‹‹የዜሮ ድምር ፖለቲካ›› በመንግሥት ባለሥልጣናትና ተቋማት ብቻ የሚፈጸሙ አድርጎ ማቅረብ ራሳቸው አንዳንድ ቦታ ላይ በተቃዋሚዎች ይፈጸማሉ ካሉዋቸው ሴራዎችና ያልተገቡ አሠራሮች የሚጋጭ ነው፡፡ ለምሳሌ ‹‹ተቃዋሚዎች አንዳንድ ግለሰቦች በውጭ አገሮች የፖለቲካ ጥገኝነት ለማስገኘት የተቋቋሙ እስኪመስሉ›› በሚል ያቀረቡት ሐሳብ ለዚህ ጥሩ ማስረጃ ነው፡፡ ከዚህ የበለጠ ኪራይ ሰብሳቢነት ምን አለ? ያስብላል፡፡

ድርጅቱ በወቅቱ የተከተለውንና ብዙዎች እንደ አደገኛ አዝማሚያ የተመለከቱትን አካሄድም አልመረመሩም፡፡ በራሳቸው ላይ ተፈጸመ ያሉትን ሴራ፣ በአጠቃላይ ተቋማዊ አሠራሩ እንዳልነበርና በሌሎችም እንዳልተፈጸመም ማሳየትም አልቻሉም፡፡ ከራሳቸው ተነስተው ተቋማዊና ፖለቲካዊ ስህተቶችን አልመረመሩም ተብለው ይተቻሉ፡፡

በአባል ፓርቲዎች መካከል አንድም የፖለቲካ አንድነት አለመኖሩ፣ ሁለትም በመሪዎች መካከል የታየውን ከፍተኛ የሥልጣን ጥመኝነትና በአጠቃላይ የድርጅቱ ህልውና ላይ ያደረሰውን ጉዳት አልመረመሩም ያስብላል፡፡

በ1997 ዓ.ም. ለተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ መንስዔ የኢሕአዴግ ተቃዋሚዎችን የማዳከም ስትራቴጂ (ገጽ 59) ብቻውን የተመለከቱት ይመስላል፡፡ ለቅንጅት መፍረስ የመሪዎች ቁርጠኝነት ማጣት፣ የእርስ በርስ ፉክክርና ንትርክ ቡድንተኛ አስተሳሰብንም አልተመለከቱም፡፡ የገዥው ፓርቲ ስትራቴጂ አስፈጻሚ ኢቲቪ ነው ለሚለው ማረጋገጫ አንዱ በአንድነት መሪዎች መካከል የተፈጠረውን ድብድብ መዘገቡን ሲተቹም፣ የመሪዎችን ዲሲፕሊን ማጣት ግን አልተመለከቱም፣ አልተቹም፡፡ ‹‹ስሜታችንን መቆጣጠር አቅቶን ድብድብ ውስጥ ገባን፡፡ ኢቲቪ ይህንን ቀርፆ ለሕዝብ በማቅረብ ተመልከቱ አገር ሊመሩ ቀርቶ እርስ በርስ አይስማሙም፤›› ብሎ መዘገቡን የተቹበትን ምክንያት ግልጽ አላደረጉም፡፡ እንደ አንዳንድ ገለልተኛ ተንታኞች ምልከታ፣ የተቃዋሚ መሪዎች በሥልጣን ጥመኝነት የተጠመዱ፣ የፀና አቋም የሌላቸውና ግልጽ የሆነ የማታገያ ስትራቴጂ የሌላቸው ናቸው፡፡

በ2002 ምርጫ በመድረክ በኩል ታዩ ያሉዋቸውን ድክመቶች በባሰ ሁኔታ በ1997 ዓ.ም. አለመፈጸማቸውን አላሳዩም፡፡ በምርጫ 2002 መድረክ ለምርጫ ቅስቀሳ የሚውል የገንዘብ ድጋፍ በማሰባሰብ ረገድ በቤተሰብ፣ በቤተ ዘመድና በጓደኝነት ላይ ያተኮረ እንደነበር ጸሐፊው (ገጽ 73 – 86) ያሰፈሩ ሲሆን፣ ይህ የጠራ የፖለቲካ ፕሮግራም ይዞ በምክንያትነት ደጋፊን መፍጠር አለመቻሉን አመላካች ነው፡፡ ምናልባትም ሕዝቡ ተቃዋሚዎችን የማይደግፈው ‹‹በአደገኛ ፍርኃት ውስጥ ስለገባ ነው›› ለሚለው ድምዳሜያቸው ምንጩ ‹‹የኢሕአዴግ የማስፈራራት ስልት›› ብቻ ስለመሆኑም አጠራጣሪ ያደርገዋል፡፡ ሕዝቡ የትግል ፅናት በሌላቸው ተቃዋሚዎች ላይ ተስፋ ቆርጦ ስላለመሆኑስ በምን እርግጠኛ መሆን ይቻላል?

ያላነበቡ ገምጋሚዎች

ለገዥው ፓርቲ ቅርበት ያላቸው ግለሰቦች በስፖንሰርነት በሽበሽ መጻሕፍት እንደሚያመርቱ ሁሉ በተቃውሞ አካባቢ ያሉ ጸሐፊዎችም የምርቃት ሥነ ሥርዓቶች የፖለቲካ መቀስቀሻ መናኸሪያ እየመሰሉ ናቸው፡፡ ይህንን መጽሐፍ የገመገሙት ዶ/ር ኃይሉ አርዓያና ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ናቸው፡፡ ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ ምልከታቸውንና የመጽሐፉን ይዘት በአግባቡ ያስቀመጡ ሲሆን፣ በተለይ ጸሐፊው በተደራረቡ ኃላፊነት ተወጥረው ይህንን ሥራ ማበርከታቸውን አድንቀዋል፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝም ከ1983 ዓ.ም. በኋላ ‹‹በነፍጥ የመጣ›› ያለውን ሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት ሲወቅስ ‹‹ነፃነት በልመና፣ መግለጫ በማውጣትና መጽሐፍ በማስመረቅ አይገኝም፤›› በሚል በጭብጨባ የታጀበ ንግግር ጀምሮ ስለመጽሐፉ አስተያየት ሰጥቷል፡፡ ‹‹በእንዲህ ዓይነት ትግል ለውጥ አይመጣም፡፡ ተቃዋሚዎች ለመሞት እንጂ ለመግደል የተዘጋጁ አይደሉም፡፡ እኛ የምንመክረው ኢሕአዴግን እንጂ ተቃዋሚዎችን አይደለም፤›› ብሎ ‹‹ከሰሜን አፍሪካ የዲሞክራሲ ንቅናቄ ልንማር ይገባል፤›› በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

‹‹ከዚህ መጽሐፍ መገንዘብ እንደሚቻለው ቀጣዮቹ ምርጫዎች ዋጋ የላቸውም፤›› በማለት፣ ‹‹በ2006 ዓ.ም. ተቃዋሚዎችን ከውጭ ሆነን ከማየት ወጥተን ተቀላቅለን ትግሉን እናፋፍመው፤›› የሚለው ንግግሩ በከፍተኛ ጭብጨባ የታጀበ ነበር፡፡ በማጠናቀቂያ አስተያየቱም፣ ‹‹መጽሐፉን ባላነበውም ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ እንደነገሩን…›› ሲል ሲያጨበጭቡለት የነበሩትን ታዳሚዎች ያሳዘነ ነበር፡፡ በወቅቱ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አስተያየት ሰጪዎችም ይህንን ቅሬታ ነው የገለጹት፡፡ ‹‹ተቃዋሚ ነው ወይስ ጋዜጠኛ?›› የሚል ጥያቄ ከማቅረባቸውም በላይ፣ አንድ ሰው ስለማያውቀውና ስላላነበበው ለምን አስተያየት እንደሚሰጥ እንደሚያሳዝናቸው ተናግረዋል፡፡

ቀደም ሲልም የፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም መጽሐፍ ‹‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ›› ውይይት ላይ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ሰፊ ንግግር ካደረጉ በኋላ፣ ‹‹መጽሐፉን ባላነበውም…›› የሚለው ማጠቃለያቸው በታዳሚዎች ተቃውሞ አስነስቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በእንዲህ ዓይነት የፖለቲካ መጻሕፍት እንዲህ ዓይነት በዕውቀት ላይ ያልተመሠረተ አስተያየት መስጠቱ እየተበራከተ ‹‹ካላነበብን የሌሎችን አስተያየት አርፈን ብናዳምጥ የተሻለ ነው፤›› በማለት በመምጣቱ፣ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ድርጊቱ እንዲታረም አጥብቀው ያሳስባሉ፡፡

**************

*Originally published on Ethiopian Reporter, on July 17, 2013, titled “የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?› ዥንጉርጉርነት”, by Yemane Nagesh

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories